Thursday, March 29, 2012

ሰበር ዜና:- ጥቃት የተፈጸመባትን ሕፃን ጉዳይ ፖሊስ እያጣራሁ ነው አለ

(Thursday, 29 March 2012)--ሰሞኑን በአሰቃቂ ሁኔታ ድብደባ ሲፈጸምባት በፌስቡክ ላይ በተለቀቀ ቪዲዮ የምትታየውን ሕፃን ጉዳይ ፖሊስ እየመረመርኩት ነው አለ፡፡

በመነን አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ረዳት ሳጅን አሸናፊ ክፍሌ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ጉዳዩ ለጣቢያቸው ከትናንት በስቲያ ሪፖርት ከተደረገላቸው ጀምሮ እየተከታተሉት ነው፡፡

‹‹አሁን ያለነው ማስረጃ በማሰባሰብ ሥራ ላይ ነው፡፡ ስለዚህም ጉዳዩን እየመረመርነው ነው፡፡ በመቀጠልም ጉዳዩን ለጉለሌ ፖሊስ መምሪያ ሕፃናትና እንክብካቤ ዛሬ እንመራዋለን፤›› ብለዋል፡፡ ረዳት ሳጅኑ አስፈላጊው ምርመራ ከተደረገ በኋላ የወንጀሉ ተጠርጣሪዎች በሕግ እንደሚጠየቁ ገልጸዋል፡፡

ሪፖርተር ዛሬ በአካባቢው ሄዶ ወ/ሮ ሐሊማት መሐመድንና ወጣት ሜሮን አስናቀን ለማግኘት ቢሞክርም ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡ ሆኖም ከአካባቢው ሰዎች ለመረዳት እንደተቻለው ወ/ሮ ሐሊማት መሐመድ የሕፃኗ አያት ሲሆኑ፣ በቪዲዮ ላይ እንደሚሰማው የሰፈሩ ሰዎች ‹‹ዓለም›› እያሉ ነው የሚጠራቸው፡፡ ወ/ሮ ሐሊማት (ዓለም) በአዲስ አበባ አስተዳደር የፅዳት ሠራተኛ ሲሆኑ፣ ልጃቸው (የሕፃኗ እናት) ዓረብ አገር በመሄዷ ሕፃኗን በአደራ ሲያሳድጉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

 አሁን ግን ተመልሳ እዚህ እንደምትኖር ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአካባቢው ሰዎች ድርጊቱ የተፈጸመው የዛሬ ሦስት ዓመት አካባቢ ነው የተባለው ትክክል እንዳልሆነና ምናልባትም ቢበዛ አንድ ዓመት ብቻ እንደሚሆነው ገልጸዋል፡፡

እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት ወ/ሮ ሐሊማትም ሆኑ ሜሮን በቁጥጥር ሥር አልዋሉም፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment