Wednesday, July 24, 2019

አገር የጉልበተኞች መጫወቻ አትሁን!

(July 24(ሪፖርተር))--በደቡብ ክልል ሲዳማ ዞን ውስጥ ሰሞኑን የተፈጸሙ ግድያዎች፣ ማፈናቀሎች፣ ዘረፋዎችና ውድመቶች በግልጽ የሚያመላክቱት ጉልበተኞች አጋጣሚውን ካገኙ አገር እንደሚያፈርሱ ነው፡፡ ከሲዳማ ዞን የወጡ የተለያዩ ምሥሎችና መረጃዎች ልብ ሰባሪ ከመሆናቸው በተጨማሪ፣ ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖች ያሳለፏቸውን የመከራና የሰቆቃ ቀናት ቁልጭ አድርገው ያሳያሉ፡፡

በሕጋዊ መንገድ መቅረብ የነበረበት ጥያቄ በሕጋዊ መንገድ ምላሽ እንደሚያገኝ በግልጽ እየታወቀ፣ የተፈለገው ግን ኢትዮጵያውያን በታሪካቸው ከሚታወቁበት ጨዋነት በተቃራኒ የሕገወጥነትና የውድመት ጎዳና ነው፡፡ የሕጋዊነትንና የሕገወጥነትን መፈክሮች በግራና በቀኝ እጆቻቸው አንግበው የተነሱ ጉልበተኞች፣ አጋጣሚውን በመጠቀም ንፁኃን ኢትዮጵያውያንን በመግደል ንብረታቸውን አውድመዋል፡፡

ከእነሱ ወገን ያልተወለዱ ንፁኃንን በቀጥታ ዒላማ ያደረጉ ጉልበተኞች የበርካቶችን ሕይወት አጥፍተው፣ በርካቶችን ያለ መጠለያ ሜዳ ላይ ጥለዋል፡፡ ይህንን ዓይነቱን ነውረኛ ድርጊት የፈጸሙም ሆኑ የመሩ በሕግ የእጃቸውን እንዲያገኙ መደረግ አለበት፡፡ አገር የጉልበተኞች መጫወቻ ስትሆን ሥርዓተ አልበኝነት ይነግሣል፡፡ የዜጎች በሰላም የመኖርና የመሥራት መብት አደጋ ውስጥ ይገባል፡፡ የአገር ህልውና ወደ መጨረሻው ጠርዝ ይገፋል፡፡ ኢትዮጵያውያን አገራቸው የጉልበተኞች መጫወቻ እንዳትሆን በአንድነት መቆም አለባቸው፡፡

ለአገራቸው ከፍተኛ የሆነ ፍቅርና አክብሮት ያላቸው ሀቀኛ ኢትዮጵያውያን እንዳሉ ሁሉ፣ ምንም ፋይዳ የሌላቸው ከንቱዎችም አሉ፡፡ የኢትዮጵያዊነት ስም ሲነሳ የሚነዝራቸውና እኔ ለአገሬ የሚሉ ያሉትን ያህል፣ ከኢትዮጵያዊነት ጋር የተጣላ ሰብዕና የገነቡ አሉ፡፡

እነዚህ ለኢትዮጵያ ዕድገትና ብልፅግና አንዳችም አስተዋጽኦ ለማበርከት የማይፈልጉ ከንቱዎች፣ ሰላሟንና ደኅንነቷን ለመበጥበጥ ግን የሚቀድማቸው የለም፡፡ ችግር ሲፈጠር መፍትሔ ከመፈለግ ይልቅ፣ ሥቃይዋን ለማብዛት መርዝ ይበጠብጣሉ፡፡ በነጋ በጠባ ችግር እየፈበረኩ መተንፈሻ ያሳጧታል፡፡ ለግል ክብር፣ ዝና፣ ሥልጣንና ጥቅም ብቻ የሚቋምጡ መሰሪዎች ስለሆኑ፣ ለሕዝቡ ታሪካዊ እሴቶችና መስተጋብሮች ደንታ የላቸውም፡፡ በሰላም አብረው በመኖር ክፉና ደግ ዘመናትን አብረው ያሳለፉ ኢትዮጵያውያንን በብሔር፣ በእምነት፣ በባህልና በመሳሰሉት ልዩነቶች እየከፋፈሉ ያጋጫሉ፡፡

ግጭት በተነሳባቸው የተለያዩ ሥፍራዎች ሁሉ ማኅበረሰቡ እርስ በርስ ከለላ እየተሰጣጠ የአደጋዎችን መጠን ይቀንሳል እንጂ፣ እንደ ሕገወጦቹ ቢሆን ኖሮ ለማመን የሚከብዱ ዕልቂቶችና ውድመቶች ያጋጥሙ ነበር፡፡ አሁንም መታሰብ ያለበት ሕገወጦችና ጉልበተኞች አደብ እንዲገዙ ካልተደረገ፣ ኢትዮጵያን ዓይታው የማታውቀው ቀውስ ውስጥ የሚከቱ ግጭቶች ወደፊት ላለመከሰታቸው ምንም ዓይነት ማረጋገጫ የለም፡፡

የሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄ በሕጋዊ መንገድ ከቀረበ በኋላ በማስከተል የጉልበት ማስፈራሪያ ሲታከልበት፣ የፌዴራል መንግሥትም ሆነ የክልሉ መንግሥት በወቅቱ ተገቢውን ዕርምጃ መውሰድ ነበረባቸው፡፡ ይህ ባለመሆኑ ግን በጣም ዘግናኝ የሆኑ ነውረኛ ድርጊቶች ተፈጽመው፣ ለበርካታ ንፁኃን ሕይወት መጥፋትና ንብረት መውደም ምክንያት ሆኗል፡፡ ከሰኞ ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ የደቡብ ክልል ሁሉም ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ቀበሌዎችና ከተሞች ጭምር የፀጥታ ሥራቸው በፌዴራል ኮማንድ ፖስት ሥር እንዲሆን ተወስኗል፡፡ እዚህ ውሳኔ ላይ የተደረሰው ከፍተኛ ጥፋት ከደረሰ በኋላ ነው፡፡ ለማንም ጤነኛ ሰው በኮማንድ ፖስትም ሆነ በአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታ ውስጥ መኖር ከባድ ነው፡፡

ነገር ግን ከአገርና ከሕዝብ ህልውና የሚበልጥ ስለሌለና ጉልበተኞችም ሕግ ፊት መቅረብ ስላለባቸው፣ እየመረረም ቢሆን ሀቁን መቀበል የግድ ይሆናል፡፡ ሕገወጥነትን የዓላማ ማስፈጸሚያ በማድረግ በኢትዮጵያውያን ላይ ዘግናኝ የሆነ ጥቃት የሚፈጽሙ ኃይሎች፣ በአገሪቱ ሕግ እንዳለ ሊያውቁ ይገባል፡፡ ኮማንድ ፖስቱ የደቡብ ክልልን የፀጥታ ሥራ መምራት ብቻ ሳይሆን፣ በንፁኃን ኢትዮጵያውያን ላይ ግድያና የንብረት ውድመት ያደረሱትን ሕግ ፊት ማቅረብ አለበት፡፡ ይህም ዕርምጃ አመራር ሰጪ የሆኑትን እንደሚጨምር ግንዛቤ ሊኖር ይገባል፡፡ አገር በሕገወጦችና በጉልበተኞች መታመስ የለባትም፡፡

በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የመንግሥት መደበኛ መዋቅሮችንና የፀጥታ ኃይሎችን ወደ ጎን በመግፋት፣ መደበኛ ባልሆኑ አደረጃጀቶች የሚፈጸሙ ውንብድናዎች መቆም አለባቸው፡፡ መንግሥት የሚዳከመው መዋቅሮቹ በአግባቡ መሥራት ሳይችሉ ሲቀሩ ነው፡፡ ግጭት ባጋጠመባቸው የአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የፀጥታ አስከባሪዎችና  ፖሊሶች እንዳላዩ ሲሆኑ፣ ወይም የተገኙበትን ብሔር ወግነው ጥቃት ሲፈጽሙ እንደነበር ከበርካታ የጥቃት ሰለባዎች አንደበት በግልጽ ተሰምቷል፡፡ የዞንና የወረዳ አስተዳዳሪዎች ወገንተኝነት ያሳዩ እንደነበርም በተደጋጋሚ ተተርኳል፡፡

የመንግሥት የአስተዳደርና የፀጥታ መዋቅሮች በጉልበተኞች ቁጥጥር ሥር ሲውሉ፣ ጥቃት የሚደርስባቸው ንፁኃን ዜጎች የሚከላከላቸው አያገኙም፡፡ ማኅበረሰቡ እርስ በርስ ለመረዳዳት በጋራ ቢነሳ እንኳ የጉልበተኞች የጥቃት ሰለባ ይሆናል፡፡ አሁንም ጊዜው አልረፈደምና ጉልበተኞች በሕግ አምላክ መባል አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያውያንን በዘር፣ በሃይማኖት፣ በባህልና በመሳሰሉት እየከፋፈሉ አገሪቱን የሚያተራምሱ ሕግ መኖሩን ማወቅ አለባቸው፡፡ ለሕዝብ አንዳችም ፋይዳ የሌላቸው ሕገወጦችና ጉልበተኞች የአገሪቱን መፃኢ ዕድል አያበላሹ፡፡ ሊበቃቸው ይገባል፡፡

ሕግ በማይከበርበት አገር የዜጎች ሰላምና ደኅንነት አይጠበቅም፡፡ በሰላም ወጥቶ መግባት ይቸግራል፡፡ ተዘዋውሮ መሥራት በፍፁም አይታሰብም፡፡ ሕገወጦች የበላይነቱን ሲይዙ የጉልበት መንገድ ተመራጭ እየሆነ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ይደፈጠጣሉ፡፡ እንኳንስ ስለአገር ዕድገትና ብልፅግና ለማሰብ የህልውና ሥጋት ይቀድማል፡፡ ጉልበተኞች የሕዝቡን ሥነ ልቦና በዚህ መንገድ ከሰለቡ በኋላ የሚፈልጉትን ዓላማ ያሳካሉ፡፡ እየሆነ ያለውም ይኸው ነው፡፡

ኢትዮጵያ ከአምባገነናዊ ሥርዓት ወደ ዴሞክራሲ እንድትሸጋገር የሚፈለግ ከሆነ፣ የፖለቲካው ምኅዳር ከጉልበተኞችና ከሕገወጦች መፅዳት አለበት፡፡ የሰላምን ዋጋ ለማወቅ የግድ በግጭት ውስጥ ማለፍ እንደማያስፈልግ ሁሉ፣ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመሸጋገር በጉልበተኞች መረገጥ አይገባም፡፡ ኢትዮጵያ የጉልበተኞች ቤተ ሙከራ መሆን የለባትም፡፡ ንፁኃን በጉልበተኞችና በተላላኪዎቻቸው መሰቃየት የለባቸውም፡፡ ሕጋዊነትንና ሕገወጥነትን እያጣቀሱ በሕዝብ ስም የሚነግዱ ወረበሎች ለአገር ፋይዳ ስለሌላቸው፣ በኢትዮጵያ ምድር የሕግ የበላይነት እንዳለ ማሳያው አሁን መሆን አለበት፡፡ አገር የጉልበተኞች መጫወቻ አትሁን!
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment