Saturday, December 08, 2018

የሜቴክ የቀድሞ ዋና ዳይሬክተር የተጠረጠሩባቸው ሕገወጥ ግዥዎች ይፋ ተደረጉ

(Dec 08, (Addis Ababa))--የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) የቀድሞ ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል ክንፈ ዳኘው ሕገወጥ ግዥ እንዲፈጸም ትዕዛዝ በመስጠት፣ በመንግሥት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ አድርገዋል ተብለው የተጠረጠሩባቸው ግዥዎች ተለይተው ለፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡

እሳቸው የስምንት ሚሊዮን ዩሮ ውል ፈጽመውበታል የተባለው ከተረፈ ምርቶች የናፍጣ ነዳጅ ማምረቻ ፋብሪካ ግዥ፣ የ9.5 ሚሊዮን ዩሮ ውል የፈጸሙበት አሥር ያገለገሉ አውሮፕላኖች ግዥ፣ በ12.7 ሚሊዮን ብር ከጌትፋም ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ባለሦስት ፎቅ ሕንፃ ግዥ፣ በ195 ሚሊዮን ብር ከአቶ ዓለም ፍፁም የገዙት ሪቬራ ሆቴልና ፕላስቲክ ፋብሪካ፣ በ72 ሚሊዮን ብር የተገዛው ኢምፔሪያል ሆቴል (አሞራ ሕንፃ) ይገኙበታል፡፡

በተጨማሪም 347.9 ሚሊዮን ዶላር ውል የፈጸሙበት ከቆሻሻ የጄት ነዳጅ ማምረቻ ፋብሪካ ግንባታ፣ ከሁለት ቢሊዮን ብር በላይ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ተቀብለውበታል የተባለው የታላቁ ህዳሴ ግድብ የጫካ ምንጣሮ ሥራ፣ ለፍፁም የሺጥላ፣ ለአቶ ተስፋሁን ሰብስቤና ለአቶ ዝናህብዙ ፀጋዬ በስፖንሰር መልክ ሰጥተዋል የተባለው ከ30 ሺሕ በላይ ዶላርና ከ954 ሺሕ ብር በላይ፣ በመንግሥት ላይ ከ544 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት ያደረሱ ሁለት ያረጁ መርከቦች ግዥ፣ የ10.6 ሚሊዮን ዶላር ዓለም አቀፍ ግዥዎች፣ የ660 ሺሕ ዶላር የአገልግሎት ግዥ፣ ያለ ጨረታ የተፈጸመ የአንድ ቢሊዮን ዶላር ግዥ፣ የ4.5 ሚሊዮን ዩሮ ያገለገሉ ክሬኖች ግዥና የ6.4 ሚሊዮን ዩሮ ከውጭ ኩባንያ የተፈጸመ ግዥ መሆናቸው ተዘርዝሮ ቀርቧል፡፡

ሜጄር ጄኔራል ክንፈ የተጠረጠሩበትን ሥልጣንን ያላግባብ መጠቀም ከፍተኛ የሙስና ወንጀል፣ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን በዝርዝር ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አሥረኛ ወንጀል ችሎት አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱ መርማሪ ቡድኑ ያቀረበው ዝርዝር ማስረጃ ማለትም ከላይ የተጠቀሱትን ድርጊቶች መሠረት አድርጎ በተሰጠው 14 ቀናት ውስጥ የሠራውንና የቀረውን በዝርዝር ገልጾ፣ ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት የጠየቀበትን ለተጠርጣሪዎቹ እንዲደርስ አድርጓል፡፡

በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ ‹‹መርማሪም ቡድኑ ያቀረበውን ዝርዝር ሐሳብ እዩና ምላሻችሁን በጽሑፍ በአዳር አቅርቡ›› ሲል፣ የተጠርጣሪዎች ጠበቃ ተቃውሞአቸውን አሰምተዋል፡፡ በወንጀል ሕጉም ሆነ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕጉ የጊዜ ቀጠሮ ክርክር በግልጽ ችሎት በቃል እንዲከራከሩ ከማዘዝ ውጪ በሕግ አስገዳጅ ሆኖ በጽሑፍ እንዲቀርብ የተደነገገበት የሕግ ድጋፍ እንደሌለ ጠበቃው ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም መርማሪ ቡድኑ የሠራውንና የቀረውን ለችሎቱ ገልጾ ምላሽ እንዲሰጡ እንዲታዘዝላቸው ጠይቀዋል፡፡ ክርክሩ እየተደረገ ያለው በግልጽ ችሎት በመሆኑና ተጠርጣሪዎችም መስማት ስላለባቸው በችሎት እንዲከራከሩ ጠበቃው ደግመው ጠይቀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም በሰጠው ምላሽ በጽሑፍ ምላሽ እንዲሰጥ በሕግ አለመፈቀዱንና አለመከልከሉን፣ የችሎት ሰዓት በመጠናቀቁና ከሰዓት ውጪ አከራክሩ የሚል አስገዳጅ የሕግ ድንጋጌ እንደሌለ በመግለጽ ከፈለጉ በጽሑፍ ወይም በቃል በአዳር ማቅረብ እንደሚችሉ አስረድቷል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ከጠበቃቸው ጋር ከተመካከሩ በኋላ መርማሪ ቡድኑ ያቀረበው ዝርዝር ሐሳብ ሰፊ መሆኑን ጠቁመው፣ ምላሻቸውን በጽሑፍ ለማቅረብ ለረቡዕ ኅዳር 26 ቀን 2011 ዓ.ም. እንዲሆንላቸው ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱም ተስማምቷል፡፡

ሌላው ተጠርጣሪ ሰኞ ኅዳር 24 ቀን 2011 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው የነበሩት ሌተና ኮሎኔል ሰጠኝ ካህሳይ ሲሆኑ፣ ከተጠረጠሩበት የብርጋዴር ጄኔራል ሀድጉ ገብረ እግዚአብሔር ጸሐፊ ሰነድ እንድታሸሽ ማድረግና ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ማከማቸት የሙስና ወንጀል ውጪ በሌላ የወንጀል ድርጊት መጠርጠራቸውን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል፡፡

መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳው ሌተና ኮሎኔል ሰጠኝ ኤራ የሚባል ፀረ ታንክ መሣሪያ ግዥ ውስጥ በመሳተፍ የ15,783,750 ብር ግዥ እንዲፈጸም በማድረግ፣ በመንግሥት ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጉዳት እንዲደርስ ማድረጋቸውን ገልጿል፡፡ በመሆኑም ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡ ተጠርጣሪው በተከላካይ ጠበቆች አማካይነት ባደረጉት ክርክር፣ መርማሪ ቡድኑ ባልተከራከሩበት ጉዳይ ተጨማሪ ጊዜ መጠየቅ እንደማይቻል ገልጸው ክርክሩ ውድቅ ተደርጎ ዋስትናቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡

መርማሪ ቡድኑ በበኩሉ ምርመራው እየሰፋና ጥቆማ እየመጣ መሆኑን ጠቁሞ፣ ወደ ሌላም አቅጣጫ ሊወስደው እንደሚችል በመግለጽ የተጠርጣሪ ጠበቆች ክርክር ተገቢ ያልሆነ ነው ብሏል፡፡ ዋስትናውንም ተቃውሟል፡፡ የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው ፍርድ ቤትም መርምሮ ብይን ለመስጠት በአዳር ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

የዓለም ገነት ቆርቆሮ ፋብሪካ ባለቤትና የሪቬራ ሆቴልና የፕላስቲክ ፋብሪካ ባለቤት የነበሩት አቶ ዓለም ፍፁም ላይ፣ መርማሪ ቡድኑ የሠራውን ምርመራ አስረድቷል፡፡ የተለያዩ ሰነዶችን መሰብሰቡንና የአምስት ምስክሮችን ቃል መቀበሉን ገልጿል፡፡ በመንግሥት ላይ የደረሰውን ጉዳት በልዩ ባለሙያዎች ማስላትና ኦዲት ማድረግ እንደሚቀረው በመግለጽ፣ ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ ፖሊስ ከጠየቀው 14 ቀናት ውስጥ ስምንት ቀናት በመፍቀድ ለታኅሳስ 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ሪፖርተር (ታምሩ ጽጌ )

No comments:

Post a Comment