Wednesday, July 17, 2019

የዓባይ ባንክ ሠራተኞች ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ ይዘው ሲጓዙ መታሰራቸው ተጠቆመ

July 17, (አዲስ አበባ))--የዓባይ ባንክ አክሲዮን ማኅበር ሠራተኞች ከ16 እስከ 25 ሚሊዮን ብር ይሆናል የተባለ ገንዘብ ወደ አዲስ አበባ ይዘው ሲገቡ፣ በቁጥጥር ሥር ውለው መታሰራቸውን የሪፖርተር ምንጮች ገለጹ፡፡

የባንኩ ሠራተኞች ናቸው የተባሉት ግለሰቦች ገንዘቡን ከመሃል ሜዳ፣ ደብረ ብርሃንና በዚያው አካባቢ ካሉ የዓባይ ባንክ አክሲዮን ማኅበር ቢሮዎች ሰብስበው ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ላይ እያሉ፣ ወደ አዲስ አበባ መዳረሻ አካባቢ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡

ግለሰቦቹ እንዴት? ለምን? በማን ፈቃድ? ገንዘቡን ሰብስበው ይጓዙ እንደነበር፣ እንዲሁም የገንዘቡን ትክክለኛ መጠን እንዲያብራሩ የባንኩን ፕሬዚዳንት አቶ የኋላ ገሠሠን በግል ስልካቸው ሰኞ ሐምሌ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. አነጋግረናቸው ነበር፡፡

አቶ የኋላ፣ ‹‹ገና እያጣራሁ ነው፡፡ ልጨርስና እንነግራችኋለን፡፡ ነገ ደውሉልኝ፤›› ያሉ ቢሆንም፣ በቀጠረው መሠረት ማክሰኞ ሐምሌ 9 ቀን 2011 ዓ.ም. ቢደውልላቸውም ሆነ አጭር መልዕክት ቢላክላቸውም ምላሽ አልሰጡም፡፡

በቁጥጥር ሥር የዋሉት የባንኩ ሠራተኞችም ሆኑ ገንዘቡ እስከ ማክሰኞ ምሽት ድረስ እንዳልተለቀቁ የሪፖርተር ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment