Thursday, March 08, 2012

በአዲስ አበባ አዲስ የአድራሻ ሥርዓት ትግበራ ተጀመረ

(ቀን 2012-03-08, አዲስ አበባ)--አዲሱ የአዲስ አበባ ከተማ የአድራሻ ሥርዓት ተግባራዊ መሆን መጀመሩን የአስተዳደሩ የተቀናጀ የመሬት መረጃ አያያዝ ሥርዓት መዘርጊያ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።

የጽሕፈት ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘሪሁን አምደማርያም ትናንት ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፤ አሁን ያለውንና የተዘበራረቀውን የከተማዋን የአድራሻ ሥርዓት ወቅታዊና ዘመናዊ የሚያደርግ አዲስ የተቀናጀ የዲዛይን ጥናት ተጠናቆ ወደ ትግበራ ተገብቷል።

እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለፃ በ1988 ዓ.ም የተዘጋጀው የከተማዋ ማስተር ፕላን አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር ተመጣጣኝ አይደለም። የመረጃ ሥርዓቱ የተቀናጀ ባለመሆኑ ለነዋሪው ፈጣንና ወቅታዊ አገልግሎት ለመስጠት አስቸጋሪ አድርጎታል። በዚህ ረገድ በ2003 ዓ.ም የተሠራውን የአየር ካርታ መሠረት በማድረግ አስተዳደሩ የአድራሻ ሥርዓቱን በውጭ አማካሪ ድርጅቶች አስጠንቶ ወደ ትግበራ ገብቷል።

አስተዳደሩ ጥናቱን ተግባራዊ ማድረግ ያስችሉት ዘንድ 33 ባለሙያዎችን አሰልጥኖ ወደ ሥራ ማሠማራቱን የሚገልጹት አቶ ዘሪሁን በአሁኑ ወቅትም በተመረጡ ሁለት ወረዳዎች ላይ የሙከራ ሥራ መጀመሩን አስረድተዋል።
ከተመረጡት ሁለት ወረዳዎች ላይ ውጤቱ ከተፈተሸ በኋላ ወደ ሌሎች ወረዳዎች የማስፋፋት ሥራ የሚከናወን መሆኑን አመልክተዋል።

በዚሁ መሠረት በአሁኑ ወቅት በተመረጡት በንፋስ ስልክ በወረዳ 03 እና በቦሌ ወረዳ 10 ላይ የስያሜ መስጫ ሰሌዳ እየተተከለ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በሰሌዳው ላይ የመንገድ ስያሜን መንገዱ የሚገኝበት ክፍለ ከተማና ወረዳ፣ በመንገዱ ግራና ቀኝ የሚገኙ ብሎኮች ቁጥር፣ የቤቶች ቁጥርና የመሳሰሉት ዝርዝር ማብራሪያዎች ማካተቱንም አብራርተዋል።

ከዚሁ ጐን ለጐንም አዲስ የቤት ቁጥር የሚሰጥ መሆኑን አቶ ዘሪሁን አመልክተው ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ማድረግ ከተቻለም በመረጃ ሥርዓቱ ላይ ያለውን የግልፅ ጥናትና ተጠያቂነት ችግር እንደ ሚፈታው አስገንዝበዋል። «ለነዋሪውም ሆነ ለአስተዳደሩ በአንድ ቦታ በቀላሉ መረጃ እንዲያገኙ ከማስቻሉም ባሻገር አገልግሎቱን ለማሳላት ከፍተኛ ድርሻ ይኖረዋል ነው» ብለዋል።

በተጨማሪም የእሳት አደጋና የአምቡላንስ አገልግሎትን የአድራሻ ሥርዓቱን በመጠቀም በፍጥነት ማግኘት እንደሚያስችል አስረድተዋል። በመንግሥትም ሆነ በግሉ ዘርፍ የሚሰጡ አገልግሎቶችን እቤት ድረስ ማግኘት የሚቻልበት ሁኔታ ይፈጠራል ብለዋል።

በመሆኑም ሕብረተሰቡ ጥቅሙ የራሱ መሆኑን ተገንዝቦ የሚተከሉትን ሰሌዳዎች እንዲንከባከብ ጠይቀዋል።
የአድራሻ ሥርዓቱ በአራት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ እንደሚተገበር አቶ ዘሪሁን ተናግረው ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ ይፈጃል ተብሎ እንደተገመተም አስታውቀዋል።
Source: Ethiopian Press Agency

No comments:

Post a Comment