Sunday, July 19, 2020

ሕዝብ የሥልጣን ጥመኞች ሒሳብ ማወራረጃ መሆን የለበትም!

(July 19, (አዲስ አበባ))--ጽንፈኛ ፖለቲከኞች የሥልጣን ምንጭና ባለቤት የሆነውን የኢትዮጵያ ሕዝብ በመከፋፈል አንደኛው አመቺ ነው ባለው መንገድ ሥልጣኑን ሊያጠናክር፣ ሥልጣን ፈላጊው ደግሞ ያዋጣኛል ያለውን ዘዴ በመጠቀም በንፁኃን ደም ዓላማቸውን ለማሳካት ይሻኮታሉ፡፡ እነሱ ሰላማዊውንና ሕጋዊውን መንገድ ስተው የሥልጣን ረሃባቸውን ለማስታገስ ሕዝቡን በብሔርና በሃይማኖት ጭምር እያለያዩ ሲያፋጁ፣ የሚጠቀሙባቸው ያልበሰሉ ወጣቶች የተልዕኳቸው የመጨረሻ ውጤት ምን እንደሆነ ሳያውቁ አገር ያወድማሉ፡፡ በዚህ መሀል ግን አገር ሰላም ብለው ከድህነት ጋር የሚታገሉ ንፁኃን በጭካኔ ይገደላሉ፣ ይዘረፋሉ፣ ይፈናቀላሉ፡፡

ባለፉት ሁለት ዓመታት ተባብሶ የቀጠለው የጽንፈኞች ቁማር ዋና ዒላማዎች፣ በገዛ አገራቸው እንደ ባዕድ እየተሳደዱ የሚገደሉና ጥሪታቸው የሚወድም ንፁኃን ናቸው፡፡ በተለይ ብሔርተኛ የፖለቲካ ኃይሎች ለሥልጣን በሚያደርጉት ትንቅንቅ፣ ኢትዮጵያዊያን እንደ ታዳኝ አውሬ መጨፍጨፋቸው በፍጥነት መቆም አለበት፡፡ በሥልጣን ጥመኞች ምክንያት ኢትዮጵያዊያን በገዛ አገራቸው የሚደርስባቸው ግፍ በፍጥነት ካልቆመ፣ እንደ የመንና ሶሪያ የእርስ በርስ ጦርነት መነሳቱ አይቀርም፡፡ ሕግ የማይገዛቸው ጉልበተኞች በሚጭሩት እሳት በርካቶች ተቃጥለዋል፡፡ መጠኑን ለመገመት የሚያዳግት የአገር ሀብት ወድሟል፡፡ በአገሪቱ መንግሥት የሌለ እስከሚመስል ድረስ የፀጥታ ኃይሎች ዓይናቸው እያየ ዘግናኝ ድርጊቶች ተፈጽመዋል፡፡

የትምህርትና የጤና ተቋማት ሆን ብለው እንዲወድሙ ሲደረግ፣ መንግሥታዊ አገልግሎት መስጫዎችም ተቃጥለዋል፡፡ ግለሰቦች የሚቀይሩት ልብስ ሳይቀር ንብረቶቻቸው ወድመዋል፡፡ የጥቂት ሥልጣን ጥመኞችን ፍላጎት ለማርካት ሲባል፣ አስነዋሪና አሳፋሪ ድርጊቶች መቀጠል የለባቸውም፡፡

ከመስከረም 2011 ዓ.ም. የቡራዩ ጥቃት ጀምሮ እስከ ድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ድንገተኛ ግድያ ድረስ የነበሩትን ግድያዎችና ውድመቶች በአንክሮ ለሚከታተል ማንኛውም ዜጋ፣ በተለይ ለሰላማዊ የፖለቲካ ፉክክር ከውጭ የገቡ አብዛኞቹ ብሔርተኛ ድርጅቶች አመራሮችና ደጋፊዎች ምን ዓይነት ድርጊቶችን ያከናውኑ እንደነበር ግልጽ ይሆንለታል፡፡

በተለያዩ የፓርቲ ሚዲያዎችና የማኅበራዊ ትስስር ገጾች ይተላለፉ የነበሩ ቅስቀሳዎችና መልዕክቶች ኢትዮጵያዊያንን በመከፋፈል ማጣላት፣ የማዕከላዊ መንግሥቱን አቅም በማዳከም የክልሎችን መዋቅሮች ማፈራረስ፣ የብሔር አባል ያልሆኑ ማኅበረሰቦችን መግደል፣ መዝረፍና ማፈናቀል፣ ለዘመናት አብረው የኖሩ አማኞችን በሃይማኖት ለማጣላት መስጊዶችንና አብያተ ክርስቲያናትን ማቃጠል፣ ገልልተኛ መሆን የሚገባቸው የፀጥታ አካላት ውስጥ ሰርጎ በመግባት የዓላማ አስፈጻሚ ለማድረግ መሞከር፣ በታዋቂ አክቲቪስቶቻቸው አማካይነት ኢትዮጵያዊነትን የሚያመክኑ የማያቋርጡ ሐሰተኛ የታሪክ ትርክቶችን ማነብነብ፣ ወዘተ የተለመዱ ድርጊቶች ሆነው ነው የዘለቁት፡፡ በሰው አገር በሥርዓት እየኖሩ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ዕልቂትና ውድመት እንዲደርስ የሚፈልጉ ብሔርተኛ ዳያስፖራዎች ሳይቀሩ፣ ኢትዮጵያን የማፈራረስ ዘመቻ አካል መሆናቸውን በሰሞኑ ድርጊቶቻቸው በሚገባ ለመታዘብ ተችሏል፡፡

 ይህ ሁሉ የሥልጣን ጥመኞች አረመኔያዊ ድርጊት፣ ኢትዮጵያ በኮሮና ወረርሽኝና በህዳሴ ግድቡ ምክንያት ከግብፅ ጋር በተናነቀችበት ወቅት ሊረግብ አልቻለም፡፡ የሥልጣን ጥመኞቹ ዋነኛ ዓላማ ኢትዮጵያን በመበታተን ድሮ ያልተሳካውን የግንጠላ መርሐ ግብር ለማሳካት በመሆኑ፣ ከኋላ ታሪካዊ ጠላት የሆነችው ግብፅ አለችበት፡፡ የውስጥ ተላላኪዎች ንፁኃንን እየገደሉ አገር የሚያተራምሱት የግብፅ ተከፋይ ስለሆኑ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር መንቃት አለበት፡፡ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ እየጮሁ ያሉ አገር አፍራሾችን በማሳፈር ታሪክ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ መንግሥት ሥርዓት ባለው መንገድ ሕግ እንዲያስከብር ማስገደድ አለበት፡፡ ማንም ሆነ ማንም አገርን ለማተራመስና ሕዝብን ለዕልቂት ለመዳረግ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ በሕግ አደብ እንዲያስገዛ ከማድረግ ባለፈ፣ መስመሩን የሳተውንም ጭምር ልክ እንዲያስገባ ጫና ማሳደር ይኖርበታል፡፡ መንግሥትም በቁጥጥር ሥር የዋሉ ተጠርጣሪዎችን በተመለከተ የሕግ ሒደቱን ለፍትሕ አካላት በመተው፣ በሕግ የተሰጠውን ኃላፊነት ይወጣ፡፡ በፍትሕ አካላት ሥራ ጣልቃ እንዳይገባ ጥንቃቄ ያድርግ፡፡ ከአላስፈላጊ የፕሮፓጋንዳ ድርጊቶች ይቆጠብ፡፡

ጥቅም በሌላቸው ተግባራት ምክንያት ከአሁን በኋላ የአንድም ሰው ሕይወት ወይም ንብረት መጎዳት አይኖርበትም፡፡ በሕገወጥ ድርጊቶች ሳቢያም ሕዝብ መሰቃየት የለበትም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በገዛ አገሩ በፈለገው ሥፍራ የመኖር፣ የመዘዋወርና የመሥራት ተፈጥሯዊና ሕጋዊ መብቱ መከበር አለበት፡፡

በምንም ዓይነት ሁኔታ ሥጋት እንዳይገባው ሕጋዊ ዋስትና ሊኖረው ይገባል፡፡ የሥልጣን ጥመኞች ባኮረፉና ባልተመቻቸው ቁጥር መንጋ እያደራጁ፣ በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ማዝመታቸው ማብቃት አለበት፡፡ እስካሁን ለተፈጸሙ ወንጀሎችም በሕግ ተገቢውን ቅጣት ማግኘት አለባቸው፡፡ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊያን ላይ ከባህር ማዶ ሆነው ዕልቂትና ውድመት የሚያውጁ ኃይሎችም በሕጋዊ፣ በፖለቲካዊና በዲፕሎማሲያዊ መንገዶች አደብ እንዲገዙ ይደረግ፡፡

በሰው አገር በሰላም እየኖሩ ኢትዮጵያንንና ሕዝቧን ማመስ ወንጀል ነው፡፡ መንግሥት ራሱን ከአላስፈላጊ ህፀፆች በማፅዳት ሕዝብና አገርን ከወንጀለኞች ይከላከል፡፡ ውስጡ ተደብቀው አገርን ከመዝረፍ በተጨማሪ ነውረኛ ድርጊቶችን የሚፈጽሙ አድርባዮችንና አስመሳዮችን ያጋልጥ፡፡ በሁለት ቢላ የሚበሉ የአገር ፀሮች መንግሥታዊ መዋቅሮች ውስጥ ተሰግስገው፣ ሥርዓተ አልበኞችንና የሥልጣን ጥመኞችን እያገለገሉ ነው፡፡ መረጃ ከማቀበል እስከ ውንዥንብር ፈጠራ ድረስ ተልዕኮ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡

ሆን ተብለው በታቀዱ ጥቃቶች በርካቶች ሲገደሉና ንብረታቸው ሲወድም፣ በክልል መዋቅሮች ውስጥ የተሰገሰጉ አመራሮችም ተሳታፊ እንደነበሩ ግልጽ ነው፡፡ በሥራቸው ያሉ የፀጥታና የሕግ አስከባሪዎችን ተልዕኮ በማሽመድመድ ንፁኃን ሲገደሉና ንብረታቸው ዶግ አመድ ሲሆን በዝምታ አይተዋል፡፡ ማዕከላዊ መንግሥቱ የመከላከያ ሠራዊት አሰማርቶ ሁኔታዎች ሲረጋጉ ከያሉበት ብቅ እያሉ አስተዛዛኝ ይሆናሉ፡፡ ዜጎች ከጥቃት አድኑን ብለው ሙጥኝ ሲሉዋቸው ጆሮአቸው የማይሰማ እነዚህ ጉዶች፣ ራሳቸውን አደራጅተው ለመከላከል ሲንቀሳቀሱ ግን ፖሊስ ያዘምቱባቸዋል፡፡

እንዲህ ዓይነቱ ያፈጠጠና ያገጠጠ አክራሪ ብሔርተኝነት ነው ኢትዮጵያን ለማፈራረስ ዳር ዳርታ ላይ ያለው፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱን ሁሉንም የሚያስማማ በማድረግ ኅብረ ብሔራዊት አገር ለመገንባት የሚያስችሉ አሜሪካን የመሳሰሉ መልካም ምሳሌዎች እያሉ፣ አምስት ቦታ ተከፋፍላ እንደ ፈራረሰችው ዩጎዝላቪያ ዓይነት እንዲሆን የሚማስኑትን ጽንፈኛ ብሔርተኞች በቃችሁ ማለት ተገቢ ነው፡፡

ነጋ ጠባ ልዩነትን ብቻ እየሰበኩ አብሮ የኖረን ሕዝብ የሚያጋድሉና ቂም በቀል የሚጋብዙ አክራሪ ብሔርተኞች አደብ ካልገዙ፣ በኢትዮጵያ ምድር ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ የእርስ በርስ ጦርነት ከማስነሳት አይመለሱም፡፡ አሁንም ይህንን ዓላማ ለማሳካት ሲሉ በሥልጣን ጥም የናወዘ አዕምሮአቸውን የጥፋት ቤተ ሙከራ አድርገውታል፡፡ ያልበሰሉ ለጋ ወጣቶች ላይ የማያቋርጥ የፕሮፓጋንዳ መርዝ በመርጨት፣ አውዳሚ የፖለቲካ ሥልታቸውን ገፍተውበታል፡፡ ለዚህም ሲባል በአንድ ወቅት አሳሪና ታሳሪ፣ ገራፊና ተገራፊ የነበሩ ‹‹ፌዴራሊስት›› የሚል የዳቦ ስም አውጥተው አገር ለማፍረስ ተማምለው ተነስተዋል፡፡

ከድምፃዊ ሃጫሉ ግድያ በስተጀርባ ያለው ወንጀል በሕግ ፊት ፍንትው ብሎ እስኪወጣ ድረስ መታገስ ቢያስፈልግም፣ ግድያው ከተሰማ በኋላ በከፍተኛ ፍጥነትና ቅንጅት በአዲስ አበባ ከተማና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ከተሞች ዕልቂቶችና ውድመቶች ሲፈጸሙ ዓላማው ግልጽ እንደነበር አይካድም፡፡ ከግድያው በፊት ራቅ ካሉ ከገጠራማ ሥፍራዎች በሚገባ ተዘጋጅተው ከተሞች ላይ እንዲፈሱ የተደረጉት ወጣቶች፣ በሻሸመኔና በዝዋይ ከተሞች ንብረት ማጋየትና ማውደም የጀመሩት እኮ ከሌሊቱ አሥር ሰዓት ነበር፡፡ እነዚህ ከተሞች ለመድረስ ከአራት ሰዓታት በላይ መጓዝ የነበረባቸው ሲሆን፣ የከተማ ውስጥ አሰማሪዎቻቸው ደግሞ የእነ ማንን ንብረት እንደሚያወድሙ ቀደም ብለው ተዘጋጅተው ነው የጠበቋቸው፡፡

ሐዘናቸውን በአግባቡ ለመግለጽ የወጡት እኮ በሥርዓት ሲነጋ ነበር የተገኙት፡፡ ነገር ግን በሃጫሉ ድንገተኛ ሕልፈት የደነገጡ ኢትዮጵያዊያን ለመልካም ባህል፣ እሴትና ሞራል ተቃራኒ የሆኑ ድርጊቶች ሲፈጸሙ፣ የአስከሬን ነጠቃ ተካሂዶ አሳፋሪ ክስተቶች ሲያጋጥሙና በየቦታው የዕልቂትና የውድመት ዜናዎች ሲደርሱ ከፍተኛ የልብ ስብራት ነበር ያጋጠማቸው፡፡ በድምፃዊው ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች ላይ የማይሽር ጠባሳ ነው የተፈጠረው፡፡ ይህ የሥልጣን ጥመኞች ትራጄዲ ድራማ ዋናው ግቡ ኢትዮጵያን በማተራመስ የግብፅ ምርኮኛ ለማድረግ እንደነበር እንዴት ይካዳል? ይህንን አጋጣሚ ተጠቅመው አገር ለማተራመስ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ውስጥ የነበሩት የቀድሞ አምባገነኖች ፍላጎት ምን እንደሆነ አይታወቅም እንዴ? የኢትዮጵያ ወጣቶች በአንክሮ መረዳት ያለባቸው ይህንን ደባ ነው፡፡ በስሜት ሳይሆን በምክንያታዊነት አስተሳሰብ በመመራት የሥልጣን ጥመኞችን መሰሪ ሴራ ይመርምሩ፡፡

ጽንፈኛ ብሔርተኞች የኋላቀር የትግል ሥልታቸው መጠቀሚያ ለማድረግ የሚፈልጉት፣ ሐሰተኛ ታሪክ በመንዛት ኢትዮጵያዊያንን መከፋፈል ነው፡፡ በርካታ የምዕራብ አውሮፓና የእስያ አገሮች፣ አሜሪካና ሌሎችም በአገረ መንግሥት ግንባታ ወቅት ከባድ ጊዜያትን አሳልፈዋል፡፡ በዚህ ወቅት ግዛታቸውን አስፋፍተው አሁን የያዙትን ቅርፅ አግኝተዋል፡፡ በኢትዮጵያም የሆነው ይህ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያንም አንድ ሆነው ተስፋፊዎችንና ወራሪዎችን በመከላከል ቅኝ ሳይገዙ የቀሩት ግዛታቸውን ይዘው ነው፡፡ አንዱ ብሔር ሌላውን የጨቆነበት የታሪክ ምዕራፍ አይታወቅም፡፡ በዚህ ዘመን ግን ጽንፈኞች አገር ለማፍረስ ሐሰተኛ ታሪክ ፈብርከው ለኋላቀር ፖለቲካቸው መጠቀሚያ በማድረግ፣ ለዘመናት አብሮ የኖረውን ሕዝብ ማፋጀት ይፈልጋሉ፡፡ ይህንን አስነዋሪ ድርጊት የሚፈጽሙት ደግሞ በውጭ ትልልቅ ዩኒቨርሲቲዎች ጭምር ያስተምራሉ የሚባሉ ጽንፈኞች ናቸው፡፡

የትምህርት ትልልቅ ማዕረጎችን ይዘው ሰብዓዊነትን እየተዳፈሩ ዘረኝነትን በማቀንቀን ሕዝብ ያስፈጃሉ፡፡ እነሱ በሥልጣን ጥም ነደው አገር ለማንደድ የዋሁን የአርሶ አደር ልጅ ይጠቀሙበታል፡፡ ዛሬ ሥልጣኑ መንበሩ ላይ የኦሮሞ ሰው ተቀምጦ እነሱ ወደኋላ ሄደው የገባሪና የአስገባሪ ታሪክ ያነበንባሉ፡፡ የፊውዳል ሥርዓት ቀብሩ ከተፈጸመ ከ45 ዓመታት በኋላና ራስን በራስ ማስተዳደር ሦስት አሠርት አስቆጥሮ፣ ወጣቱን በበታችነት ስሜት እየነዱ ይማግዱታል፡፡ በድህነት ውስጥ የሚማቅቀውን ሕዝባቸውን ለመታደግ ሳይሆን፣ የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ለመክተት የመርዝ ፕሮፓጋንዳቸውን ይረጫሉ፡፡ ለአገሪቱም ሆነ ለሕዝቡ አንዳችም ፋይዳ ሳይኖራቸው የጠላት ተላላኪ ሆነው ያሟርታሉ፡፡ እነዚህ ለማንም የማይበጁ ስለሆኑ በቃችሁ መባል አለባቸው፡፡ ለዚህም ነው ለእነዚህ የሥልጣን ጥመኞች ሕዝብ የጥፋት ሒሳብ ማወራረጃ መሆን የሌለበት!
ሪፖርተር, አዲስ አበባ, ርዕሰ አንቀጽ

No comments:

Post a Comment