Friday, December 21, 2018

በሕገወጥነት የተጠረጠሩ 28 ትልልቅ የሪል ስቴት ኩባንያዎች ታገዱ

(Dec 21, (አዲስ አበባ))--የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሕገወጥነት የጠረጠራቸውን 28 ትልልቅ የሪል ስቴት ኩባንያዎች አገደ፡፡ በምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) የተቋቋመው ኮሚቴ በሪል ስቴት ኩባንያዎች ላይ የዳሰሳ ጥናት ካደረገ በኋላ አገልግሎት እንዳያገኙ አግዷል፡፡

የታገዱት የሪል ስቴት ኩባንያዎች ኖህ ሪል ስቴት፣ ሰንሻይን፣ አያት፣ ሳትኮን ኮንስትራክሽን፣ ሴንቸሪ 21 ኮንስትራክሽን፣ ሙለር፣ ሳንታ ማርያ፣ ዋይቲዋይ ኮንስትራክሽን፣ ኃይሌና ዓለም ሪል ስቴት፣ ሰዒድ መሐመድ፣ ማኅተባይ ሪል ስቴት፣ አደይ አበባ፣ ፍሰሐ ሴት፣ ናታን፣ ጌታቸው ወልዴ፣ ወልመስ ኮንስትራክሽን፣ ሐውስ ዊዝደም የጋራ መኖሪያ ቤቶች፣ ዮሐንስ ካሳዬ፣ የማናት፣ ዛምራ ትሬዲንግ፣ ማክሮ፣ ሮማናት፣ ፀሐይ ሪል ስቴት፣ መክሊት ሪል ስቴት፣ ጎላጉል ሪል ስቴት፣ ካሩቱሪ ሪል ስቴት፣ ባታ ሪል ስቴትና ፈቃዱና ጓደኞቹ ሪል ስቴት ኩባንያዎች ናቸው፡፡

በዕግዱ መሠረት የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የመሬት ባንክና ማስተላለፍ ጽሕፈት ቤት፣ ከሰኞ ታኅሳስ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ለሚቀጥሉት 15 ቀናት ለሪል ስቴት ኩባንያዎቹ ምንም ዓይነት አገልግሎት እንደማይሰጥ አስታውቋል፡፡ የሪል ስቴት ኩባንያዎች የተጠረጠሩት በሕገወጥነት፣ በተለይም መሬት ያገኙበት መንገድ፣ ግንባታ የሚያካሂዱበት አግባብ፣ እንዲሁም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ለሦስተኛ ወገን ለማስተላለፍ የሚያቀርቡት የአገልግሎት ጥያቄ ብዛትና ፍጥነት የአስተዳደሩን ጥርጣሬ ከፍ እንዳደረገው ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ትልልቆቹ ሪል ስቴት ኩባንያዎች የገነቧቸውን ቤቶች ለሦስተኛ ወገን ለማስተላለፍ የሚያካሂዱት እሽቅድምድም ጥርጣሬ አሳድሯል፡፡

‹‹ለሦስተኛ ወገን ለማስተላለፍ የሚደረገው የስም ማዘዋወር ሩጫ ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሀብት እንደ ማሸሽ ይቆጠራል፤›› በማለት የገለጹት ኃላፊው፣ ‹‹የታገዱት የሪል ስቴት ኩባንያዎች ሰሞኑን በተለያዩ ወንጀሎች ከሚጠረጠሩ ሰዎች ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው ይችላል የሚል ጥርጣሬ በሰፊው ተፈጥሯል፤›› በማለት፣ አስተዳደሩ የወሰደውን የጥርጣሬ ዕርምጃ መነሻ ምክንያት አብራርተዋል፡፡  የተቋቋመው ኮሚቴ ከመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ጋር በቅንጅት ጥናት ካካሄደ በኋላ ሕጋዊ ሆነው ለሚገኙት አገልግሎት መስጠትን የሚጀምር መሆኑን፣  ችግር እንዳለባቸው ማረጋገጫ በሚቀርብባቸው ላይ ደግሞ የማስተካከያ ዕርምጃ ይወስዳል ተብሏል፡፡

ቀደም ሲል በ2002 ዓ.ም. በቀድሞ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ጊዜ በሪል ስቴት ኩባንያዎች ላይ ዕርምጃ ተወስዶ ነበር፡፡
በተለይ ከከተማ አስተዳደሩ መሬት ወስደው ባላለሙ፣ የወሰዱትን ቦታ ሳያለሙ ለሦስተኛ ወገን ባስተላለፉ፣ በወሰዱት የግንባታ ፈቃድ መሠረት ሳይሆን በራሳቸው ፍላጎት በገነቡ ላይ፣ ሕጋዊና አስተዳደራዊ ዕርምጃ ተወስዶባቸው ነበር፡፡
ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ምክትል ከንቲባ ታከለ የሪል ስቴት ኩባንያዎች ሕጋዊነት ጉዳይ እንዲመረመር ያዘዙ ሲሆን፣ ውጤቱ ከ15 ቀናት በኋላ መታወቅ ይጀምራል ተብሏል፡፡ 
(ሪፖርተር ውድነህ ዘነበ)

No comments:

Post a Comment