Sunday, December 23, 2018

ከሴራ ፖለቲካ ማንም አያተርፍም!

የኢትዮጵያን የፖለቲካ ምኅዳር ካበላሹት በርካታ ከንቱ ነገሮች መካከል አንዱ ሴረኝነት ነው፡፡ ሴረኝነት የኢትዮጵያን መልካም አጋጣሚዎች ከማበላሸት አልፎ የበርካቶችን ሕይወት የቀጠፈ፣ ያሰቃየ፣ ለስደት የዳረገና ተስፋ ያስቆረጠ ነው፡፡ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከ1953 ዓ.ም. መፈንቅለ መንግሥት ማግሥት ጀምሮ እስካሁን ድረስ የሴረኞች ሰለባ ነው፡፡ በአገሪቱ ፖለቲከኞች መካከል እርግማን ያለ ይመስል ከመነጋገርና ከመደራደር ይልቅ መተናነቅ፣ ዕውቅና ተሰጣጥቶ ከመፎካከር ይልቅ መጠላለፍና መጠፋፋት ለዓመታት የዘለቀ በሽታ ነው፡፡

ይኼንን ዓይነቱን ኋላ ቀርነትና ጨለምተኝነት በጣጥሶ ለአገር ሰላም፣ ዴሞክራሲና ዕድገት ከመጨነቅ ይልቅ አሁንም በሴራ ፖለቲካ መሻኮት ቀጥሏል፡፡ ይህ የዘመናት ሕመም በገዥው ኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች መካከል ከፍተኛ ውጥረት ፈጥሯል፡፡ በኦሮሚያ ክልል በገዥው ኦዴፓና በቅርቡ ወደ አገር ቤት በተመለሰው ኦነግ መካከል መኳረፍ አሳይቷል፡፡ በሌሎች አካባቢዎችም ውስጥ ለውስጥ የሚብስለሰሉ ነገሮች አሉ፡፡ ከፖለቲካ ፓርቲዎቹ የተረፈው ሽኩቻ በየቦታው ግጭቶች እየቀሰቀሰ የንፁኃን ደም በከንቱ ይፈሳል፡፡ ሕፃናት፣ እመጫቶች፣ ነፍሰ ጡሮች፣ አዛውንቶችና አቅመ ደካሞች ይፈናቀላሉ፡፡ በሴረኞች ምክንያት የሕዝብ ሕይወት ይመሰቃቀላል፣ አገር ትቃወሳለች፡፡

እስካሁን የተመጣበት መንገድ የሕዝብን ምሬት ከመጠን በላይ በማድረጉ ምክንያት ለሦስት ዓመታት ያህል ድብልቅልቁ በወጣ ለውጥ አገሪቱ ስትናጥ ከርማ፣ ካለፉት ዘጠኝ ወራት ወዲህ አገሪቱ አዲስ የለውጥ ጉዞ ጀምራለች፡፡ ይህ ጉዞ ግን በበርካታ ፈተናዎች ተከቦ በሕዝብ ድጋፍ እዚህ ቢደርስም፣ አሁንም እጅግ በጣም የሚያሳስቡ ችግሮች ተጋርጠዋል፡፡ አልፎ አልፎ የሚፈጸሙ ስህተቶች ቢኖሩ እንኳ ይታረማሉ በሚል መንፈስ ሕዝብ አሁንም ለውጡን ደግፎ፣ አገሪቱ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንድትሸጋገር ዕገዛ እያደረገ ነው፡፡

ይኼንን የሕዝብ የለውጥ መንፈስ በመጋራት የፖለቲካ ፓርቲዎች ግንባር ቀደም አመራር መስጠት ሲገባቸው፣ አሁንም ብዙዎቹ እያንቀላፉ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አንድም ጠመንጃ ሳይተኩሱ በቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በዘንባባ ዝንጣፊ አቀባበል ከተደረገላቸው መካከል፣ ለሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉ የማይመጥን ድርጊትና ባህሪ እያሳዩ ያሉ አሉ፡፡

ከበርካታ ዓመታት ስደት በኋላ በተፈጠረው መልካም አጋጣሚ ወደ አገር ቤት ከተመለሱ በኋላ፣ ይኼንን መልካም አጋጣሚ ለማምከን መሯሯጥ ምን የሚሉት ነው? ከሰላማዊ የፖለቲካ የጨዋታ ሕግ በማፈንገጥ ትርምስ መፍጠር ምን ዓይነት ትርፍ ያስገኛል? ችግሮችን በሰከነ መንገድ መፍታት? ወይስ የተለመደው አዙሪት ውስጥ ገብቶ መፃኢ ዕድልን ማጨለም? ይህ በፍጥነት ምላሽ የሚፈልግ ጥያቄ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ የትም የማያደርስ የሴራ ፖለቲካ ታክቶታል፡፡ ሕዝብን ከድህነት፣ ከኋላ ቀርነትና ከጨለማ ውስጥ የማያወጣ ሴረኝነት፣ አገርን አተራምሶ ቀውስ ከመፍጠር የዘለለ ፋይዳ እንደሌለው ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ትናንት አምባገነንነት አገርን ቆላልፎ መላወሻ በማሳጣቱ ምክንያት የተከፈለው መስዋዕትነት ሳያንስ፣ ጥቂቶችን ሥልጣን ላይ በአቋራጭ ጉብ ለማድረግ ንፁኃንን ዕልቂት ውስጥ ለመክተት የሚደረገው ሰይጣናዊ ድርጊት መቆም አለበት፡፡

ከግለሰቦችና ከቡድኖች በላይ የሥልጣን ሉዓላዊ ባለቤት የሆነ የተከበረና የታፈረ ሕዝብ መኖሩን መዘንጋት ነውር ነው፡፡ ከምንም ነገር በላይ አገር የምትባል የጋራ ጎጆ መኖሯን ችላ ማለት ፀያፍ ነው፡፡ ከፖለቲካ ፓርቲ በላይ ሕዝብና አገር መኖራቸውን የማይረዳ ፖለቲከኛም ሆነ የፖለቲካ አቀንቃኝ ራሱን መመርመር ይኖርበታል፡፡ የሴራና የአሻጥር ፖለቲካ የኋላቀርነት መገለጫ ነው የሚባለው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ይህ ያለንበት ዘመን ለሐሳብ አፍላቂዎች ብቻ ትኩረት የሚሰጥ በመሆኑ፣ የዳበረ አስተሳሰብ ያላቸው በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ መንገድ ይፎካከራሉ፡፡ የሐሳብ ልዕልና የሌላቸው ደግሞ ሴራ እየጎነጎኑ አገር ስለሚያምሱ ፋይዳ ቢስ ናቸው፡፡


ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ሕግ ማክበርን ይጠይቃል፡፡ በየደረጃው ያሉ የአስተዳደር አካላት ውጤታማ ሆነው እንዲሠሩ ዕገዛ ይፈልጋል፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማት ጠንክረው ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበት ሥርዓት እንዲፈጥሩ እንረዳዳ ይባልበታል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱ ነፃና ገለልተኛ እንዲሆን፣ ከማንም ያልወገነ የምርጫ ቦርድ እንዲመሠረት፣ ሚዲያው በነፃነትና በገለልተኝነት እንዲሠራ፣ የፀጥታ ኃይሎች የማንም ተቀጥላ ሳይሆኑ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ፣ ወዘተ መሠረቱን በጋራ እንጣል ይላል፡፡ የሕግ የበላይነት በሚገባ ሰፍኖ ሕገወጥነት ሲመክን የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ይከበራሉ፡፡

ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በእኩልነት የሚወዳደሩበት ዴሞክራሲያዊ ምኅዳር ይፈጠራል፡፡ እነዚህ መልካም ነገሮች በኢትዮጵያ ምድር በተግባር እንዲታዩ የበኩልን ማዋጣት ሲገባ፣ ሰላምና መረጋጋት የሚያደፈርስ ድርጊት ውስጥ መገኘት ያስነቅፋል፡፡ በተለይ በዚህ ወቅት ችግሮች ቢያጋጥሙ እንኳ ቅድሚያ ለመነጋገርና ለመደራደር መስጠት ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ በማናለብኝነት ስሜት መፎከርም ሆነ እንዳሻ ለመሆን አቧራ ማስነሳት ከሕዝብ ጋር ያጣላል፡፡ ይህ ደግሞ አትራፊ አይደለም፡፡

ዘወትር እንደምንለው የአገር ህልውና ከምንም ነገር በላይ ነው፡፡ የአገሪቱ ችግሮች ደግሞ በጣም ብዙና ውስብስብ ናቸው፡፡ ተራማጅ ኃይል አገሪቱን ካለችበት አረንቋ ውስጥ አውጥቶ ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሸጋገር ሲለፋ፣ ለሚያጋጥሙ ችግሮች በጋራ መፍትሔ እየፈለጉ አብሮ መሥራት ሲገባ እንደ ጠላት ማደናቀፍ ያሳዝናል፡፡

ሕዝብ የአምባገነንነትና የጭቆና ኑሮ ሰለቸኝ ብሎ ትናንት በእንቢታው ነፃ ያወጣቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ጭምር መሰናክል  ሲሆኑ፣ ወዴት እየመለሳችሁኝ ነው ብሎ ጥያቄ ማንሳቱ አይቀርም፡፡ ይኼንን ጥያቄ ደግሞ አድበስብሶ ማለፍ አይቻልም፡፡ የዘመናት ውስብስብ ችግሮች የሚፈቱት በሴራ ፖለቲካ ሳይሆን፣ ለሕዝብ ጥቅምና መብት የሚበጀውን በማመላከትና ለተግባራዊነቱም ተግቶ በመሥራት ብቻ ነው፡፡ ከዚያ ወጪ ለአቋራጭ ሥልጣን ተብሎ ለሕዝብ የማይበጅ አጀንዳ አንግቦ መዞር ለትርፍ ሳይሆን ለኪሳራ ይዳርጋል፡፡ የሴራ ፖለቲካ ጠልፎ ሲጥል እንጂ አንድም ቀን ድል ሲያጎናፅፍ እንዳልታየ ታሪክ ብርቱ ምስክር ነው፡፡

ሕዝብ የሚፈልገው ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት ነው፡፡ እነዚህን ዕውን ማድረግ የሚቻለው ደግሞ በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ትግል ብቻ ነው፡፡ ከሴራ ፖለቲካ ማንም አያተርፍም!
(ሪፖርተር በጋዜጣዉ ሪፓርተር )

No comments:

Post a Comment