Sunday, July 19, 2020

ከኢትዮ ቴሌኮም ዕውቅና ውጪ የሚሠራ የሳተላይት መቀበያ መሣሪያ ከአቶ ጃዋር ቤት ማግኝቱን ፖሊስ ተናገረ

(July 19, (አዲስ አበባ))--ከድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ጋር በተያያዘ ተጠርጥሮ በእስር ላይ በሚገኘውና በቅርቡ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስን (ኦፌኮ) የተቀላቀለው የአቶ ጃዋር መሐመድ መኖሪያ ቤት ሲበረበር፣ ከኢትዮ ቴሌኮም ዕውቅና ውጪ የሚሠራ የሳተላይት መቀበያ መሣሪያ መገኘቱን የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ለፍርድ ቤት አስታወቀ፡፡

የምርመራ ቡድኑ ሐምሌ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. ለፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት በተፈቀደለት የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜያት የሠራውን የምርመራ ሪፖርት ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ፣ የአቶ ጃዋር ቤት በፍርድ ቤት የብርበራ ፈቃድ ሲበረበር የተለያዩ ሲዲዎች፣ ላፕቶፖች፣ ኮምፒዩተሮች፣ ፍላሾች፣ ኢንተርኔት ለየት ባለ ሁኔታ የሚጠቀሙበት ከኢትዮ ቴሌኮም ውጪ የሆነ የሳተላይት መሣሪያ ተገኝቷል ብሏል፡፡

መርማሪ ቡድኑ እንዳብራራው የድምፃዊው ግድያ ከተፈጸመ በኋላ አቶ ጃዋር ባስተላለፈው ትዕዛዝ በአዲስ አበባ የ14 ሰዎች ሕይወት መጥፋቱንና ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረት መውደሙን፣ በኦሮሚያ ክልል የወደመውን ንብረት ግምት ገና በመሥራት ላይ ቢሆንም፣ የ167 ሰዎች ሕይወት መጥፋቱንና በአጠቃላይ የ181 ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃና የሰዎች ምስክርነት ቃል መቀበሉንም ገልጿል፡፡ ብሔርንና ሃይማኖትን መሠረት ያደረገ አመፅና ዕልቂት እንዲፈጠር ጥሪ መተላለፉንና በርካታ ንብረቶች እንዲወድሙ መደረጉን የገለጸው መርማሪ ቡድኑ፣ ይህንን ድርጊት የሚያረጋግጡለት የ34 ሰዎች የምስክርነት ቃል መቀበሉን፣ 14 የምርመራ ቡድኖች በማዋቀር ከፍተኛ ጉዳት ወደ ተፈጸመባቸው ሻሸመኔ፣ አርሲ ነገሌ፣ ምሥራቅ ሐረርጌና የተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች ለምርመራ መላኩን ጠቁሟል፡፡

ተጠርጣሪው ብሔርና ሃይማኖትን መሠረት ያደረገ የእርስ በርስ አመፅ እንዲነሳ ሕገወጥ ቡድን በማደራጀትና ሕገወጥ ትጥቅ በማስታጠቅ፣ ሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. የድምፃዊ ሃጫሉ አስከሬን ወደ ትውልድ ቦታው አምቦ ከተማ እየተሸኘ እያለ ቡራዩ ኬላ ላይ ሲደርስ በአካባቢው ባለው የፀጥታ ኃይል ላይ ተኩስ በመክፈትና አስከሬን በመቀማት፣ ወደ ኦሮሚያ ብልፅግና ጽሕፈት ቤት እንዲመለስ ማድረጉን መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ የኦሮሚያ ብልፅግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤትን በኃይል ጥሰው ሲገቡ ከታጣቂ ቡድኑ በተተኮሰ ጥይት አንድ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል የፖሊስ አባል መገደሉንና ሦስት መቁሰላቸውን በፎረንሲክ ምርመራ ማረጋገጡንም አስረድቷል፡፡

ቡድኑ የታጠቃቸው የጦር መሣሪያዎች ከማንኛውም (ከክልልም ሆነ ከፌዴራል) መንግሥታዊ ተቋም ወይም የሚመለከተው አካል ፈቃድ እንዳልተሰጣቸው ማረጋገጡን መርማሪ ቡድኑ ተናግሮ፣ ይዘዋቸው የነበሩት የጦር መሣሪያዎችም አሥር ክላሽኒኮቭ ጠብመንጃዎች፣ አንድ ቺቺና ዘጠኝ የሬዲዮ መገናኛዎች መሆናቸውን፣ በእነዚህ የጦር መሣሪያዎች ሌላ ወንጀል መሠራት አለመሠራቱን ለማረጋገጥ ለምርመራ መላኩንም አስረድቷል፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች በተለይም በኦሮሚያ፣ በድሬዳዋ፣ በሐረር፣ በሻሸመኔ፣ በአርሲ ነገሌና በሌሎችም አካባቢዎች ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች 181 ሰዎች መሞታቸውንና ጠቅላላ ግምቱ ያልታወቀ በርካታ ንብረት መውደሙን ጠቁሞ፣ የቡድኑ ዕቅድ የድምፃዊ ሃጫሉን አስከሬን ለአሥር ቀናት አዲስ አበባ በማቆየት ቀጣይ አመፆችን ለማቀጣጠል እንደነበር የሚያረጋግጡ ምስክሮችን ቃል መቀበሉንም አስረድቷል፡፡

ወደ ክልል የተላከው መርማሪ ቡድን የሞቱትን፣ የቆሰሉትንና የወደመውን የንብረት ዓይነትና መጠን በማስረጃ መለየት፣ ያልተያዙ ግብረ አበሮችን መያዝ፣ ያስተላለፈውን የአመፅ ቅስቀሳ ቀጥተኛ ትዕዛዝ ከሚመለከተው [ከተጠርጣሪው] መቀበል፣ በብርበራ የተገኙ የተለያዩ ኤሌክትሮኒክስ መሣሪያዎችን ምርመራ ውጤት ለመቀበል፣ ለተለያዩ ተቋማት የተጻፉ ደብዳቤዎችን ምላሽ ለመጠበቅ፣ የሕክምና ማስረጃዎችን ለመቀበል፣ ከኦኤምኤን ጋር ያለውን ግንኙነት በሚመለከት የሚደረግ ምርመራ፣ በአዲስ አበባ ውጥረት ለመፍጠር ከሚሠሩ ኃይሎች ጋር ያለውን ግንኙነት መመርመር፣ ቀሪ ምስክሮችን ቃል መቀበል፣ በሞባይሎች የተላለፈውን የአመፅና ብጥብጥ ቀስቃሽ ጥሪ መመርመርና የባለሙያ ትንተና ለማሠራት፣ በኦኤምኤን የተላለፈ የአመፅ ጥሪ ከብሮድካስት ባለሥልጣን ለመቀበል ተጨማሪ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡

አቶ ጃዋር አራት ጠበቆች ያለው ቢሆንም ራሱ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳው፣ ሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. አንድም ጥይት አልተተኮሰም፣ ሰውም አልሞተም ብሏል፡፡ የሃጫሉን አስከሬን ይዘው እየሄዱ እያሉ ቡራዩ ኬላ ላይ ሲደርሱ መንገዱ ተዘግቶ ማለፍ ባለመቻላቸውና ለሕይወታቸውም ስለሠጉ፣ አስከሬኑን ይዘው መመለሳቸውን አስረድቷል፡፡

እንደ አቶ ጃዋር ገለጻ አስከሬኑን ይዘው ሲመለሱ ከመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር በመደዋወልና በመነጋገር፣ የኦሮሚያ ባህል ማዕከል አመቺ ስለሆነ አስከሬኑን ወደዚያ ወስደው አሳርፈዋል፡፡ ‹‹ይህ የፖለቲካ ጉዳይ ነው፡፡ የዋስ መብት ለማስከልከል ተብሎ ከግድያና ከብጥብጥ ጋር መያያዝ የለበትም፡፡ ይህም ችግር መፈታት ያለበት በፍርድ ቤት ሳይሆን በውይይትና በድርድር ነው፤›› ብሏል፡፡ ዜግነቱን ቀይሮ የመጣው ለፖለቲካ ትግል እንጂ፣ በሕገወጥ መንገድ ለመደራጀት እንዳልሆነ ተናግሮ፣ ‹‹የፖለቲካ አሠላለፍን በውይይትና በንግግር ለማስኬድ እንጂ፣ እንዲህ ዓይነት ድራማ ያደርግ የነበረን ሥርዓት አታግለን ቀይረናል፤›› ብሏል፡፡

የአቶ ጃዋር ጠበቆች በተጨማሪ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት ደንበኛቸው ከነበረበት ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ማረፊያ ቤት ተቀይሮ የታሰረበት ቦታ ምድር ቤት (ቤዝመንት) ውስጥ መሆኑን፣ በቂ ብርሃን እንደማያገኝ፣ ለመፀዳዳት በ24 ሰዓታት ውስጥ ጠዋት 12፡00 እና ከሰዓት በኋላ 12፡00 ሰዓት ላይ ብቻ በመሆኑ መቸገሩን ተናግረዋል፡፡ ከቤተሰቡ ጋር በበቂ ሁኔታ እንደማይገናኝ፣ ምግብ ከማቀበል ባለፈ በ40 ሜትር ርቀት ላይ ስለሚቆምና አቶ ጃዋር ደግሞ በርቀት የማየት ችግር ስላለበት በርቀት የሚያየው ሰው ቤተሰብ ይሁን ጓደኛ መለየት እንደሚቸገርም ገልጸዋል፡፡

ርቀታቸው ሁለትና ሦስት ሜትር እንዲሆን ቢደረግ የተወሰነ ሚስጥርም ሊነጋገሩ እንደሚችሉ አክለዋል፡፡ ጠበቆችም በበቂ ሁኔታ እንደማያገኙትና ከአንድ ጊዜ በላይ ‹‹በቃ›› እንደሚባል፣ እንዲሁም የታሰረበት አካባቢ ሜክሲኮ አካባቢ ከመሆኑ በስተቀር ትክክለኛ ቦታውና ስያሜው እንደማይታወቅም ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ መገናኛ ብዙኃን ደንበኛቸውንና (አቶ ጀዋርን) እነሱን (ጠበቆቹን) እየቀረፁ በቴሌቪዥን እያሳዩ መሆኑን ጠቁመው፣ በኅብረተሰቡ አካባቢ ተፅዕኖ የሚፈጥርና በተጠርጣሪውም ላይ ነፃ ሆኖ የመገመት ሕገ መንግሥታዊ መብት እያሳጡ ስለሆነ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ በመሀል አስቁሞ፣ ‹‹የሚዲያዎቹን ስምና ያስተላለፉትን ዘገባ ለይታችሁ አቅርቡ›› በማለት ሌላ የሚያስረዱት ካለ እንዲቀጥሉ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን በአቶ ጃዋር ላይ ‹‹ሠርቻለሁ›› ያለውን ምርመራ ከእሱ ጋር መገናኘት አለመገናኘቱን ፍርድ ቤቱ የምርመራ መዝገቡን ወስዶ እንዲያይላቸው፣ ያልያዛቸው ግብር አበሮችን ምክንያት በማድረግ ተጠርጣሪውን መያዣ ማድረግ እንደሌለበት፣ ከኦኤምኤን ጋር በተያያዘ የሚሰበስባቸው ማስረጃዎችም ቢሆኑ ዋስትና ሊያስከለክሉ ስለማይችሉ፣ የዋስ መብት እንዲከበርለት በደፈናው ‹‹የቀሩን ማስረጃዎች አሉ›› በማለት ብቻ ምን ያህል ግብረ አበሮች እንኳን እንደሚያዙ ሳይገለጽ ተጨማሪ ጊዜ ለማስፈቀድ ብቻ መባል ስለሌለበት፣ ፍርድ ቤቱ ውድቅ እንዲያደርግላቸው ጠበቆቹ ጠይቀዋል፡፡

ቡድኑ ከድምፃዊ ሃጫሉ ሞት ጋር በተያያዘ ተጠርጣሪው ባስተላለፈው ጥሪ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች የሰዎች ሞትና የንብረት ውድመት እንዳለና መርማሪ ቡድን መላኩን ቢናገርም፣ ድምፃዊ ሃጫሉ የሞተው ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. በመሆኑና አቶ ጃዋር ደግሞ የተያዘው ሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. ስለሆነ የሚያገናኘው ነገር እንደሌለም ገልጸዋል፡፡ መርማሪ ቡድኑ ማስረጃዎችን እንዲያሰባስብ ቢናገርም ከተጠርጣሪው ጋር እንዴት እንደሚያያዝም እንዳላስረዳ በመግለጽ፣ አቶ ጃዋር ከተያዘ በኋላ የተፈጸሙ የወንጀል ድርጊቶች እሱን እንደማይመለከት፣ ግድያን በሚመለከትም እሱ በቀጥታ ስለማዘዙ የተገለጸ ነገር እንደሌለም አስረድተዋል፡፡ ድርጊት ተፈጸመ የተባለውም የእሱ አጃቢዎች ትጥቅ ከፈቱ በኋላ የሆነ ነገር መሆኑንና መርማሪ ቡድኑ ከሃጫሉ ግድያ በፊት ስለተደረጉ እንቅስቃሴዎች ወይም የቃለ መጠይቅ ማስረጃዎች እያሰባሰበ እንደሆነ ቢናገርም፣ አቶ ጃዋር ማንኛውንም ነገር ፊት ለፊት ስለሚናገር ከእሱ ጋር ግንኙነት የሌለው መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር መርህ፣ ዜጋን አስሮ ማስረጃ መፈለግ ሳይሆን ማስረጃን አሰባስቦ፣ አንጥሮና አረጋግጦ መያዝ መሆኑን ደንግጎ እንደሚገኝ የገለጹት ጠበቆቹ፣ የተገኘው ማስረጃ የተጠረጠውን ሰው ሊያስከስሰው ወይም ላያስከስሰው እንደሚችል ሳይመዘን ማሰር ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን ተፅዕኖ እያሳደሩ ላሉት ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግና ሌሎች ተቋማትም ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶ ዘመቻው እንዲቆም እንዲያደርግላቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀው፣ መርማሪ ቡድኑ ያቀረበውን የምርመራ ሪፖርት በቂ ሆኖ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ መፍቀድ ሳያስፈልግ የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን አቶ ጃዋርና ጠበቆቹ ባቀረቡት ክርክር ላይ በሰጠው ምላሽ እንዳስረዳው፣ አቶ ጃዋር ታስሮ የነበረው በትውስት በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ማረፊያ ቤት ቢሆንም አሁን ታድሶ ባለቀው ቀድሞ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት የነበረና ከሜክሲኮ ወደ ቄራ በሚወስደው መንገድ ላይ በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ ነው፡፡ እስር ቤቱ ከየትኛውም እስር ቤት የተሻለና ብርሃን ያለበት ሆኖ ምድር ቤት ውስጥ ሳይሆን፣ የሕንፃው የመጀመርያ ወለል ላይ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ንፅህናውም ቢሆን እጅግ በጣም ጥሩ የሚባል በመሆኑ የተጠርጣሪው ጠበቆች ያቀረቡት አቤቱታ ከእውነት የራቀ መሆኑን አክለዋል፡፡ ከአቶ ጃዋር ንፅህና አጠባበቅ ጋር በተያያዘ የተነሳውን ቅሬታ በአስተዳደር በኩል እንደሚፈታ ተናግረዋል፡፡ ከቤተሰብ ጋር በተገናኘ የቀረበው ቅሬታ ጊዜው የኮሮና ቫይረስ ሥርጭት ያለበትና በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጭምር ለዜጎች ደኅንነት ሲባል የተወሰነ ድንጋጌ በመኖሩ ለጥንቃቄ ተብሎ እንጂ፣ መብትን ለመጋፋት እንዳልሆነ መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል፡፡ አቶ ጃዋር በርቀት የማይታየውና ቤተሰብና ወዳጆቹን መለየት ከተቸገረ በመነጽር እንዲጠቀም አሳስበዋል፡፡

ጠበቆቹ ግን እያገኙት ለብቻው እያነጋገሩት መሆኑንም አስታውቋል፡፡ ማስረጃ ማሰባሰብን በሚመለከት ድምፃዊው እንደ ሞተ ወዲያውኑ በኦኤምኤን በቀጥታ አመፅ ቀስቃሽ መልዕክት ማስተላለፉን፣ ለዚህም የ12 ሰዎች የምስክርነት ቃል መቀበሉን፣ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ጽሕፈት ቤት ግቢ የተገደለው የልዩ ኃይል አባል የተመታበት ጥይት ሁለት ቀለህ በፎረንሲክ ተመርምሮ መረጋገጡን፣ ‹‹ፖለቲከኛ ነኝ›› የሚለውን ሽፋን በመጠቀም ወንጀል መሥራት እንደማይቻልና እሱ በወንጀል ተጠርጥሮ በቁጥጥር ሥር መዋሉን አስረድቶ፣ ከሃጫሉ ግድያ በፊትም በሆነ ከግድያው በኋላ ማንንም ያለ ማስረጃ ፖለቲከኛ በመሆኑና የፖለቲካ አመለካከት በማራመዱ እንደማይታሰር በመግለጽ የጠየቀውን ተጨማሪ የ14 ቀናት ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡

የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ወንጀል ችሎት ተጠርጣሪው ጤንነቱ ተጠብቆ፣ የሰብዓዊ መብት ክብር ተጠብቆለት ከቤተሰቦቹና ጠበቆቹ ጋር እንዲገናኝ፣ የግል ንፅህናና መፀዳዳት የተፈጥሮ ሕግ እንጂ በትዕዛዝ ወይም በይሁንታ ስለማይሆን ባስፈለገው ጊዜ እንዲጠቀም በጥብቅ መታዘዙን ተናግሯል፡፡ በጠበቆቹ በኩል መገናኛ ብዙኃንን በሚመለከት የቀረበው አቤቱታ በግልጽ ባለመቅረቡና ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግም በምርመራ ያገኘውን ለሕዝብ ይፋ ከማድረጉ በስተቀር ስም አጥፍቷል የሚያስብል ነገር ለፍርድ ቤቱ የቀረበለት ነገር ስለሌለ እንዳልተቀበለው ገልጾ፣ መርማሪ ቡድኑ የጠየቀውን የ14 ተጨማሪ ቀናት በመፍቀድ ለሐምሌ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በሌላ የምርመራ መዝገብ የተካተተውና ነጋዴ መሆኑ የተገለጸው አቶ ሐምዛ ቦረና  (አዳነ) የተካተተበት ዘጠኝ ተጠርጣሪዎች በተመሳሳይ ችሎት የቀረቡ ሲሆን፣ ሁሉም ሕገወጥ ታጣቂዎች እንደነበሩ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ለፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ የፌዴራል ፖሊስና የመከላከያ ሠራዊት አባላት የነበሩና ለልዩ ጥበቃ ሥልጠና የወሰዱ መሆናቸውን መርማሪ ቡድኑ ገልጾ፣ ያለ ምንም መልቀቂያ በራሳቸው ፈቃድ ተቋማቸውን ለቀው የአቶ ጃዋር አጃቢ መሆናቸውንም አክሏል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በሕገወጥ መንገድ በታጠቁት የጦር መሣሪያ በመታገዝ ሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. የድምፃዊ ሃጫሉ አስከሬን ወደ አምቦ በመሸኘት ላይ እያለ ቡራዩ  ሲደርስ፣ በፀጥታ ኃይሎች ላይ ተኩስ በመክፈትና አስከሬኑን በግዳጅ በማስመለስ ወደ ብልፅግና ፓርቲ ኦሮሚያ ጽሕፈት ቤት እንዲገባ ማድረጋቸውን ገልጿል፡፡

በዚህ ወቅት አንድ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል ፖሊስ አባል መገደሉንና ሦስት መቁሰላቸውን፣ በአሥር ምስክሮች ማረጋገጡንና ከላይ በአቶ ጃዋር ምርምራ ላይ የገለጻቸው የጦር መሣሪያዎች መያዛቸውን አስረድቷል፡፡ አብዛኛው የማስረጃ ዝርዝር በፎረንሲክ መረጋገጡን፣ ሁከት፣ ብጥብጥ፣ የሕይወት መጥፋትና ንብረት ውድመትን በሚመለከት በግልና በመንግሥት ተቋማት ላይ በአምስት ክፍላተ ከተሞች (በአዲስ አበባ) ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ ውድመት መድረሱንም ማረጋገጡን አስረድቷል፡፡ በቁጥጥር ሥር የዋሉ 43 ተጠርጣሪዎችን ቃል መቀበሉን፣ በኦሮሚያ በተለያዩ አካባቢዎች ስለሞቱ ሰዎችና ስለወደሙ ተቋማት በደብዳቤ መጠየቁንና በአጠቃላይ ምርመራው ውስብስብና ሰፊ በመሆኑ በላይ ከአቶ ጃዋር ምርመራ ጋር በተያያዘ የተገለጸው በተመሳሳይ ሁኔታ በእነዚህ ተጠርጣሪዎችም ላይ ስለሚቀረው፣ ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት መርማሪ ቡድኑ ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ በጠበቆቻቸው አማካይነት የታሰሩት ከአቶ ጃዋር ጋር መሆኑን በድጋሚ አስታውሰው፣ ተመሳሳይ ቅሬታዎችን አስመዝግበዋል፡፡ ከቤተሰብ ጋር እንደማይገናኙ፣ ምግብ ቢቀርብላቸውም ማን እያቀረበላቸው መሆኑን ማወቅ እንዳልቻሉ፣ ከጠበቆቻቸው ጋር የተገናኙት አንድ ጊዜ ብቻ መሆኑን፣ ለአንዳንዶች ስልክ በመፍቀድ ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙ ቢደረግም ለእነሱ መከልከሉን፣ ሁሉም ታጣቂዎች እንዳልሆኑና የተወሰኑት ሾፌሮች መሆናቸውን፣ በምርመራው ማን ምን እንዳደረገ እንዲገለጽላቸው፣ ‹‹ትዕዛዝ ተቀብለው ነው? በራሳቸው ተነሳሽነት?›› የሚለው ተጣርቶ እንዲነገራቸው፣ የተወሰኑ ቃላቸውን እንዳልሰጡ፣ ከታሰሩ 16 ቀናት ቢሆናቸውም እስካሁን እንዴት የምስክሮቹን ቃል ተቀብሎ እንዳልጨረሰ፣ ፖሊስ ዳተኝነት ማሳየቱንና በነበረው ጊዜ ሥራውን በአግባቡ እየሠራ እንዳልሆነም አስረድተዋል፡፡

ነጋዴ ነው የተባለው አቶ ሐምዛ የተጠረጠረበት ወንጀልና ጥፋቱ እንዳልተነገረው፣ በጥቅሉ ሃይማኖትን መሠረት ያደረገና ብሔርን ከብሔር ጋር ለማጋጨት በሚል የቀረበው ክስ ተገቢ እንዳልሆነም ጠበቆቹ ተናግረዋል፡፡ የአንድ ብሔረሰብን ለመጉዳት የሚለው፣ ‹‹የቱን ብሔር ከየትኛው ለማጋጨት? የሃይማኖት ልዩነት በመፍጠር የተባለው የትኛውን ሃይማኖት ከየትኛው?›› በማለትም ጠይቀዋል፡፡ ተጠርጣሪ ሐምዛ በራሱ ለማስረዳት ጠይቆ ሲፈቀድለት እንዳስረዳው፣ አቶ ጃዋርና እሱ አይገናኙም፡፡ እንደ ማንኛውም ዜጋ አስከሬን አጅበው ወደ አምቦ ለመሸኘት፣ አስከሬን ከጳውሎስ ወጥቶ ዊንጌት ጋር ሲደርስ ተቀላቅሏል፡፡ ቡራዩ ኬላ ሲደርሱ በአሥር ሲኖትራኮች የተጫኑ ወጣቶች መንገዱን በመዝጋታቸው፣ ከባለሥልጣናት ጋር በመደዋወልና ‹‹ምን እናድርግ?›› ብለው በመመካከር፣ ተመለሱ ስለተባለ አስክሬኑን የብልፅግና ፓርቲ  ኦሮሚያ ጽሕፈት ቤት ይዘው መግባታቸውን አስረድቷል፡፡

ወደ ጽሕፈት ቤቱ የገቡት በሥርዓት ተከፍቶላቸው ሲሆን፣ የኦሮሚያ ፖሊስ መጥቶ አስከሬኑን ሲወስድ ‹‹በቁጥጥር ሥር ውላችኋል›› መባላቸውንም ገልጿል፡፡ መሣሪያ አስረክቡ ሲባሉ እሱ ከመንግሥት ፈቃድ የተሰጠው ማካሮቭ ሽጉጥ እንዳለውና የታጠቁት ሁሉም እንዳልነበሩ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ እሱን፣ አቶ በቀለንና አቶ ጃዋርን እንደወሰዷቸው፣ እስከዚያን ሰዓት ድረስ ምንም ዓይነት ችግር እንዳልነበረና የሚወራው ድራማ እነሱን እንደማይመለከት አስረድቷል፡፡

መርማሪ ቡድኑ በሰጠው መግለጫ ታጣቂዎቹ የመከላከያና የፌዴራል ፖሊስ አባል ሆነው እያሉ ፈቃድ ሳይጠይቁ ወይም ሕጋዊ መልቀቂያ ሳያስገቡ ስለመቅረታቸው የገለጸው ትክክል እንዳልሆነ፣ መንግሥት ራሱ ለአቶ ጃዋር የመደበላቸው ጥበቃዎች መሆናቸውን፣ በኋላ ጥበቃውን መንግሥት ሲያነሳ በስምምነት የቀሩ እንጂ በሕገወጥ መንገድ የተቀጠሩና የተደራጁ እንዳልሆኑም ጠበቆቹ አስረድተዋል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ መርማሪ ቡድን የሰጠው ምላሽ አብዛኛው ለአቶ ጃዋር ከሰጠው ምላሽ ጋር የሚመሳሰል ሲሆን፣ በቁጥጥር ሥር የዋሉት የወንጀል ሕጉን ተላልፈዋል በሚል ተጠርጥረው መሆኑን አስረድቷል፡፡ የብልፅግና ፓርቲ ኦሮሚያ ጽሕፈት ቤትን በሥርዓት ሳይሆን ሰብረው በኃይል መግባታቸውንና በተኮሱት ጥይትም የሰው ሕይወት መጥፋቱን ተናግሯል፡፡ ቡራዩ ኬላ አካባቢ ተኩስ ከፍተውና የፀጥታ ኃይሎችን አቁስለው መመለሳቸውን የሚያስረዱ አሥር ምስክሮችን ቃል መቀበሉን፣ የጦር መሣሪያ አጠቃቀምን በልዩ ሁኔታ የሠለጠኑ መሆናቸውንና የአቶ ጃዋር ትዕዛዝ በቀጥታ በመቀበል ለፀጥታ ሥራ በተሰማሩ ሰዎች ላይ መተኮሳቸውን አስረድቷል፡፡ የድምፃዊ ሃጫሉን አስከሬን ለአሥር ቀናት በማቆየትና የምንሊክን ሐውልት በማፍረስ የሃጫሉን አስከሬን እዚያ እንደሚቀብሩ ሲያደናግሩ እንደነበርም መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል፡፡

አቶ ሐምዛ በማኅበራዊ ድረ ገጽ መልዕክት በማስተላለፍ ድምፃዊ ሃጫሉ እንደተገደለ መግለጹንም አክሏል፡፡ የእሱ ሽጉጥ ሌላ ወንጀል እንደተሠራበትና እንዳልተሠራበት ለማወቅ የፎረንሲክ ምርመራ ውጤት እየጠበቀ መሆኑን በማስረዳት የጠየቀው 14 ተጨማሪ ቀናት እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ በአቶ ጃዋር የምርመራ መዝገብ ላይ ያለውን ትዕዛዝ በድጋሚ በማዘዝና 12 ቀናትን በመፍቀድ፣ ለሐምሌ 21 ቀን 2012 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment