Friday, October 05, 2018

ዶ/ር አብይ አህመድ የኢህአዴግ ሊቀመንበር አቶ ደመቀ መኮንን ም/ሊቀመንበር ሆነው በድጋሚ ተመረጡ

(አዲስ አበባ፣ መስከረም 25፣ 2011 (ኤፍ.ቢ.ሲ))--ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በሃዋሳ ሲካሄድ የቆየው የኢህአዴግ 11ኛው ድርጅታዊ ጉባኤው ዛሬ በማጠናቀቂያ ቀኑ የግንባሩን ሊቀመንበር እና ምክትል ሊቀመንበር ምርጫ አድርጓል።

በዚህም መሰረት ዶክተር አብይ አህመድ የግንባሩ ሊቀመንበር አቶ ደመቀ መኮንን ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር በመሆን በድጋሚ ተመርጠዋል ዛሬ በተካሄደው ምርጫ 177 ሰዎች ድምጽ የሰጡ ሲሆን ዶክተር አብይ 176 ድምጽ በማግኘት ሊቀ መንበር በመሆን ተመርጠዋል።

ለምክትልነት በተሰጠው ድምጽ ደግሞ አቶ ደመቀ መኮንን 149 ድምጽ በማግኘት ምክትል ሊቀ መንበር ሆነው በድጋሚ ተመርጠዋል። ባለፈው መጋቢት ወር ላይ ጉባኤውን አድርጎ የነበረው የኢህአዴግ ምክር ቤት ቀደም ብሎ በፈቃዳቸው ስልጣናቸውን በለቀቁት የቀድሞው የግንባሩ ሊቀመንበር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝን ለመተካት ባደረገው ምርጫ ነበር ዶክተር አብይ አህመድ ለመጀመሪያ ጊዜ በግንባሩ ሊቀመንበርነት የተመረጡት።

ለቀናት ድርጅታዊ ጉባኤውን ሲያካሂድ የቆየው ግንባሩ በህገ ደንቡ መሰረት በድርጅታዊ ጉባኤው ሊቀመንበሩን እና ምክትል ሊቀመንበሩን እንደሚመርጥ ማስቀመጡን ተከትሎ ነው ዛሬ ምርጫ በማድረግ ዶክተር አብይ አህመድን በሊቀመንበርነት አቶ ደመቀ መኮንን ደግሞ በምክትል ሊቀመንበርነት የመረጣቸው።
ኤፍ.ቢ.ሲ

No comments:

Post a Comment