Friday, July 17, 2020

ግብፅ የዓባይን ውኃ ለመቆጣጠር በያዘችው አቋም ምክንያት የህዳሴ ግድብ ድርድር ተቋረጠ

(July 17, (ሪፖርተር))--በአፍሪካ ኅብረት መሪነት ሲካሄድ የነበረው የታላቁ ህዳሴ ግድብ ድርድር ያለ ስምምነት ተቋረጠ፡፡ ግብፅ ከድርድሩ ይዘት በመውጣት የዓባይን ውኃ የመቆጣጠር አቋም በመያዟ፣ ለድርድሩ መቋረጥ ምክንያት መሆኗን ኢትዮጵያ አስታውቃለች፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ (አምባሳደር) ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ላለፉት 11 ቀናት በኢትዮጵያ፣ በግብፅና በሱዳን መካከል የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የውኃ ሙሌትና አስተዳደርን አስመልክቶ ሲካሄድ የቆየው ድርድር ከስምምነት መድረስ ባለመቻሉ ምክንያት፣ ድርድሩ ሰኞ ሐምሌ 6 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት ላይ ተቋርጧል፡፡

ድርድሩ ያለ ስምምነት የተቋረጠበት ምክንያትም የግብፅ መንግሥት ድርድሩ ከሚያተኩርበት ጭብጥ በመውጣት የዓባይ ውኃን ለመቆጣጠር ያለሙ ጉዳዮች እንዲካተቱ በመጠየቁ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በግብፅ በኩል የተነሱትን እነዚህን ፍላጎቶች እንደማትቀበል አቋም በመያዟ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

የግብፅ መንግሥት ተደራዳሪዎች ከዚህ ቀደም በነበሩት ድርድሮች ሲያነሷቸው የነበሩት የዓባይ ውኃን የተመለከቱ ጉዳዮች፣ በዚህኛው ዙር ድርድርም ይዘው መቅረባቸውን ዲና (አምባሳደር) ገልጸዋል፡፡

በግብፅ በኩል የተነሳው አጀንዳ ኢትዮጵያ የዓባይን ውኃ በቀጣይ እንዳታለማ በስምምነት ለማሰር ያለመ መሆኑን የገለጹት ቃል አቀባዩ፣ የግብፅ ፍላጎት ድርድሩን በመንተራስ የአሁኑንም ሆነ ቀጣዩን የኢትዮጵያ ትውልድ የተፈጥሮ ሀብቱ በሆነው የዓባይ ውኃ ላይ የመወሰን ሉዓላዊ መብቱን የሚገፍ መሆኑን አመልክተዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት የአፍሪካ ኅብረትና ሌሎች ታዛቢዎች ለተወጡት ሚና ከፍተኛ አክብሮት እንዳለው የገለጹት ቃል አቀባዩ፣ አሁንም ቢሆን በሦስቱ አገሮች መካከል ያለው ልዩነት በአፍሪካ ኅብረት ሚናና በሦስቱ አገሮች በጎ ፍላጎት መፈታት እንደሚችል ኢትዮጵያ እንደምታምን አስረድተዋል፡፡

የሰሞኑን ድርድር አስመልክቶ ድርድሩን ሲታዘቡ የነበሩ ባለሙያዎች፣ ሪፖርታቸውን አጠናቅረው ለአፍሪካ ኅብረት የሚያስገቡ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡

የድርድሩን መቋረጥ አስመልክቶ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሽኩሪ ለግብፅ ሚዲያዎች በሰጡት መግለጫ፣ መንግሥታቸው መፍትሔ ፍለጋ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የፀጥታው ምክር ቤት  በድጋሚ አቤቱታ ያቀርባል ብለዋል፡፡

‹‹የግብፅን፣ የአካባቢውና የዓለምን ሰላምና ደኅንነት ሥጋት ላይ የሚጥል ማንኛውም አካል ሲፈጠር፣ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ሥጋቱን የመቅረፍ ኃላፊነት አለበት፤›› ሲሉም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

በእንግሊዝ አገር የሚታተመው ቴሌግራፍ የተባለው ጋዜጣ ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ይዞት በወጣው ዘገባ፣ የጦር መሣሪያ የጫነ አንድ አውሮፕላን ከግብፅ ተነስቶ ሶማሊያ ማረፉን አስነብቧል፡፡ እንደ ዘገባው ከሆነ ግብፅ ይህንን ያደረገችው ለኢትዮጵያ መንግሥት መልዕክት ማስተላለፍ ፈልጋ ነው፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት የህዳሴ ግድቡ የልማት ፕሮጀክት መሆኑንና ምንም ዓይነት የደኅንነት ሥጋት እንደማያመጣ በማስታወቅ፣ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በግድቡ ላይ ያለውን የሦስቱ አገሮች ልዩነት እንደ ፀጥታ ችግር እንዳያስተናግድ ማሳሰቡ ይታወሳል፡፡

የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ይህንን ጉዳይ የሚያስተናግድ ከሆነ ማለቂያ የሌላቸው ተመሳሳይ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ የሚነሱ አቤቱታዎችን ለመመልከት እንደሚገደድ፣ ይህም የተቋሙን ህልውና እንደሚፈታተን ገልጾ ነበር፡፡

ግብፅ ወደ ሶማሊያ የላከችው የጦር መሣሪያ በኢትዮጵያ በኩል የቀረበውን መከላከያ ሙግት ለመቀልበስ፣ የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በህዳሴ ግድቡ ላይ የቀረበለትን አቤቱታ እንዲመለከት ለማድረግ የተጠነሰሰ ሴራ መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞች ይገልጻሉ፡፡

የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ደግሞ የሰሞኑ ድርድር የተቋረጠው በድርድሩ የሚደረሰው ስምምነት አስገዳጅ መሆን ይገባዋል በሚለው ነጥብ መሆኑን፣ ኢትዮጵያ ደግሞ አስገዳጅ ስምምነቱ ወደፊት በዓባይ ውኃ የመጠቀም መብቷን የሚነፍግ መሆኑን በመግለጽ በመቃወሟ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
ሪፖርተር, አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment