Saturday, December 08, 2018

የሚያዋጣው ለአገር ክብር በአንድነት መቆም ብቻ ነው!

(Dec 08, (Addis Ababa))--አገር ተከብራና ታፍራ ለዜጎቿ የምትመች መሆን የምትችለው ፍትሕ ሲሰፍን ነው፡፡ ፍትሕ በሌለበት ክብር የለም፣ አብሮነት አይታሰብም፣ ህልውናም ለአደጋ ይጋለጣል፡፡ ኢትዮጵያውያን በፍትሕ ዕጦት ምክንያት ማቀዋል፣ እንደ አውሬ ተሳደዋል፣ ሰፊ ለም መሬትና ተስማሚ የአየር ንብረት ይዘው የድህነት መጫወቻ ሆነዋል፣ የአምባገነኖች ሰለባም ተደርገዋል፡፡ በገዛ አገራቸው ባይተዋርነት እንዲሰማቸው ተደርገው በኃፍረት አንገታቸውን ደፍተዋል፡፡

የሕግ የበላይነት ተደርምሶ ጥቂቶች በአገርና በሕዝብ ላይ እየተጫወቱ ፍትሕ የጉልበተኞች ምርኮኛ ሆኗል፡፡ እንኳንስ በገዛ የአገር የጋራ ጉዳይ ተስማምቶ ለመወሰን፣ ዓይን ለዓይን መተያየት ባለመቻሉ ጥላቻና ቂም በቀል አገሪቱን እንደ ዓረም ወርሷታል፡፡

ይህንን አስከፊና አሳፋሪ የታሪክ ምዕራፍ በመዝጋት እንደ አዲስ መነሳት ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያውያንን የለያዩና አብረው እንዳይቆሙ ያደረጉ ከንቱ ድርጊቶችና አስተሳሰቦች ወደ ጎን ተደርገው፣ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ለመጀመር እጅ ለእጅ መያያዝ ያስፈልጋል፡፡ የአገር ክብርና ዝና የሚታደሰው በዚህ መንገድ ብቻ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን ባስተላለፉት መልዕክት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ የፍትሕ ጥያቄ ሲያቀርብ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

በአንድ አገር ውስጥ የመንግሥት መኖርን ግዴታ ከሚያደርጉት መሠረታዊ ምክንያቶች መካከል አንዱ፣ ፍትሕ ማረጋገጥ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ ፍትሕ የሚረጋገጠው ደግሞ ንፁኃን በኩራት ቀና ብለው የሚሄዱበት፣ ወንጀለኞች ደግሞ የትም የማይደበቁበት ሥርዓት መፍጠር ሲቻል ነው ብለዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ ንፁኃን ዜጎች እንጂ ወንጀለኞች በኩራት የሚኖሩባት አገር መሆን የለባትም፤›› በማለት ወንጀል የፈጸሙ እንዲቀጡ፣ ሊፈጽሙ ያሰቡ እንዲጠነቀቁ፣ እነሱን ሊከተሉ የሚከጅሉ እንዲማሩ ብለው ወንጀለኞችን የማደንና ለሕግ የማቅረብ ሒደት ይቀጥላል እንጂ አልተፈጸመም ሲሉ አክለዋል፡፡ በአራቱም ማዕዘናት አገሪቱን ከወንጀለኞች ነፃ የማድረግ ዓላማ መያዙንም አስታውቀዋል፡፡ ይህ ውሳኔ የሕግ የበላይነትን በማስከበር የአገር ክብርን ለማስጠበቅ ትልቅ አንድምታ ስላለው፣ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ድጋፍ ሊቸሩት ይገባል፡፡

ኢትዮጵያውያን በዚህ ታሪካዊ ወቅት በሚገባ መገንዘብ ያለባቸው ከግል ጥቅምና ዝና በላይ አገር የምትባል የጋራ ቤት መኖሯን ነው፡፡ በወንጀል የተጠረጠረ ማንም ሰው ፍትሕ ፊት መቅረብ ይኖርበታል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱ ነፃነት ተጠብቆ ራሱን የመከላከል ኃላፊነት ያለበት ተጠርጣሪው ብቻ ነው፡፡

ከዚያ ውጪ በብሔር፣ በእምነት፣ በልዩ ግንኙነቶችና በመሳሰሉት እያመካኙ አላስፈላጊ ድርጊት ውስጥ መግባት የሕግ የበላይነትን መጋፋት ነው፡፡ እንደተባለው ወንጀል ብሔር፣ ፆታ፣ ሃይማኖት ወይም ሌላ ማንነት የለውም፡፡ ወንጀል በተፈጥሮው ግለሰባዊ የሞራል ዝቅጠት መገለጫ እንጂ ማኅበራዊ መሠረት የለውም፡፡ ይልቁንም ማንኛውም ተጠርጣሪ ተገቢውን ፍትሕ እንዲያገኝ፣ የዳኝነትና የፍትሕ ሥርዓቱ ነፃነት እንዲረጋገጥ መትጋት ይሻላል፡፡

ይህ የሕግ የበላይነት እንዲኖር ከማገዙም በላይ፣ ሕገወጥነት እንዲወገድ ራሱን የቻለ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል፡፡ አገር የራባት ፍትሕ ነው፣ ሕዝብ የተጠማው ፍትሕ ነው፡፡ ፍትሕ ሲኖር ዝርፊያና እርኩሰት የተሞላባቸው ድርጊቶች ሥፍራ አይኖራቸውም፡፡ እነዚህ ሰይጣናዊ ድርጊቶች ሲወገዱ አገር ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲ ይንሰራፋባታል፡፡ ክብሯ ተጠብቆ ከትውልድ ወደ ትውልድ ትሸጋገራለች፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ በሕዝቡ አርቆ አሳቢነትና አስተዋይነት ምክንያት እንጂ፣ ይፈጸሙ እንደነበሩት አስነዋሪ ድርጊቶች ለማሰብ የሚያዳግቱ ጥፋቶች ይደርሱ ነበር፡፡ ይህ አገሩን ከምንም ነገር በላይ የሚወድ አስተዋይ ሕዝብ እርስ በርሱ የጋራ እሴቶቹንና መስተጋብሮቹን በመጠበቅ ሚዛናዊነት ማሳየቱ ትልቅ ግምት የሚሰጠው ነው፡፡ በየጊዜው የተፈራረቁ አምባገነኖች ያደረሱዋቸው በደሎችና ግፎች ተችለው እዚህ የተደረሰው በዚህ ጨዋና የተከበረ ሕዝብ ምክንያት ነው፡፡ ይህ የተከበረ ሕዝብ ባለፉት ዓመታት የተፈጸሙ ግፎችንና በደሎችን ታግሶ እዚህ ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡

ካሁን በኋላ በኢትዮጵያ ምድር በአራቱም ማዕዘናት ፍትሕ እንዲሰፍን እጅ ለእጅ እንያያዝ ሲባል፣ እነዚያ የመከራ ዘመናት ተመልሰው እንዳይመጡ በአንድነት ለመቆም ነው፡፡ ካሁን በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ በሥልጣን መባለግ ማክተም እንዲኖርበት በአንድነት መቆም ተገቢ ነው፡፡ የሥነ ምግባር ዝቅጠት በተንሰራፋበት ትውልድ ይላሽቃል እንጂ፣ ዕድገት በፍፁም አይታሰብም፡፡ የዛሬ ተሿሚዎች ከትናንቱ ከንቱ ድርጊት መማር አለባቸው፡፡ ትናንት አገሪቱን ያቆሸሹ አሳፋሪ ድርጊቶች እንዲገቱ ብቻ ሳይሆን፣ ዳግም እንዳያንሰራሩ አከርካሪያቸውን መስበር ይገባል፡፡ ይህንን ማድረግ ሲቻል አገር የቀደመ ክብሯ ይመለሳል፡፡ ልጆቿም በኩራት አንገታቸውን ቀና ያደርጋሉ፡፡

አሁን ጊዜው የመበቃቀልና በሴረኝነት የመፈላለግ ሳይሆን፣ በእኩልነትና በፍትሐዊነት የሚኖርበት ሥርዓት ለመፍጠር በጋራ መረባረቢያ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን በብሔር፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ አመለካከትና በመሳሰሉት ከእነ ልዩነቶቻቸው ለጋራ አገራቸው አንድ ላይ መቆም ከቻሉ፣ ኢትዮጵያ እንኳን ለእነሱ ለተቀሩት አፍሪካውያን ወንድሞችና እህቶች ትተርፋለች፡፡ በኢትዮጵያ ምድር የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና አስደንጋጭ ዝርፊያዎች ዳግም እንዳይከሰቱና ጠንካራ ተቋማት እንዲገነቡ በጋራ መሥራት፣ እንዲሁም ልዩነቶችን በዴሞክራሲያዊ መንገድ እያስተናገዱ ለአገር የጋራ ጥቅምና ደኅንነት በአንድነት መቆም ይቻላል፡፡

ከግላዊና ከቡድናዊ ጥቅሞች በላይ አገሩን በታላቅ ፍቅር የሚወድ ጀግና ሕዝብ ስላለ፣ ፖለቲከኞችም ሆኑ የአገር ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ወገኖች በሙሉ አገርን ማስቀደም ይኖርባቸዋል፡፡ አገር የዴሞክራሲና የፍትሕ አምባ እንድትሆን ተግቶ መሥራት ይገባል፡፡ ሕዝብ ከምንም ነገር በላይ የሚያሳስበው የአገሩ ህልውና ስለሆነ፣ የሚያዋጣው ለአገር ክብር በአንድነት መቆም ብቻ ነው!
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment