Friday, December 21, 2018

የሕወሓት የፓርላማ አባላት የተቃወሙት የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ፀደቀ

(Dec 21, (Addis Ababa))---የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሥራ አስፈጻሚው መንግሥት የቀረበለትን የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅን፣ ሐሙስ ታኅሳስ 11 ቀን 2011 ዓ.ም. በተለየ ሁኔታ የጋለ ክርክር አካሂዶ በአብላጫ ድምፅ አፀደቀ። በምክር ቤቱ መቀመጫ ያላቸው የሕወሓት አባላት ረቂቅ አዋጁ ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ መፅደቅ የለበትም በማለት ከፍተኛ ክርክር አድርገዋል። የወሰንና የማንነት ጉዳይን የሚመለከት ሥልጣን በሕገ መንግሥቱ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የተሰጠ በመሆኑ ተመሳሳይ ኃላፊነት ለኮሚሽኑ ሊሰጥ አይገባም ሲሉ ሞግተዋል።

አዋጁን በማፅደቅ ኮሚሽኑ እንዲቋቋም ማድረግ ሕገ መንግሥቱን በሁለት መንገድ እንደሚጣረስ አውስተው፣ አንድም የፌዴሬሽን ምክር ቤትን ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣን በመንጠቅ በሌላ በኩል ደግሞ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ያልተከተለ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ማድረግ መሆኑን በመጥቀስ ተከራክረዋል።

የሕወሓት ከፍተኛ አመራር የሆኑት የምክር ቤቱ አባል አቶ አጽብሃ አረጋዊ አዋጁ ከሕገ መንግሥቱ ጋር የሚጣረስ መሆኑን በመግለጽ ከተከራከሩ በኋላ፣ ‹‹በቀላሉ እንደሚፀድቅ እርግጠኛ ነኝ፣ ነገር ግን የሚያመጣውን ጣጣ ቆም ብለን ብናይ?›› ሲሉ ጠይቀዋል።  አቶ አጽብሃ ይህንን መናገራቸው በአንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ላይ ቁጣን ፈጥሯል። ከእነዚህም መካከል የአዴፓ አባል የሆኑት የምክር ቤቱ አባል አቶ አጥናፍ ጌጡ ይገኙበታል።

አቶ አጥናፍ በሰጡት አስተያየት፣ ‹‹ጣጣ ያመጣል፣ አደጋ አለው የሚሉ ኃይለ ቃሎችና ማስፈራሪያዎችን መናገር ለዚህ ምክር ቤት አይመጥንም፣›› ሲሉ የግሳፄ ይዘት ያለው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ይህ አዋጅ ለውጡ ያመጣው ዕድልና ለአገሪቱ ሕዝቦች ሰላም የሚሰጥ መሆኑንም አክለዋል። ኮሚሽኑን እንዳይቋቋም የሚፈልጉ ወገኖች ኮሚሽኑ ሕገ መንግሥቱ የማይሸፍናቸውን የማንነትና የወሰን ጉዳዮች ጭምር ወደኋላ ሄዶ ያያል ከሚል ሥጋት እንደሚቃወሙት ጠቅሰው፣ ኮሚሽኑ ወደ ኋላ ሄዶ ሕገ መንግሥቱ የማይሸፍናቸውን ጉዳዮች ጭምር ሊመረምር እንደሚገባ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

በረቂቁ ላይ ዝርዝር ምርመራ በማድረግ የውሳኔ ሐሳብ ያቀረቡት የፓርላማው የውጭ ግንኙነትና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ዳባ የኮሚሽኑ መቋቋም ከሕገ መንግሥቱ ጋር እንደማይጣረስ፣ እንዲሁም የፌዴሬሽን ምክር ቤትን ሥልጣን እንደማይጋፋ ተናግረዋል። የፌዴሬሽን ምክር ቤት በቋሚ ኮሚቴው በኩል በረቂቅ አዋጁ ላይ አስተያየቱን እንዲሰጥ መደረጉን የተናገሩት አቶ ተስፋዬ ኮሚሽኑ መረጃ የመሰብሰብ፣ የመተንተንና ለሚመለከታቸው አካላት ምክረ ሐሳብ የማቅረብ ኃላፊነት ብቻ እንደሚኖረው አስረድተዋል።

የፌዴሬሽን ምክር ቤት አስፈላጊ ነው ብሎ ካመነበት ምክረ ሐሳቡን ሊቀበል እንደሚችል፣ በራሱ መንገድም ተመሳሳይ ኃላፊነት ያለው ኮሚሽን ወይም ተቋም እንዳያቋቁም የሚከለክለው ነገር ባለመኖሩ ከሕገ መንግሥቱ ጋር እንደማይጣረስ አስረድተዋል። ሌሎች የምክር ቤት አባላት በሰጡት አስተያየት ደግሞ የዜጎች ሰብዓዊ መብቶች ሲጣሱና ሲኮላሹ የሕገ መንግሥት ጥሰት ጥያቄ ሳይነሳ፣ ለሰላም ፋይዳ ያለው ኮሚሽን እንዳይቋቋም የሕገ መንግሥት መጣረስን እንደ ምክንያት ማቅረብ እንደማይገባ በመግለጽ ተከራክረዋል።

አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ በቂ ክርክር እንደተደረገ ገልጸው ፓርላማው ወደ ድምፅ መስጠት የተሸጋገረ ሲሆን፣ በስብሰባው የታደሙት 33 የሕወሓት አባላት የተቃውሞ ድምፅ ሰጥተዋል።  አራት የደኢሕዴን አባላት ደግሞ የተዓቅቦ ድምፅ ሰጥተዋል፡፡ በዚህም መሠረት የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽንን ለማቋቋም የቀረበው ረቂቅ አዋጅ በአብላጫ ድምፅ ፀድቋል።
ሪፖርተር ዮሐንስ አንበርብር

No comments:

Post a Comment