Tuesday, July 30, 2019

በእሳት ተከቦ ማንቀላፋት አይቻልም!

(28 July, (አዲስ አበባ))--የኢትዮጵያን ዕጣ ፈንታ ከሚወስኑ መሠረታዊ ነገሮች መካከል አንዱና ዋነኛው ሰላም ነው፡፡ የአገር ህልውናም ሆነ የሕዝብ ደኅንነት የሚወሰነው በሰላም ነው፡፡ ሰላም ከሌለ መንግሥት አይኖርም፡፡ ይኖራል ተብሎ ቢታሰብ እንኳ የጉልበተኞች ስብስብ ነው የሚሆነው፡፡ ሰላም የህልውና ዋልታና ማገር ቢሆንም በቀላሉ የሚገኝ ግን አይደለም፡፡ ሰላም እንዲሰፍን በሕዝብ መካከል መተማመን ሊኖር ይገባል፡፡ ልሂቃን በአገር ጉዳይ በግልጽ መነጋገር መቻል አለባቸው፡፡ ልዩነቶች በእኩልነት ተስተናግደው የተሻለ ሐሳብ ተቀባይነት ሊያገኝ የሚችለው ሰላም ሲኖር ነው፡፡ ዋናው ጥያቄ ግን ሰላም እንዴት ይስፈን የሚለው ነው፡፡ ከግለሰብ ጀምሮ አገርን እስከሚመሩ ሰዎች ድረስ ለሰላም ትልቅ ግምት መስጠት አለባቸው፡፡

መንግሥት ጥያቄዎች ቀርበውለት በሕጋዊ መንገድ መመለስ ሲኖርበት ዳተኛ ከሆነ፣ ጥያቄ አቅራቢዎች ሌላ አማራጭ ሲፈልጉ ግጭት ይፈጠራል፡፡ በሕጋዊ መንገድ ጥያቄዎችን ማቅረብ ያለባቸው ኃይልን ተጨማሪ አማራጭ ሲያደርጉ፣ መንግሥት ሕግ ለማስከበር ሲል የኃይል ዕርምጃ ውስጥ ይገባል፡፡ ግለሰቦች በማኅበራዊ ትስስሮችም ሆነ በተለያዩ ዘደዎች ሐሰተኛ ወሬዎችን ሲያሠራጩ፣ በስሜት የሚጋልቡ ሰዎችን በማነሳሳት ጥፋት እንዲፈጸም ያደርጋሉ፡፡ ነገር ግን በሠለጠነ መንገድ ለመነጋገር ሲቻል ልዩነት ቢኖር እንኳ የጋራ አማካይ መፍጠር አያዳግትም፡፡ በአሁኗ ኢትዮጵያ ከእጅ እያመለጠ ያለው ፀጋ ይህ ነው፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አስተዳደር ሥልጣን ከተረከበ ወዲህ፣ ለአገር የሚጠቅሙና ተስፋ የተደረገባቸው በርካታ ጅምሮች ታይተዋል፡፡ ነገር ግን እነዚህን ጅምሮች ተባብሮ ለማስቀጠል የታየው የተሟሟቀ መነሳሳት እንከን ገጥሞታል፡፡ ይህንን እንከን በጋራ መርምሮ ከመነጋገር ይልቅ በየጎራው ማድፈጥና በነገር መጎነታተል፣ ከዚያም አለፍ ሲል በጠላትነት መተያየትና ለጠብ መፈላለግ እየተለመደ ነው፡፡ ያጋጠመው ችግር እንዴት መላ ሊበጅለት ይገባል ማለትን የመሰለ መፍትሔ ፍለጋ እያለ፣ ለውጡን አስቀልብሶ ቀውስ ውስጥ የሚከት ሴራ መጎንጎን ውስጥ እየተገባ ነው፡፡

ይህ ማንን ይጠቅማል ቢባል መልሱ ማንንም ይሆናል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ግራ የሚያጋባ ነገር ሲገጥም ነው እንግዲህ የመፍትሔ ያለህ መባል ያለበት፡፡ ችግር እንደ ተራራ በገዘፈባት አገር ውስጥ ልዩነትን አደብ አስገዝቶ በአንድነት መቆም አለመቻል ለሰላም ጠንቅ ነው፡፡ እንኳንስ ሽግግሩን በስኬት አጠናቆ ወደ ሚቀጥለው ምዕራፍ ለመሸጋገር፣ የህልውና ጉዳይ ዋናውና አሳሳቢው ይሆናል፡፡ ብዙዎችን የሚያስጨንቀው ተስፋ የተደረገበት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መጨንገፍ ብቻ ሳይሆን፣ ይህንን በሥጋት የተሞላ ጊዜ እንዴት ማለፍ ይቻላል የሚለው ነው፡፡ እዚህ ሁኔታ ውስጥ መገኘት ደግሞ በጣም ያሳዝናል፡፡

‹‹በሽታውን የደበቀ መድኃኒት አያገኝም›› እንደሚባለው፣ በአሁኑ ጊዜ እንደ ዋዛ ችላ የሚባሉ ችግሮች ከፍተኛ ጉዳት እያስከተሉ ነው፡፡ እውነቱን እንነጋገር ከተባለ በችግሮች ላይ በሀቅና በቅንነት የመነጋገር ፈቃደኝነቱ ካለ፣ ያን ያህል ለአደጋ የሚዳርጉ አልነበሩም፡፡ ነገር ግን ሴረኝነትና መሰሪነት የዓመታት ልማድ በመሆናቸው መተማመን የለም፡፡ በተለይ ፖለቲከኞች የረባ ብቃትና የሕዝብ ውክልና ሳይኖራቸው የሚፈጥሯቸው ችግሮች በሴራ የተተበተቡ ናቸው፡፡ የረባ አጀንዳ ሳይኖራቸው በማይረቡ ሐሰተኛ ወሬዎች መንጋዎችን ማሠለፍ ግን አያቅታቸውም፡፡

ቀላሉ የመቆመሪያ ካርድም ብሔርተኝነት ነው፡፡ ልሂቃኑ ደግሞ ከግላዊና ከቡድናዊ ጥቅም በላይ ምንም ነገር ስለማይታያቸው፣ የአገር ሰለምና ደኅንነት ለእነሱ ደንታቸው አይደለም፡፡ በመብት ተሟጋችነት ከለላ የሚያደቡ መሰሪዎች ራሳቸውን ትንንሽ ነገሥታት በማድረግ፣ በማኅበራዊ ትስስሮች ቅራኔዎችን በመፈልፈል ለግጭት የሚዳርጉ ቅስቀሳዎችን ያካሂዳሉ፡፡ ለሰከነና ለሠለጠነ ፖለቲካዊ ውይይት ዕድል አይሰጡም፡፡ ግለሰቦች የመሰላቸውን ሐሳብ ሲሰነዝሩ በየጎራው ፍላጎት እየተመነዘረ ይወገዛሉ፡፡ የንግግርና የጽሑፍ ነፃነት ይደፈጠጣል፡፡ ሐሳብን በሐሳብ ከመሞገት ይልቅ ማንነትን መሠረት ያደረጉ ዘለፋዎችና ስድቦች ይመረጣሉ፡፡ በዚህ ምክንያት የአደባባይ ሰዎች እየጠፉ አጉራ ዘለሎች የበላይነቱን ይይዛሉ፡፡ ይህ ደግሞ ለአገር ውድቀት ነው፡፡

ኢትዮጵያን ከድህነት፣ ከኋላቀርነትና ከዘርፈ ብዙ ችግሮች ማላቀቅ የሚገባቸው ልጆቿ በቅራኔ ተወጥረው ስለሰላም ማሰብ ይከብዳል፡፡ ይሁንና በዚህ ፈታኝ ጊዜ ደፋርና የመጣው ይምጣ የሚሉ ልጆች ያስፈልጓታል፡፡ ከምንም ነገር በላይ የአገራቸው ህልውና የሚያሳስባቸው ኢትዮጵያውያን ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ፣ ለሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር፣ ሁሉንም ኢትዮጵያውያን በእኩልነትና በፍትሐዊነት የምታስተናግድ ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትፈጠር በግንባር ቀደምትነት መሠለፍ አለባቸው፡፡

ይህ ጉዞ የሚጀምረው የተኮራፉ ወገኖች ለምን በጠረጴዛ ዙሪያ የሚነጋገሩበት ዕድል አያገኙም? መሠረታዊ የሆነ ቅራኔ ሳይኖር በመለስተኛ ችግሮች ለምን የጠላትነት ስሜት ይፈጠራል? ጥያቄዎች ያሉዋቸው ወገኖች ለምን በአግባቡ አይስተናገዱም? በሠለጠነ መንገድ በግልጽ ከመነጋገር ይልቅ ሐሜትና አሉባልታ ለምን ይቀድማሉ? ወዘተ. በመሳሰሉት ላይ መነጋገር የግድ ይላል፡፡ ኢትዮጵያ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የጋራ ቤታቸው እንደሆነች በመግባባት፣ የዘመናት ችግሮቿን ለመፍታት መረባረብ ይጠቅማል፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው አጉል ትከሻ መለካካት አገር ከማጥፋት የዘለለ ፋይዳ የለውም፡፡

ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ ከግጭት አዙሪት ውስጥ በፍጥነት መውጣት እንዳለባት ብዙ ቢወተወትም፣ በቅርቡ በደቡብ ክልል በሲዳማ ዞን ዘግናኝ ድርጊት ተፈጽሞ ንፁኃን ተገድለዋል፡፡ ነገ ይህ ዓይነቱ አሳዛኝና አሳፋሪ ድርጊት የት እንደሚያጋጥም አይታወቅም፡፡ በመላ አገሪቱ በሚፈጸሙ ጥቃቶች ንፁኃን ሲጎዱ እጃቸውን እንደ ጲላጦስ የሚለቃለቁ ኃይሎች፣ ድርጊታቸው አገርን ሲያጠፋ ወደ እነሱም እንደሚመጣ ሊረዱ ይገባል፡፡ ለጊዜው ከሕግና ከሕዝብ ዓይን የተሰወሩ ቢመስላቸውም ታሪክና ትውልድ ይፋረዳቸዋል፡፡ ለአገራቸው የሚያስቡ ሀቀኛ ኢትዮጵያውያን ግን እየታዩ ባሉት አሳዛኝ ድርጊቶች ተስፋ ሳይቆርጡ፣ ለሰላም መስፈን የሚቻላቸውን ሁሉ ከማድረግ ሊቆጠቡ አይገባም፡፡

ኢትዮጵያ የአደባባይ ሰዎች እንዳይኖሯት በሚያሸማቅቁ ነውረኞችና ከንቱዎች ሳይበገሩ፣ በግንባር ቀደምትነት ለሰላም መስፈንና ለነገ ብሩህ ተስፋ ኃላፊነታቸውን የመወጣት አደራ አለባቸው፡፡ ወቅቱ የፈለገውን ያህል አሥጊ ቢሆንምና ለአደጋ የሚዳርጉ ክስተቶች መኖራቸው ግልጽ ቢሆንም፣ ማንኛውንም ዓይነት መስዋዕትነት በመክፈል አርዓያነት ያለው ተግባር ለማከናወን ወደኋላ ማለት የለባቸውም፡፡  ኢትዮጵያ የምትፈልገው በክፉ ጊዜያት የሚታደጓትን እንጂ፣ በደስታዋ ጊዜ የሚፎክሩላትን አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ እሳት ውስጥ ገብተው የሚታደጓት ልጆች እንዳሉዋት ማስመስከር ይገባል፡፡ ለዚህም ነው በእሳት ተከቦ ማንቀላፋት አይቻልም የሚባለው!
ሪፖርተር , አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment