Thursday, July 04, 2019

‹‹በኢትዮጵያ አንድነት የሚመጣ ካለ ግንባራችንን እንሰጣለን›› ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)

(July 04, (አዲስ አበባ))-- ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የዓመቱን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኞ ሰኔ 24 ቀን 2011 ዓ.ም. ሲያቀርቡ፣ ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ካቀረቡት ሪፖርት በተጨማሪ በወቅታዊ ሁኔታ ላይ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ዝርዝር ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፌዴራሊዝም ሥርዓቱና ተደጋግመው ከሚነሱ የክልልነት ጥያቄዎች ጋር ለተነሱላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ፣ ኢትዮጵያ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን አገር መሆኗን አምኖ አለመቀበል መጨረሻው መባላትና ኢትዮጵያንም የዓለም ውራ ማድረግ እንደሆነ ተናግረዋል።

‹‹በኢትዮጵያ አንድነት የሚመጣ ካለ ግንባራችንን እንሰጣለን›› ሲሉም ተደምጠዋል። በአገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥትና ወታደራዊ አመራሮች ላይ ከሳምንት በፊት ስለተፈጸመው ግድያ ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የዚህ ግድያ ዓላማ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ እንደሆነ በመንግሥት መገለጹን አስመልክቶ ከምክር ቤቱ አባል መፈንቅለ መንግሥት በክልል ደረጃ እንዴት ሊካሄድ ይችላል? ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹መፈንቅለ መንግሥቱን የጠነሰሱት ያወጡለትን የዳቦ ስም አናውቅም፡፡ እኛ የምናውቀው ኢ-ሕገ መንግሥታዊ ስለመሆኑ ነው፤›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

በሐዘን ድባብ ውስጥ ሆኖ የመንግሥትን ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ያዳመጠው ፓርላማ ውሎ የአገሪቱ ሕግ አውጪ ፓርላማ የሚገኝበት አራት ኪሎ አካባቢ ሰኞ ሰኔ 24 ቀን 2011 ዓ.ም. ጠዋት ጉዳይ ኖሮት ያቀና ሰው፣ በአካባቢው ከፍተኛ የፀጥታ ኃይሎች ሥምሪትና ቅኝት እንደነበር በቀላሉ ማስተዋል ይችላል፡፡

ሁኔታው ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የመንግሥታቸውን ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በዕለቱ ለፓርላማው የሚያቀርቡ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የተፈጠረ ቢሆንም፣ የነበረው የፀጥታ ኃይሎች ሥምሪትና ጥብቅ ክትትል በእጅጉ የተለየና በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ዘመን ይደረግ ከነበረው የፀጥታ አስከባሪዎች አጀብ ጋር ተመሳሳይ ነበር፡፡

ከቀበና ድልድይ ወደ አራት ኪሎ የሚወስደው መንገድ ግንፍሌ ተብሎ ከሚጠራው ድልድይ አካባቢ እስከ አራት ኪሎ ድል አደባባይ፣ እንዲሁም ከአዋሬ አደባባይ አንስቶ ወደ አራት ኪሎ የሚያወጣው መንገድ በፀጥታ ኃይሎች፣ በአመዛኙም በሪፐብሊካን ጋርድ አባላት ሥምሪትና ቅኝት ውስጥ ነበር፡፡

በፓርላማው አቅራቢያና ወደ ፓርላማው የሚወስዱ ሸለቆዎችም ሆነ በዙሪያው በሚገኙ ሕንፃዎች ላይም የሪፐብሊክ ጋርድ አባላት ቦታ ቦታዎችን ይዘው ይስተዋሉ የነበረ ሲሆን፣ በፌዴራል ፖሊስ በመደበኛነት ይጠበቅ የነበረው የፓርላማው ቅጥር ግቢም እንዲሁ በሪፐብሊካን ጋርድ አባላት ጥበቃ ሥር ነበር፡፡

በመሆኑም ከፍተሻ ጀምሮ ያለውን የደኅንነት ጥበቃ ሥራ የፌዴራል ፖሊስ አባላቱ ለሪፐብሊኩ ጋርድ ለሰዓታት አስረክበው ነበር፡፡ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. አመሻሽ ላይ በባህር ዳርና በአዲስ አበባ ከተሞች የተፈጸመው የከፍተኛ አመራሮች ግድያ ካለፈ ገና ዘጠነኛው ቀን ላይ በመሆኑ ጥቃቱን ተከትሎ የተፈጠረው ሥጋት አለመገፈፉን፣ በዕለቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የተደረገው ከፍተኛ የፀጥታ ኃይል ሥምሪትና ጥበቃ እንደማሳያ ሊወሰድ የሚችል ነው፡፡

በዕለቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ የፓርላማ ተመራጮቹ አለባበስ አገሪቱ ሐዘን ውስጥ መሆኗን የሚያስረዳ ነበር፡፡ በዚህ ድባብ ውስጥ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከሃያ ደቂቃ ገደማ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዓመቱን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን እንዲያቀርቡ፣ በአፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ ተጋብዘዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዓመታዊ ሥራ አፈጻጸማቸውን የተመለከተ ባለ 20 ገጽ ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን፣ ሪፖርታቸውም በሦስት ዓበይት ጉዳዮች ማለትም የሰላም፣ የዴሞክራሲና የመልካም አስተደደር ሥራዎች፣ የኢኮኖሚ ዕቅድ አፈጻጸምና የውጭ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ ዕቅድ አፈጻጸም ላይ ያተኮሩ ነበሩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀረቡትን ሪፖርትና ይህንን ተከትሎ ከፓርላማ አባላት ለቀረቡ ጥያቄዎች የሰጡት ማብራሪያ ዋና ዋና ጉዳዮች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

አስተዳደራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ለምክር ቤቱ ያቀረቡት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በመጀመርያ ትኩረት ያደረገው የሰላም፣ የዴሞክራሲና የአስተዳደር ጉዳዮችን በተመለከተ ሲሆን፣ በዚህ ላይ በዓመቱ የተፈጸሙ ተግባራትን ከመዘርዘራቸው አስቀድሞ ያነሱት ጉዳይ አገሪቱ በቀደሙት ዓመታት የነበረችበትን ሁኔታና የዚህ የዞረ ድምር በአገሪቱ ፖለቲካዊ አስተዳደር ላይ እየፈጠረ ያለውን ተግዳሮት ያመለከተ ነበር፡፡

እሳቸው ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው አስቀድሞ በነበረው ሕዝባዊ የለውጥ ትግልና ማብራሪያ በሌላቸው ሕዝባዊ ተቃውሞዎች አገሪቱ ለተከታታይ ሦስት ዓመታት ስትናጥ እንደነበር ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በዚህም የተነሳ የመንግሥት ፖለቲካዊና ተቋማዊ አቅሞች ተሽመድምደው እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ በወቅቱ የመንግሥት ቅቡልነት በከፍተኛ ደረጃ አሽቆልቆሉ የነበረ በመሆኑ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አገሪቱን የማቆየት ሙከራ ቢደረግም፣ የመንግሥት መዋቅር በመዳከሙ በአገሪቱ የእርስ በርስ ዕልቂት አደጋ ተጋርጦ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

በዚህ ሕዝባዊ ትግልና ተቃውሞ ውስጥ እሳቸው ወደ ሥልጣን መምጣታቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ከዚህ የመንግሥት ለውጥ በኋላም ቢሆን ቀደም ሲል የነበረው ማዕበል የዞረ ድምር ፈተናዎችን መፍጠሩን አስታውሰዋል፡፡ በዚህም የተነሳ በዜጎች ላይ ሞት፣ ጉዳትና መፈናቀል፣ እንዲሁም በመሠረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ማስከተሉንና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችን ማስተጓጎሉን ገልጸዋል፡፡

