Wednesday, July 03, 2019

ልሂቃን ከስህተት ተማሩ!

(Jul 03, (አዲስ አበባ, (ሪፖርተር) ))--የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጭቆና ቀንበር የሚላቀቀው፣ ከአስከፊው የድህነት ማጥ ውስጥ የሚወጣው፣ መብቱና ነፃነቱ ተከብሮ በሰላም መኖር የሚችለው ልሂቃን የሚባሉት የኅብረተሰብ ክፍሎች ራሳቸውን ሲገሩ ነው፡፡ በትምህርት ተቋማት፣ በፖለቲካ ፓርቲዎች፣ በሲቪክ ማኅበራት፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት፣ በእምነት ተቋማት፣ በሚዲያዎችና በመሳሰሉት ውስጥ የሚገኙ ልሂቃን ራሳቸውን መግራት ካልቻሉ አንዲት ጋት መራመድ አይቻልም፡፡ ልሂቃኑ ከታሪክ ስህተት ተምረው ለዘመኑ የሚመጥን ተግባር መፈጸም ካልቻሉ መኖራቸው ፋይዳ ቢስ ነው፡፡

የሚያጋጥሙ ችግሮችን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ፈትሸውና ተንትነው ለመፍትሔ የሚረዱ ሐሳቦችን ማቅረብ የሚገባቸው ልሂቃን፣ በአሉባልታ ትንተና ውስጥ ሲገኙ ያሳፍራል፡፡ የተለዩ ሐሳቦችን በምክንያታዊነት መሞገት የሚጠብቃቸው ልሂቃን በሴራ ንድፈ ሐሳብ ከተጠመዱ፣ መማራቸው ትርጉም አልባ ይሆናል፡፡ የቀሰሙት ዕውቀት ችግር ፈቺ መሆን ሲገባው፣ ለተጨማሪ ችግሮች መፈልፈያ ሲውል ያሳስባል፡፡

የአገሪቱን ተጨባጭ ሁኔታ ካጋጠሙና ሊያጋጥሙ ከሚችሉ ችግሮች አንፃር በመተንተን መፍትሔ መጠቆም የሚገባቸው ልሂቃን፣ በሚፈለጉበት ቁመና ላይ ሳይገኙ በስህተት ላይ የሚረማመዱ ከሆነ ኪሳራው የአገር መሆኑን ሊረዱ ይገባል፡፡ በዚህ መሠረት ራስ ላይ ፍተሻ ማድረግ የእነሱ ኃላፊነት ነው፡፡

ከአብዛኛው የኅብረተሰብ ክፍል ላቅ ያለ ግምት የሚሰጣቸው ልሂቃን፣ ልዩነትን በፀጋ ካልተቀበሉ ከሌላው ምን ይጠበቃል? በግርድፍ የቀረቡ መረጃዎችን እንዳለ ተቀብለው የሚያስተጋቡ ከሆነ፣ መረጃን የማጥለል ሥራ የማን ሊሆን ነው? ውይይትና ድርድርን ወደ ጎን በመግፋት ጠመንጃ የሚወለውሉትን የሚያበረታቱ ልሂቃን ከበዙ፣ ሐሳብን በሐሳብ ማን ሊሞግት ነው? የሌሎች ሐሳብ ግልጽ ካልሆነ ማብራሪያ መጠየቅ እየተቻለ፣ በራስ ትርጉም ብቻ የውንጀላ ፕሮፓጋንዳ መሥራት ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው? በ21ኛው ክፍለ ዘመን ውስጥ የሚኖር ጠንቃቃና ዘመናዊ ሰው ጠመንጃ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ እንዲፈተፍት አይፈቅድም፡፡

ለዚህም ነው ጠመንጃ ባነገተ ፖለቲከኛ የተደቆሰ ሰው ያ አስከፊ ታሪክ አይደገምም ማለት ሲገባው፣ ለአዲስ ጠመንጃ ነካሽ የጥብቅና ያህል ክርክር ካደረገ ከፈልኩ የሚለው መስዋዕትነት ከንቱ የሚሆነው፡፡ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ጠመንጃ እንዳይገባ ኢትዮጵያዊያን ንቁ ይሁኑ ማለት፣ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሠረቱ እንዳይበላሽ ጥንቃቄ ይደረግ ማለት ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ስሞታም ሆነ አሉባልታ መረጃ አልባ ያደርጋል፡፡

ተደጋጋሚ ስህተትም ያሠራል፡፡ ልዩነት ቢኖር እንኳ ባልጠራ መረጃ ላይ ወይም በራስ ብቻ በሚሰጥ ትንታኔ ወይም ትርጓሜ ስም ማጥፋት ነውር ነው፡፡ ‹‹ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ›› አይቻልምና፡፡ በሐሰተኛ መረጃና በተሳሳተ ትርጓሜ ማደናገር ለጊዜው ነው እንጂ የትም አያደርስም፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ የመነጋገር ባህል ብርቅ አልነበረም፡፡ ማኅበረሰቡ በተለያዩ ወጎቹና ልማዶቹ መሠረት እርስ በርሱ የሚነጋገርባቸው በርካታ ጉዳዮች አሉት፡፡ ችግሮች ሲያጋጥሙም የሚፈታባቸው ዘዴዎች ፈርጀ ብዙ ናቸው፡፡ ወደ ብዙዎቹ ልሂቃን ስንመለስ ገን ከትችት፣ ከነቀፋ፣ ከአሉባልታና ከሐሜት የዘለለ ወግ ያለው ውይይት ወይም ክርክር ይፈራል፡፡ ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት እንዲከበር ከፍተኛ ጩኸትና እሮሮ ሲሰማ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ልሂቃኑ በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ተገናኝተው ሲነጋገሩ ግን ቁጣና እልህ ጎልተው ይታያሉ፡፡ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ደግሞ ነፃ ውይይት ማድረግ አይቻልም፡፡

በአንድ ግለሰብ ሐሳብ ሥር የሚጻፉ ምላሾችን ማየት ብቻ በቂ ነው፡፡ በማኅበራዊ ሚዲያ በተሰነዘረ ሐሳብ ምክንያት ድጋፎችና ተቃውሞዎች የሚጎርፉት ግለሰቡ ካለው ቡድናዊ ትስስር አንፃር ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ለአገር የሚጠቅሙ ሐሳቦች ቢኖሩ እንኳ በከንቱ ይባክናሉ፡፡ ልሂቃኑ በሥርዓት መነጋገርና ሐሳቦች ደግሞ በክርክር መልክ መያዝ ካልቻሉ፣ እንዴት ተደርጎ ነው አገር ማቆም የሚቻለው? ይህ መልስ የሚያሻው የወቅቱ ጥያቄ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ልሂቃን ደርዝ ያለው ውይይት ኖሮ የሐሳብ ገበያው እንዲሟሟቅ ማድረግ ካልቻሉ፣ ለአገር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያላቸው ግለሰቦች ‹‹ጎመን በጤና›› ብለው ይሸሻሉ፡፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ በስድብ ምክንያት ከሐሳብ ገበያው የተገለሉ ለአገር የሚጠቅሙ ሰዎች፣ መደበኛ ሚዲያውን እየሸሹ የሐሳብ ድርቅ እየበረታ ነው፡፡ አገሪቱ የአደባባይ ሰዎችን ባጣች ቁጥር የንግግር ነፃነት ትርጉም አልባ ይሆናል፡፡ ከምክንያታዊያን ይልቅ በስሜት የሚገነፍሉ ይበራከታሉ፡፡

 እንዲህ ዓይነት ሰዎች ሲበዙ የፖለቲካው ምኅዳር የጉልበተኞች መሰባሰቢያ ይሆናል፡፡ ጉልበተኞች ሲበረቱ ደግሞ ጉዞው ጭልጥ ወዳለ አምባገነንነት እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ ልሂቃን ከገቡበት ችግር ራሳቸውን አላቀው በምክንያታዊነት ላይ የተመሠረተ የሐሳብ ፉክክር ውስጥ መግባት ካልቻሉ፣ መጪው ጊዜ ከብሩህነት ይልቅ ድቅድቅነት ያይልበታል፡፡

ሚዲያውም ቢሆን መመራት ያለበት የሙያው ሥነ ምግባር በሚፈቅደው መሠረት እንጂ፣ የመጣ የሄደውን አወዳሽና አውጋዥ በመሆን አይደለም፡፡  ልሂቃን የሚዲያ ምልከታቸው ከጎራ ድጋፍና ተቃውሞ አንፃር እንዲሆን እያበረታቱ መቀጠል አይኖርባቸውም፡፡ ‹‹የእኛ›› ወይም ‹‹የእነሱ›› የሚለው ኋላቀር ፈሊጥ ዘመን አልፎበታል፡፡ ልሂቃኑ ስለሚዲያ ነፃነት ሲነጋገሩ ከምንም ነገር በላይ ገለልተኝነቱ ሊያሳስባቸው ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ‹‹ውኃ ቢወቅጡት እምቦጭ›› ነው፡፡ ከጉዳት በስተቀር ለማንም አይጠቅምም፡፡

የመጨረሻው ነጥብ የሚሆነው፣ ‹‹አንድን ነገር በተደጋጋሚ እየሞከሩ ውጤት መጠበቅ ተላላነት ነው›› የሚለውን አባባል ማስታወስ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከስህተት መማር ብርቅ ነው፡፡ ‹‹ብልህ ከሌሎች ስህተት ይማራል፣ ሞኝ ግን ከራሱም አይማርም›› የሚለው አባባል ለዘመኑ ልሂቃኖቻችን ምሳሌ ይሆናል፡፡

የስልሳዎቹ ትውልድ በ‹ቀይ› እና በ‹ነጭ› ሽብር አማካይነት የፈጸማቸው ስህቶቶች አልታረሙም፡፡ ዛሬም ወንድም ወንድሙን ገድሎ ይፎክራል፡፡ በጎራ ተቧድነው የአንዱን ሞት ሲያሞግሡ የሌላውን የሚያንኳስሱ አሉ፡፡ ያኔ ከአንድ ርዕዮተ ዓለም (ማርክሲዝም ሌኒኒዝም) ያጣቅሱ የነበሩ ወንድማማቾች፣ የመስመር ልዩነት በማለት ተጫርሰዋል፡፡ ሰፊውን ሕዝብ ነፃ እናወጣለን ብለው በቃላት ሳይቀር ተጣልተው ተላልቀዋል፡፡

 ዛሬም ይኼ መከረኛ ሕዝብ በስሙ የሚነግዱበት በዝተዋል፡፡ ሕዝቡን እርስ በርሱ ለማጋጨት የብሔርተኝነት ቁማር ከሚጫወቱት ጀምሮ፣ ለሥልጣን ሲሉ ደም የሚያፈሱ እየታዩ ነው፡፡ አርሶ አደሩን ጥሪቱን አሽጠው መሣሪያ ያስታጠቁ ኃይሎች እነሱ ሲከብሩ፣ እሱ ግን በገዛ ገንዘቡ ድህነት ሸምቶ መጪው ጊዜ ጨልሞበታል፡፡

ልሂቃን ግን ይህንን በአደባባይ ሲያወግዙ አይሰማም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዘመናት የመከራ ጊዜያትን ተሳስቦ ያላሳለፈ ይመስል፣ መሣሪያ አስታጥቀው እርስ በርሱ የሚያባሉትን ኃይሎች ከጥቂቶች በስተቀር ደፍሮ የሚገስፅ ሽማግሌ ወይም የሃይማኖት አባት ማየት ብርቅ ነው፡፡ ልሂቃኑ ፀጉር ከመሰንጠቅ ያለፈ በተግባር የሚያሳዩት የለም፡፡ በዚህም ምክንያት ከተስፋ ይልቅ የሥጋት ደመና ነው የሚታየው፡፡

ለሕግ የበላይነት ልዕልና፣ እንዲሁም ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚጠቅሙ መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ከመነጋገር ይልቅ፣ ሕዝቡንና አገሪቱን ወደ ኋላ የሚመልሱ ስህተቶች ውስጥ መዘፈቅ ተለምዷል፡፡ በስህተት መንገድ ላይ መመላለስ በዝቷል፡፡ ሀቅን አንጥሮ ከመፈለግ ይልቅ አሉባልታ ላይ መራኮት ልማድ ሆኗል፡፡ ለዚህም ነው ልሂቃን ከስህተት ተማሩ የሚባለው፡፡
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment