Wednesday, December 19, 2018

ሕዝብ በአገሩ ህልውና አይደራደርም!

(Dec 19, (Addis Ababa))--በአገሪቱ የተለያዩ አቅጣጫዎች የሚደመጡ ነገሮች ከተስፋ ይልቅ ለሥጋት እያደሉ ነው፡፡ ከመጠን በላይ ራስ ወዳድነት የተጠናወተውና አርቆ አሳቢነት የጎደለው የተወሰኑ ወገኖች ድርጊት ሕዝብን ሰላም እየነሳ ነው፡፡ የአገሩን ህልውና በምንም ነገር መደራደር የማይፈልገው ይህ የተከበረ ሕዝብ ሁሉንም ነገር በትዕግሥት እየታዘበ ነው፡፡ ከሰላምና መረጋጋት ይልቅ ስለአገር መፍረስና መበተን ብቻ በአንደበታቸው መርዝ የሚረጩ ወገኖች፣ ሥልጣንን ከሕዝብ ድምፅ ይልቅ በጠመንጃ ብቻ ለማግኘት የሚተጉ ቅብዝብዞች፣ ዛሬ የተናገሩትን ነገ የማይደግሙ ወላዋዮችና የዘመናት ቂምና ቁርሾ እየቀሰቀሱ አገር ለማጥፋት የተማማሉ እኩዮች ከመጠን በላይ ውጥረት እየፈጠሩ ናቸው፡፡

በተለያዩ አካባቢዎች ግጭት በመቀስቀስ የፌዴራል መንግሥቱንና የአገሪቱን የፀጥታ ኃይሎች ፋታ በማሳጣት አንፃራዊውን ሰላም እያደፈረሱ ያሉ ኃይሎች፣ የንፁኃን ደም እንዲፈስና የአገር አንጡራ ሀብት እንዲወድም እያደረጉ ነው፡፡ የአገር ጠላት ይመስል የሌሎች የከሸፈ አጀንዳ መሣሪያ በመሆን አገርን የጦር አውድማ ለማድረግ የሚተጉ ኃይሎች፣ በሕግ የበላይነት አደብ እንዲገዙ ካልተደረገ መጪው ጊዜ ያሳስባል፡፡ የአገሪቱን ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር አንቀሳቅሶ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት መነሳት ሲገባ፣ ተመልሶ የተለመደው አረንቋ ውስጥ ለመንቦጫረቅ የሚደረገውን አጉል ድርጊት ሕዝብ ተባብሮ ማስቆም አለበት፡፡

ኢትዮጵያን ዕድለ ቢስ አገር ናት ከሚያስብሉ ተጠቃሽ ምሳሌዎች መካከል አንዱ፣ በታሪክ አጋጣሚ ያገኘቻቸውን መልካም ዕድሎች መጠቀም አለመቻሏ ነው፡፡ ከመከኑት ዕድሎች አንደኛው ደግሞ እናውቃለን በሚሉ ልሂቃን ሳቢያ የተጨናገፈው የካቲት 1966 ዓ.ም. አብዮት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጣ ገንፍሎ የተቀጣጠለው ያ ሕዝባዊ አብዮት አቅጣጫውን ስቶ የወታደራዊ አምባገነንነት ሰለባ የሆነው፣ በወቅቱ የነበሩ ልሂቃን መስከን አቅቷቸው እርስ በርስ ስለተባሉ እንደነበር ታሪክ ይናገራል፣ መካድም አይቻልም፡፡

አሁንም ይህ ችግር በተለየ መንገድ ቀጥሎ ክልሎችን የግጭት መናኸሪያ በማድረግ በሰላምና በመረጋጋት ፋንታ አገር ማተራመስ በስፋት ተይዟል፡፡ ከመጠን ያለፈ ራስ ወዳድነት በተጠናወታቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ምክንያት የአገር ህልውና ለአደጋ እየተዳረገ ነው፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት የሚያስችል የፖለቲካ ሥነ ምኅዳር ለመፍጠር እጅ ለእጅ መያያዝ ሲገባ፣ አገሪቱን የግጭት አውድማ ለማድረግና ሕዝብን ሰቆቃ ውስጥ ለመክተት የሚደረገው አውዳሚ ጥረት አሳሳቢ ሆኗል፡፡ ሕዝብ እነዚህን ኃይሎች ስለሚያውቃቸው በፍጥነት የመግታት ኃላፊነት አለበት፡፡

አያያዛቸው የአገር ህልውና የሚያጠፋ ነውና፡፡ በርካታ ውስብስብ ችግሮች ባሉበት አገር ውስጥ ልዩነቶችን በሠለጠነ መንገድ እያስተናገዱ ለሰላማዊና ለዴሞክራሲያዊ ፉክክር ራስን ማዘጋጀት ሲቻል፣ በዘመናት ችግሮች ላይ ተጨማሪ ችግሮች እየቀፈቀፉ አገርን ማተራመስ የኋላቀርነት ትልቁ ማሳያ ነው፡፡ በሕዝብ መሀል መሠረታዊ ቅራኔ ሳይኖር እርስ በርሱ ማጋጨት፣ በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ መፈታት ያለበትን ጊዜያዊ ችግር የማይታረቅ ቅራኔ በማድረግ ግጭት መቀስቀስ፣ ትናንት አምባገነንነትን በሕይወት መስዋዕትነት የታገለውን ወጣት ትውልድ በማታለል ወይም በፕሮፓጋንዳ በመመረዝ ለጥፋት ማሰማራትና የአገርን ሰላም ማደፍረስ ከፀረ ሕዝብነት ውጪ ሌላ ስያሜ መስጠት ያዳግታል፡፡ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ከጠመንጃና ከጉልበት የፀዳ መሆኑ እየታወቀ ትጥቅ ሳይፈቱ መፈንጨት፣ ከሕዝብ ፍላጎት በተቃራኒ ሌላ የተደበቀ ዓላማ አለ ማለት ነው፡፡

የሰላማዊ ፖለቲካ የጨዋታ ሕግ ግን ይኼንን አይፈቅድም፡፡ በሐሰት የዓዞ እንባ እያነቡ ሕዝብን ጦርነት ውስጥ ለመማገድ መሞከርም የጊዜ ጉዳይ እንጂ ይጋለጣል፡፡ ለ21ኛው ክፍለ ዘመን በማይመጥን የዜሮ ድምር አስተሳሰብ ጠመንጃ አንግቶ መፎከር በሕዝብ ያስንቃል፡፡ ሕዝብም ይኼንን በአንክሮ መከታተልና ማጋለጥ ይኖርበታል፡፡ ማንም በላዩ ላይ መቀለድ የለበትም፡፡ በአገሩ ህልውና አይደራደርምና፡፡

ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በፍጥነት በጡረታ መገለል ያለባቸው ለዚህ ዘመን አስተሳሰብ የማይመጥኑ አሉ፡፡ እነዚህም በሁለት ይከፈላሉ፡፡ የመጀመሪያዎቹ ለረጅም ዓመታት ከስህተታቸው ሳይማሩ ባሉበት ረግተው የቆሙ ሲሆኑ፣ በስም የፖለቲከኝነት ካባ ከመደረብ ውጪ ፋይዳ ያለው አበርክቶ የላቸውም፡፡ ለዓመታት ባሉበት ሲረግጡ ከመኖር የዘለለ የረባ ውጤት ባለማስመዝገባቸው፣ አዲሱን ትውልድ ለመምራት የሚችሉበት ምንም ዕድል የላቸውም፡፡ በአጭሩ ይበቃቸዋል፡፡ ሁለተኞቹ ለዘመኑ አስተሳሰብ አለመመጠናቸው ብቻ ሳይሆን አደገኞች ናቸው፡፡ እነዚህኞቹ ‹‹ባልበላውም ጭሬ ልድፋው›› እንዳለችው ዶሮ፣ በተገኘው አጋጣሚ አገርን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከማተራመስ ወደ ኋላ አይሉም፡፡

እነሱ በወኪሎቻቸው አማካይነት በሚቀሰቅሱት ግጭት ንፁኃን ይገደላሉ፣ ለአካል ጉዳት ይዳረጋሉ፣ ከኖሩበት ቀዬ ይፈናቀላሉ፡፡ በተጨማሪም የአገር ሀብት ይወድማል፡፡ የእነሱ ፍላጎት ረግጦ መግዛት ስለሆነ ስለሰብዓዊና ዴሞክራሲ መብቶች ደንታ የላቸውም፡፡ እውነትን በማዛባትና በተጨባጭ የሚታይን በመካድ ሕዝብን ማሳሳት ወይም ማደናገር ልማዳቸው ስለሆነ፣ የእነሱ ዓላማ ይሳካ እንጂ ለአገር አይጨነቁም፡፡ ተፈጥሯቸውም አይደለም፡፡ በሴራና በአሻጥር ፖለቲካ ጥርሳቸውን ስለነቀሉ ለሕዝብም ለአገርም ደንታ የላቸውም፡፡ ሕዝብ የእነዚህ እኩዮች ሰለባ እንዳይሆን ነቅቶ በመጠበቅ ራሱን መከላከል አለበት፡፡ የእነዚህን ወኪሎችና ተላላኪዎች በማጋለጥ አገሩን መጠበቅ ግዴታው ሊሆን ይገባል፡፡ በአገሩ ህልውና ላይ መቀለድ ስለሌለባቸው፡፡  በአገሪቱ የተጀመረውን ለውጥ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሠረት ማድረግ የሚገባቸ

ው ልሂቃን ተብዬዎች ደግሞ፣ በሕዝብ ውስጥ ውዥንብር እየፈጠሩ ቀውስ እያባባሱ ነው፡፡ በተለይ በማኅበራዊ ሚዲያዎች ውስጥ በየዕለቱ በሚዋዥቅ አስተያየታቸውና ቅስቀሳቸው መንታ ሰብዕና የተላበሱ አክቲቪስት ተብዬዎች በአገር ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱ ነው፡፡ ለጋራ አገር የሚጠቅም ሐሳብ አፍላቂዎች መሆን ሲገባቸው፣ በተከመሩ ችግሮች ላይ ተጨማሪ እየፈበረኩ ሕዝብን ውዥንብር ውስጥ እየከተቱ ነው፡፡ በየቀኑ በየሥርቻው የሚፈለፈሉ ችግሮችን እያራገቡ መንግሥትንም ሆነ ለአገር በንፁህ ህሊና የሚሠሩ ሰዎችን የእግር እሳት እየሆኑባቸው ነው፡፡ መንግሥትን መተቸትና የበለጠ እንዲሠራ መጎትጎት ሲገባቸው የጎራ ፖለቲካ በመቀስቀስ አላሠራ ማለት ለአገር የማይጠቅም ከባድ በሽታ ነው፡፡ በሕዝብ ተቀባይነት ማግኘት የሚቻለው በዚህ መንገድ አይደለም፡፡ ለጊዜው ተሳክቶ ከሆነም አያዛልቅም፡፡

የሚያዛልቀው ይኼንን ምስኪን፣ ጨዋና አገሩን የሚወድ አስተዋይ ሕዝብ ሰላምና ዴሞክራሲ ማጎናፀፍ ነው፡፡ ሥልጣን በአቋራጭ ለማግኘት ወይም የተፅዕኖ አድማስን ለማስፋት የሚደረገው አጉል ርብርብ ጠልፎ ይጥላል፡፡ ለዚህም ይታበዩ የነበሩትን ዞር ዞር ብሎ ማየት ብቻ በቂ ነው፡፡ ሕዝብ ሁሉንም ነገር በቅርብ ርቀት ስለሚያውቅ መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ይህ አገሩን የሚወድ የተከበረ ሕዝብ በአገሩ ህልውና ከማንም ጋር አይደራደርም፡፡ ስለዚህ አገርን ውጥረት ውስጥ መክተት አያዋጣም፡፡ ከሕዝብ ጋር ያላትማልና፡፡ የተገኘውን መልካም ዕድል ማበላሸት አይገባም፡፡ ይልቁንም ይህንን መልካም ዕድል ሕዝብ ለሚፈልገው ዓላማ ማዋል ያስከብራል፡፡ ለዚህም ነው ሕዝብ በአገሩ ህልውና አይደራደርም የሚባለው!
ሪፖርተር (በጋዜጣዉ ሪፓርተር )

No comments:

Post a Comment