በዋናነትም አክራሪ ብሔርተኝነት፣ ግጭትና የዜጎች መፈናቀል፣ ኢመደበኛ አደረጃጀቶች (ደቦዎች) የሚፈጥሯቸው ነውጦች፣ የወሰን፣ የማንነትና የአደረጃጀት ጥያቄዎችን ተገን በማድረግ የሚከሰቱ ችግሮች፣ ሕገወጥ የመሣሪያ ዝውውር፣ የሚዲያ ጽንፈኝነት፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሁለንተናዊ (ዩኒቨርሳል) እሴቶችን ከማቀንቀን ይልቅ ወርደው ወደ እርስ በርስ ግጭቶች ውስጥ መግባት፣ በከተማ ውስጥ የተደራጁ ወንጀሎችና የኢኮኖሚ አሻጥሮች የአገሪቱን ውስጣዊ ደኅንነትና ፀጥታ የፈተኑ ችግሮች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡

አደጋዎቹን ለመቀነስና ለማስቆም የተለያዩ ዕርምጃዎች እንዲወሰዱ መደረጋቸውን፣ ከእነዚህም መካከል ከለውጡ ማግሥት ጀምሮ ለሕዝብ ተቃውሞ ምክንያት የነበሩ አመራሮችን ማንሳት፣ አሠራሮችን ማስተካከል፣ ተቋማዊ መዋቅሮች በፍጥነትና በስፋት መገንባት፣ እንዲሁም የማደስ ዕርምጃዎች መወሰዳቸውን አመልክተዋል፡፡ በመቀጠልም ሰላም ለማስፈን የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥ ተግባር መከናወኑን፣ በዚህም በአሠራርና ማሻሻያ በትምህርት የማይቀረፉትን ችግሮች በሕግ ዕርምት እንዲወስድባቸው መደረጉን ገልጸዋል፡፡

በተወሰደው የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥ ዕርምጃ የሽብር ተግባር ለመፈጸም ሲንቀሳቀስ የነበሩ 48 የሽብር ቡድን አባላትን በቁጥጥር ሥር ማዋል፣ ብሔርን መሠረት ያደረጉ ግጭቶችን በመቀስቀስና ጥቃቶች በማድረስ ዜጎች እንዲፈናቀሉ ያደረጉ 799 አመራሮችና የፀጥታ አካላት ለሕግ እንዲቀርቡ መደረጉን ለአብነት አውስተዋል፡፡

በለውጡ ማግሥት ፈታኝ የነበረው ጉዳይ የዜጎች መፈናቀል መሆኑን የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የእሳቸው አስተዳደር ወደ ሥልጣን ከመምጣቱ በፊት 1.2 ሚሊዮን ዜጎች ተፈናቅለው እንደነበር፣ በመጋቢት 2010 ዓ.ም. እሳቸው ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ደግሞ 1.1 ሚሊዮን ዜጎች መፈናቀላቸውን ገልጸዋል፡፡ በድምሩ 2.3 ሚሊዮን ከሚሆኑት የተፈናቀሉ ዜጎች መካከል ባለፉት ጥቂት ወራት ብቻ በተደረገ የጋራ ጥረት፣ 1.3 ሚሊዮን ዜጎች ወደ ቀዬአቸው መመለሳቸውንና ይህም ትልቅ ስኬት መሆኑን በሪፖርታቸው አመልክተዋል፡፡

ዴሞክራሲው የነበረበት የምኅዳር ጥበትና ተግዳሮት ለተፈጠሩ ቀውሶች ትልቅ ድርሻ እንደነበረው፣ ይህንንም ለማሻሻልና ደረጃ በደረጃ ለመቀየርና ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመሻገር፣ እንዲሁም በሕግ ከመገዛት በሕግ ወደ መተዳደር ለማደግ ጥረት መደረጉን ተናግረዋል፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማትን መልሶ ማደራጀትና ማቋቋም፣ የደኅንነት ተቋማት የዜጎትን ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶች አክብረው ተልዕኳቸውን ብቻ እንዲወጡ የማድረግና የተለያዩ አፋኝ ሕጎችን የማሻሻል ተግባራት መከናወናቸውንና በመከናወን ላይ እንደሚገኙም አስታውቀዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፖለቲካዊና በአስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ ከላይ የተገለጹትን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡ ቢሆንም፣ የምክር ቤቱ አባላት ያቀረቡዋቸው ጥያቄዎች ግን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ጉድለቶችን ወይም ቀሪ ተግባራትን አልያም አማራጭ መፍትሔዎችን ያመለከቱ አልነበሩም፡፡ በርካቶቹ የምክር ቤቱ አባላት ያቀረቧቸው ጥያቄዎች በሰሞነኛ ፖለቲካዊ ክስተቶች ዙሪያ ያጠነጠኑ ነበሩ፡፡

እነዚህም ከሳምንት በፊት በባህር ዳርና በአዲስ አበባ ከተሞች በጥይት ስለተገደሉ ከፍተኛ የመንግሥትና የመከላከያ አመራሮችና ይህንን ግድያ መንግሥት እንዴትና ለምን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ እንዳለ፣ እንዲሁም በክልል ደረጃ መፈንቅለ መንግሥት እንዴት ሊካሄድ ይችላል የሚሉ ጥያቄዎችን በማንሳት ማብራሪያ ጠይቀዋል፡፡ በሌላ በኩል ግድያውን ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩት ብርጋዴር ጄኔራል አሳምነው ጽጌ ለግድያው ምን እንዳነሳሳቸውም ማብራሪያ ተጠይቀዋል፡፡

ሌሎች የምክር ቤቱ አባላት ደግሞ በደቡብ ክልል በሕገ መንግሥቱ የተሰጠውን ነፃነት በመጠቀም ወደ አሥር የሚጠጉ ብሔረሰቦች የክልል አደረጃጀት ጥያቄ አንስተው በየምክር ቤቶቻቸው ማስወሰናቸውን በማስታወስ፣ እንደዚህ ክልል ተመሳሳይ ውስብስብ የአደረጃጀት ችግሮች ባሉባቸው ክልሎች የሚነሱ ጥያቄዎችን በጥናት ላይ በመመሥረት የሕዝቦች ጥያቄ እንዲመለስ የፌዴራል መንግሥት ክትትልና ድጋፍ ምን ሊሆን እንደሚችል ጥያቄ ቀርቧል፡፡ በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ አንድነት እንዲፈተን ምክንያት የሆነው የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ እንደሆነ ሰፊ አመለካከት ስለመኖሩ፣ የብሔር ፖለቲካና የግለኝነት አመለካከት ትውልድን እየመረዘ በመሆኑ ይህንን ቀውስ በመፍታት ምን እንደታሰበ፣ እንዲሁም ሕገ መንግሥቱ የሕዝቦችን ጥቅም ባለማስከበሩ ሊሻሻል እንደሚገባ፣ ሕገ መንግሥቱ ከተነካ አገር ይፈርሳል በሚሉ ሁለት ጫፎች የተሠለፉ ውዝግቦች በአገሪቱ ላይ ሌላ ችግር እንዳያስከትል የመንግሥት የወደፊት እይታ እንዲብራራ ከቀረቡ ጥያቄዎች መካከል ዋናዎቹ ነበሩ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሳምንት በፊት በከፍተኛ የመንግሥትና የመከላከያ አመራሮች ላይ የተፈጸመውን ግድያና የግድያው ዓላማ መፈንቅለ መንግሥት የመባሉ ተገቢነት ላይ በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹መፈንቅለ መንግሥቱን የጻፉትና ያቀናበሩት እነሱ የሰጡትን የዳቦ ስም ምን እንደሆነ እኛ አናውቅም፡፡ እኛ የምናውቀው ኢሕገ መንግሥታዊ መሆኑንና መፈንቅለ መንግሥት መሆኑን ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹መፈንቅለ መንግሥት የሚለውን ከየት አመጣችሁት አመክንዮው ምን እንደሆነ ለመረዳት ከሆነ ደግሞ፣ የኢትዮጵያን የቅርብ ዓመታት የኋላ ታሪክ መመልከት በቂ ነው፤›› በማለት በመግለጽ፣ በ1953 ዓ.ም. በንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ላይ የተፈጸመው መፈንቅለ መንግሥት ሲባል የመፈንቅለ መንግሥት ድርጊቱ ንጉሠ ነገሥቱን እንዳልገደለ፣ በተመሳሳይ በ1981 ዓ.ም. በወታደራዊው መንግሥት ላይ ተቃጥቶ የነበረው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራም ሌላ አካል አከሸፈው እንጂ፣ የአገሪቱን መሪ አለመግደሉን በመጥቀስ የሰሞኑ ሙከራም ተመሳሳይ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

የነበረው ‹‹የመፈንቅለ መንግሥት›› ሙከራ በባህር ዳር ተጀመረ እንጂ፣ እስካሁን በተደረሰበት የምርመራ ደረጃ ብቻ ሰንሰለቱ ረዥም እንደሆነ የሰንሰለቱን ጫፎች በመጥቀስ አብራርተዋል፡፡ በባህር ዳር የጀመረው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ጀምጂም በተባለ አካባቢ ገዳይ ቅጥረኞችን ያካተተ እንደነበር፣ በኦሮሚያ ክልልም የገዳይ ቅጠረኞች መረብ መያዙን፣ ለደመወዝ ጭማሪ ጥያቄ ወደ ቤተ መንግሥት ከመጡ ወታደሮች ተመክረው የተለቀቁ በዚሁ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተመልምለው መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹ሌላው ስላልተሳካ እንዴት መፈንቅለ መንግሥት ይባላል ይሉናል፤›› በማለት ጥያቄውን በመገረም መልሰዋል፡፡

ከሁሉም በላይ በመፈንቅለ መንግሥት ሙከራው የተገደሉት አመራሮች መስዋዕትነት እንደሚያሳዝናቸው የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ሰው እንዴት አምባቸውን ይገድላል? አምባቸውን እንኳን ለመግደል ሊቆጡት የሚያሳሳ ነው፤›› ብለዋል፡፡ በተመሳሳይም፣ ‹‹ሰው ጄኔራል ሰዓረ መኰንን ለመግደል እጁን እንዴት ያነሳል? ሰዓረ እኮ እንደ ዳቦ ከላይና ከታች እሳት እየነደደበት ለኢትዮጵያ አንድነት በፅናት የቆመ ነው፤›› በማለት፣ የተሰውትን አመራሮች ሰብዕና በገለጹበት ወቅት በርካታ የምክር ቤቱ አባላት ሐዘናቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው ሲያነቡ ተስተውለዋል፡፡ አያይዘውም እሳቸው ወደ ሥልጣን በመጡበት ወቅት የተሰነዘሩ ጥቃቶችን አስታውሰዋል፡፡

ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. በመስቀል አደባባይ የተቃጣውን የግድያ ሙከራ፣ በሶማሌ ክልል የኢትዮጵያን አንድነት አደጋ ላይ ለመጣል የተደረገው ሙከራ፣ በደመወዝ ጥያቄ ታጅበው ከእነ ሙሉ ትጥቃቸው ወደ ቤተ መንግሥት የሄዱ ወታደሮች ጉዳይ፣ በሦስት ወራት መንግሥት ለመሆን አስቦ በምዕራብ ኦሮሚያ የተነሳው ኃይል፣ ዜጎችን እንደ በግ እየነዱ የማፈናቀል ድርጊትና የተፈናቀሉት እንዲመለሱ ጥረት ሲደረግ ደግሞ አስገድደው መለሷቸው ተብሎ በመንግሥት ላይ የተከፈተውን አሉባልታ፣ የሕክምና ባለሙያዎች የአገሪቱን አቅም ማስተዋል እየቻሉ ተታለው የደመወዝ ጭማሪ ጥያቄ አንስተው ፖለቲካዊ ቀውስ እንዲፈጠር መደረጉን በማንሳት መንግሥታቸውንና አገሪቱን ለማዳከም የተደረጉና የቀጠሉ ድርጊቶችን ዘርዝረዋል፡፡

‹‹እውነት ከእኛ ጋር ስለሆነ ምንም አይመጣም፣ ምንም አንሆንም፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹የተጀመረው ይህ ለውጥ ለኢትዮጵያ ፍቱን መድኃኒት ነው፤›› በማለት አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

ክልላዊ አስተዳደር ከመጠየቅና ከአገሪቱ የፌዴራሊዝም ሥርዓት ጋር ተያይዞ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹ክልል የመሆን ጥያቄ ማንሳት ሕገ መንግሥታዊ ነው፡፡ ይህ መብት ሊፈጸም የሚችለው ግን በሕገ መንግሥታዊ መንገድ ብቻ ነው፤›› ብለዋል፡፡ በደቡብ ክልል የተነሱ ክልላዊ አስተዳደር ጥያቄዎችን ክልሉን የሚያስተዳድረው ደኢሕዴን እየተመለከተው እንደሆነ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በደቡብ ክልል ምክር ቤት ተቀባይነት ያገኘ የክልልነት ጥያቄን ለመፈጸም የሚቻለው በድጋሚ እየተዋቀረ የሚገኘው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሁለት እግሩ ሲቆም እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

የአንድ አዲስ ክልል መፈጠር በሌሎች ክልሎች ላይ መናጋትን ወይም ኢንፌክሽን ሳያስከትል መፈጸም እንደሚኖርበት፣ ለዚህም የሚያስፈልጉ ተቋማዊ መሣሪያዎች በሙሉ ዝግጅትና አቅም ላይ ሊሆኑ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ይህ እስኪሟላም የክልልነት ጥያቄ ያነሱ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች በትዕግሥት እንዲጠብቁ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

‹‹ከዚህ ውጪ በሌላ መንገድ ለመሄድ የሚደረግ ሙከራን የፌዴራል መንግሥት አይታገስም፡፡ በኢትዮጵያ አንድነት የሚደራደር መንግሥት የለም፡፡ በሶማሌ የሆነው በደቡብም ይደገማል፡፡ በተለመደው መንገድ እናስተካክለዋለን፤›› ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡  የፌዴራል ሥርዓቱን በተመለከተ ያለው አመለካከትና በተግባር የሚታየው የተለያዩ መሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹በተግባር የሚታየው ፌዴራሊዝምን የበለጠ የመሻት ፍላጎት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ የቆዩ የመንግሥት ሥርዓቶች ባለቤት ብትሆንም ንጉሣዊ ሥርዓትን ሞክራ ንጉሣዊ ሥርዓቱን በኃይል ያስወገደች፣ በወታደራዊ መንግሥት ውስጥ የአንድ ያልተማከለ መንግሥት ሥርዓትን ተክላ በትጥቅ ትግል ያስወገደች፣ በኋላም ያልተማከለ ፌዴራሊዝም ሥርዓትን ያቆመች መሆኗን ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ኢትዮጵያን ቤተ ሙከራ አናድርጋት፡፡ ያለውን ሥርዓት እያሻሻልንና እያዘመንን መሄድ ነው ያለብን፤›› ብለዋል፡፡

ይህ ማለት የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ ሁሉን ነገር የሚመልስ ነው ማለት እንዳልሆነ፣ በዚሁ ልክም ፌዴራሊዝም ነው ችግር ያመጣብን ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡ አሁን ባለው የፌዴራሊዝም ሥርዓት ውስጥ ያለው ትልቅ ችግር የክልል አስተዳደርን የብሔር አስተዳደር አድርጎ የመመልከት ቀበሌኛ አስተሳሰብ እንደሆነ፣ ይህም ለኢትዮጵያ ውራ ሆኖ መገኘት ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሕገ መንግሥቱን በተመለከተ ስለሚነሱ ሁለት የክርክር ጫፎች በሰጡት አስተያየት፣ ሕገ መንግሥቱ አይነካም ማለት ሕገ መንግሥቱን እንደ አንድ የቀበሌ ወረቀት አድርጎ መመልከት እንደሆነ፣ ሕገ መንግሥቱን አልቀበልም ብሎ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጡ መብቶች መጠየቅም ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሕገ መንግሥቱ ይሻሻል ብሎ ቡራ ከረዩ መፍጠርም ተገቢ እንዳልሆነ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መሻሻል እንዳለበት የሚያምን ሐሳቡን ለቀበሌው ሕዝብ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አቅርቦ ይሽጥ ሲሉ አሳስበዋል፡፡

በሕገ መንግሥቱ ዙሪያ ንትርኮች ሊነሱ እንደማይገባ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ጉዳዩን ቀለል አድርጎ ማየትና በሐሳብ ተወያይቶ መፍታት እንደሚቻል፣ ይህም ቢሆን ግን ሁሉንም የሚያስማማ ሕገ መንግሥት ሊኖር እንደማይችልና የትም አገር እንደሌለ አስረድተዋል፡፡
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment