Sunday, September 01, 2019

በኦሮሚያ የቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት እንዳይቋቋም ቅዱስ ሲኖዶስ መንግሥትን ተማፀነ

(Sep 01, (Addis Ababa))-- ቤተ ክርስቲያን መሬት ወራሪ አይደለችም ተብሏል..
በኦሮሚያ ክልል የኦሮሚያ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት ለማቋቋም በሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን እየተደረገ ያለውን እንቅስቃሴ መንግሥት እንዲያስቆምለት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ተማፀነ፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክህነት ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ርዕሰ ደብር መሐሪ ኃይሉ አማካይነት ዓርብ ነሐሴ 24 ቀን 2011 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ እንዳስረዳው፣ ለሁለት ተከፍሎ የነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ አንድ ሆኖና ተስተካክሎ በሚገኝበት በአሁኑ ጊዜ፣ ሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን የኦሮሚያ ቤተ ክህነትን በክልል ደረጃ ለማቋቋም እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ታውቋል፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጥያቄ በማቅረብና አስፈላጊውን ዝግጅት አድርገው እንደጨረሱ በማስመሰል ነሐሴ 26 ቀን 2011 ዓ.ም. ለገሃር አካባቢ በሚገኘው የኦሮሞ ባህል ማዕከል ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን በተለያዩ ድረ ገጾች ማሠራጨታቸውንም ተናግረዋል፡፡

ጥያቄ ማቅረቡ መብት ቢሆንም በምዕመናንና በተከታዮቻቸው ታምኖበትና ውይይት ተደርጎበት በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኖ ካልሆነ በስተቀር፣ በዘፈቀደ ‹‹እንደዚህ አደርጋለሁ›› ብሎ መነሳቱ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚብስ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ማሳወቁን ምክትል ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡ በዘፈቀደ የሚደረግ ነገር አቅጣጫውን ይስትና ጉዳቱ የሰፋ ስለሚሆን በሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ ሊሰጥ የተዘጋጀውን መግለጫ ቅዱስ ሲኖዶስ የማያውቀው በመሆኑ፣ የመንግሥት አካል ድርጊቱን እንዲያስቆምለት ተማፅኖውን አቅርቧል፡፡

በሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ የሚመራው የኦሮሚያ አደራጅ ኮሚቴ ዝግጅት ሲያደርግ ከርሞ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት ጥሪ ካደረገ በኋላ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ተቃውሞ ያቀረበው ለምን እንደሆነና ከጅምሩ ማስቆም ሲችል ለምን ዝም ብሎ ሲመለከት እንደከረመ ማብራሪያ የተጠየቁት የቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ፣ ምላሽ ሳይሰጡ ከአዳራሽ ወጥተው ሄደዋል፡፡ ከእሳቸው ጋር የነበሩ የቤተ ክህነት የተለያዩ የሥራ ክፍል ኃላፊዎች ግን የየራሳቸውን አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ኃላፊዎቹ እንደተናገሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በኦሮሚያ ውስጥ ሰፊ ሥራ እየሠራች ነው፡፡ የሚባለውና አሁን እየተደረገ ያለው ነገር ፍጹም አይገናኝም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ዘርን፣ ጎሳን፣ ቀለምንና ነገድን ማዕከል አድርጋ አትሠራም ብለዋል፡፡

ሰው መሆንና የእምነቱ ተከታይ መሆን ብቻ በቂ ነው ብለው፣ ይህ ሲባል ግን አማኞች በራሳቸው ቋንቋ ትምህርተ ወንጌል እንዲማሩ፣ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት እንዲያውቁ ሰፊ ሥራ ተሠርቷል ሲሉ አስረድተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ባላት መዋቅር ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ናት›› ካሉ በኋላ፣ ለ27 ዓመታት ተሰዶ የነበረ ሲኖዶስ አንድ ሆኖ፣ በአዲስ መንፈስ ህልውናዋን አጠናክራ ወንጌልን በማገልገል ላይ እያሉ እንዲህ ዓይነት ነገር መከሰቱ ሁላችንንም አሳዝኖናል ብለዋል፡፡

ይህ እንቅስቃሴ ትልቅ አደጋ የሚያስከትል መሆኑን የገለጹት ኃላፊዎቹ፣ ሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ ጥያቄ ማንሳታቸው ተገቢ ቢሆንም፣ የቤተ ክህነትን ሕግጋት ተከትሎ መሆን እንደበረበትም ጠቁመዋል፡፡ ጥያቄው ቀደም ባሉት ጊዜያትም በተደጋጋሚ መነሳቱን አስታውሰው ጥናት እየተካሄደ የቤተ ክርስቲያኗን ቀኖናና ሥርዓት በማያፋልስ መንገድ መልስ ለመስጠት፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

አሁን ያለውን የኢትዮጵያን ጉዳይ ቤተ ክርስቲያን በተለያየ ሁኔታ በቃጠሎ፣ በመፈናቀልና የተለያዩ ፈተና ውስጥ ባለችበት ወቅት ይህ ጥያቄና እንቅስቃሴ መነሳቱ ሁሉንም እንዳስደነገጣቸው ኃላፊዎቹ አልሸሸጉም፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መሬት ወራሪ አለመሆኗን የገለጹት ኃላፊዎቹ፣ በአሁኑ ጊዜ እየተነገረ ያለው ‹‹መሬት ወራሪ ነች›› በማለት ሕዝቡን ወዳልተፈለገ ቦታ ለመክተት መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

አዲስ አበባ ውስጥ የተሠሩትን አብያተ ቤተ ክርስቲያን መመልከት ቢቻል፣ በወረራ መሬት ላይ የተሠራ አንድም ቤተ ክርስቲያን እንደማይገኝም አክለዋል፡፡ የኦሮሞ አርሶ አደር ተወርሮ የተሠራ ቤተ ክርስቲያን እንደሌለ ምሳሌ የጠቀሱት ኃላፊዎቹ በኮዬ ፈጬ፣ በቦሌ አራብሳና በጀሞ ኮንዶሚኒየም፣ እንዲሁም አይሲቲ ፓርክን ጨምሮ በሙሉ የተሠራባቸውን ቦታዎች መመልከት ቢቻል የኦሮሞ አርሶ አደር መሬት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በእነዚህ ቦታዎች ላይ ግን አንድም  ቤተ ክርስቲያን  አለመሠራቱን ጠቁመዋል፡፡ ለኢንዱስትሪ ዞንና የተለያዩ ነገሮች ሰፋፊ ቦታዎች ታጥረው ባሉበት ሁኔታ፣ ቤተ ክርስቲያን መሬት እንደወረረች ተደርጎ መወራቱ ተገቢ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ መጻሕፍትን በኦሮሚኛ በማስተርጎም፣ ስብከትና ቅዳሴ ጭምር በክልሉ እየሰጠችና በርካታ አገልግሎቶች እየተሰጡ መሆኑንም አክለዋል፡፡

ጥያቄው መቅረቡና ቢቋቋምስ ምን ችግር አለው ተብለው የተጠየቁት ኃላፊዎቹ፣ ጥያቄ መቅረቡ ችግር ባይሆንም፣ ‹‹ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አንድ ናት፣ አትከፋፈልም፣ ሐዋርያት በሠሯት በአንዲት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤›› ብለዋል፡፡ በስደት በነበረችበት ጊዜ እንኳን ዶግማዋና ቀኖናዋ ቋንቋን መሠረት አድርጎ የተቋቋመ አለመሆኑንና ቋንቋ መገልገያ እንጂ መከፋፈያ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡ ሃይማኖት አንድ ያደረገውን ቋንቋ ገድቦ ሊያለያየው አይችልም ብለው፣ ቋንቋን መሠረት ያደረገ መከፋፈል ካለ ለኦርቶዶክስ እምነት ብቻ ሳይሆን ለሌላውም እምነት አደጋ መሆኑን አስምረውበታል፡፡

የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ መሆናቸውንና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊና ጉዳይ አስፈጻሚ መሆናቸውን የገለጹት አባ ወልደየሱስ እንደናገሩት፣ በጥቅምት ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ አባገዳዎችን ጨምሮ በርካታ ልዑካን ከኦሮሚያ በስብሰባው ላይ ተገኝተው ነበር፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስ ሐሳብ አቅርበው ነበር ብለዋል፡፡

ግን ያነሱት ቤተክህነት ስለማቋቋም ሳይሆን በኦሮሚያ የሚደረገው አገልግሎት በቂ አለመሆኑን ነበር፡፡ በዚህም መሠረት ቅዳሴ በኦሮሚኛ እንዲደረግ ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል ብለዋል፡፡ ‹‹በዓለም ቋንቋ ሁሉ ወንጌልን ስበኩ›› ስለሚል ትልቁ መጽሐፍ፣ በኦሮሚኛም ሆነ በሌላውም ቋንቋ እንደሚቀድሱ፣ እንደሚሰብኩና እንደሚዘምሩ ተናግረዋል፡፡ ሃይማኖት ቋንቋ እንደማያግደውና ድንበርም እንደሌለው አስረድተዋል፡፡ አሥራ አንድ ጳጳሳት ከኦሮሚያ የተመረጡና የኦሮሞ ተወላጅ መሆናቸው ምንም ዓይነት መድልዎ እንደሌለ አመላካች መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ለኦሮሚያ ክልልና ሕዝብ የሚያስፈልገውን ለማድረግ ቤተ ክርስቲያን ዝግጁ ስለሆነች፣ ‹‹ቤተ ክህነት እናቋቁም›› ሳይሆን የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ መሆኗንም ተናግረዋል፡፡ በነገድና በቋንቋ ተሸፍኖ ሌላ ነገር ለማራመድ መንቀሳቀሱ ግን እንደማያዋጣ አስረድተዋል፡፡ ‹‹አይደለም የእምነቱ ተከታይ መንግሥት የሃይማኖት አንድነትን ጠብቆ እያጠናከረ ባለበት ሁኔታ ዘረኝነት እንዲጠፋ፣ ቆሻሻ የሆነ የዘረኝነት አመለካከት እንዲወገድ ዓለማዊው መንግሥት ካደረገ፣ መንፈሳዊው መንግሥት ደግሞ ሰው ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት እኩል ነው ይላል፤›› ብለዋል፡፡

የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ለመሆን መሥፈርት እንደማያስፈልግ፣ ዘር፣ ቀለም ሳይሆን ሰው መሆን ብቻ በቂ በመሆኑ፣ ‹‹እኛ አማራ ክልልና ትግራይ ክልል ሄደን በእንተ ስሟ ለማርያም ብለን ነው ተምረን አሁን እያገለገልን የምንገኘው፤›› ብለዋል፡፡ ዲያቆናቱን ቀሳውስቱን፣ መነኮሳቱንና ጳጳሳቱን እዚህ ያደረሰው የአማራና የትግራይ ሕዝብ መሆኑንም ደጋግመው ተናግረዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በኦሮሚያ ክልል የ‹‹አብነት ትምህርት ቤቶች›› ስለሌሉ መሆኑንም አክለዋል፡፡ አሁን ግን በሁሉም ቦታ ‹‹የአብነት ትምህርት ቤቶች›› መቋቋማቸውንና በቋንቋቸው ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ኦሮሚያ ክልል የፌዴራል መንግሥት መሆን እንደማይችለው ሁሉ፣ የኦሮሞ ሀገረ ስብከት እንጂ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ማቋቋም እንደማይቻልም አክለዋል፡፡ የሚጠቅመውም የኦሮሞ ዲያቆናት፣ ቀሳውስትና ጳጳሳትን ማብዛት እንጂ ቤተ ክህነት ማቋቋም አለመሆኑንም ደጋግመው አሳስበዋል፡፡
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment