Sunday, June 16, 2019

መተማመን ካልተቻለ አብሮ መራመድ አይቻልም!

(16 June 2019))--የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አስተዳደር በይፋ ሥራ ከጀመረ ወዲህ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ የኢትዮጵያን አጠቃላይ ዕውነታዎች ፍንትው አድርገው ከሚያሳዩ ክንውኖች ጀምሮ፣ ለዘመናት ተደብቀው የኖሩ ገመናዎችም ተገላልጠው ታይተዋል፡፡ ‹‹በሽታውን የደበቀ መድኃኒት አያገኝም›› እንደሚባለው፣

በርካታ ድብቅ ደዌዎች በይፋ በመታየታቸው ለፈውስ የሚያገለግሉ መፍትሔዎችን መፈለግ፣ የአገር ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ወገኖች ኃላፊነት ነው፡፡ የዘመናት ቁስልን ማመርቀዝ ብቻ ሳይሆን፣ አገርሽቶ መመረዝ እንዳያመጣ ማድረግም አስፈላጊ ነው፡፡ ለዚህም ሲባል ኢትዮጵያ በስፋት የገባችበት ለውጥ መሬት ቆንጥጦ፣ በኢትዮጵያዊያን ተሳትፎ በሚያስፈልገው ፍጥነት መጓዝ አለበት፡፡

ለውጥ አንዱን ጠቅሞ ሌላውን የሚጎዳ፣ አንዱን አቅፎ ሌላውን የሚያገል ውጤት እንዳይኖረው አካሄዱ ላይ ስምምነት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ቁልፉ መተማመን ነው፡፡ መተማመን የሚቻለው ደግሞ በመርህ ላይ የተመሠረተ የሰጥቶ መቀበል ግንኙነት ሲዳብር ነው፡፡ ይኼንን ዓይነቱን የሠለጠነ አካሄድ ተግባራዊ ለማድረግ ግን ቀናነት ያስፈልጋል፡፡ በአሻጥርና በሴራ የተተበተበው አሰልቺውና አታካቹ መንገድ ማንንም የትም አያደርስም፡፡ ይህም በተደጋጋሚ ተሞክሮ ከሽፏል፡፡

በኢትዮጵያ የግማሽ ክፍለ ዘመን ፖለቲካ ታሪክ በተደጋጋሚ የታየው በአምባገነንነት የተጀቦነ አጉል ብልጣ ብልጥነትና ክፋት ዜጎችን ለእስራት፣ ለሥቃይ፣ ለስደትና ለሞት ከመዳረግ ውጪ ፋይዳ ቢስ እንደነበር ለማንም ቢሆን የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ ለዓመታት በሥልጣን የቆየበት መንግሥታዊ አስተዳደር በሕዝብ ላይ የፈጠረው ምሬትና መንገሽገሽ ይኼንን በሚገባ ያሳያል፡፡ ለሦስት ዓመታት የዘለቀው ሕዝባዊ እንቢተኝነት የፈጠረው ከፍተኛ ትግል፣ ከራሱ ከኢሕአዴግ ውስጥ የለውጥ ኃይል እንዲደራጅ ማድረጉና የለውጥ ኃይሉም ቅርፊቱን በርቅሶ በመውጣት ሥልጣኑን በመረከቡ አገሪቱን ከጥፋት ታድጓል፡፡ ሕዝቡም በከፍተኛ ድጋፍ የለውጥ ኃይሉን መቀበሉ ይኼንን ሐሳብ ሙሉ ያደርገዋል፡፡

በሒደት ግን በየሥፍራው ያጋጥሙ በነበሩና አሁንም ባሉ ችግሮች ምክንያት ደግሞ የሐሳቦች መከፋፈል ይታያል፡፡ ለውጡን ከልብ የሚደግፉ፣ የሚጠራጠሩና የሚቃወሙ በየፈርጁ በስፋት ይስተዋላሉ፡፡ ሥልጣንን በዘዴ የነጠቀው፣ የተነጠቀውም ሆነ አመቺ ሁኔታ ካገኘ ለመንጠቅ የሚያሰፈስፈውም የዚህ የተከፋፈለ ስሜት ማሳያ ናቸው፡፡ ይኼንን ሁኔታ በመለወጥ ትክክለኛውን መንገድ መያዝ የሚቻለው ዓላማ፣ ለውጡን የጋራ ግብ በማድረግ ለሁሉም እኩል የሆነች አገር ለመገንባት መተማመን መፍጠር ሲቻል ነው፡፡ ካልሆነ ግን ውጤቱ ተያይዞ መውደቅ ነው፡፡ ከመውደቅ ደግሞ ምንም አይገኝም፡፡

በአሁኑ ጊዜ መተማመን እንዳይኖር ከሚያደርጉ ችግሮች መካከል የተወሰኑትን ነቅሶ መነጋገር ይገባል፡፡ የመጀመርያው በኢትዮጵያ አንድነትና በሕዝቡ አብሮነት ላይ የጋራ ራዕይ ሊኖር የግድ ይላል፡፡ ኢትዮጵያ ሲባል የሚከፋቸውና የሕዝቡን አብሮነት መስማት የማይፈልጉ ወገኖች አሁንም አሉ፡፡ ኢትዮጵያ በምትባል አገር ውስጥ እየኖሩ በቅዥት ሌላ ፍለጋ የሚባዝኑ ወገኖችን ወደ ዕውነታው በመመለስ፣ የአገር የጋራ ራዕይ ተጋሪ ወይም ተቋዳሽ ማድረግ የጠቢብ ፖለቲከኞች ግዴታ ነው፡፡

እነዚህ ወገኖች ለዓመታት ያጠመቋቸውን ወጣቶች ሳይቀር መስመር አስይዞ፣ የኢትዮጵያ የባለቤትነት መንፈስ እንዲኖራቸው ተግቶ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ሁለተኛው ከሥልጣን በላይ የአገር ጉዳይ ግድ የማይሰጣቸው ወገኖችም በብዛት አሉ፡፡ የእነሱ ግብ ሥልጣን በተገኘው መንገድ ተይዞ የሚፈልጉትን ዓላማ ማሳካት ሲሆን፣ ለእዚህ ሲባል ደግሞ ንፁኃን ቢሞቱና አገር ምስቅልቅሏ ቢወጣ ደንታ የላቸውም፡፡ እነዚህ ወገኖችና ተከታዮቻቸው ከግላዊና ከቡድናዊ ጥቅም በላይ የአገር ህልውና ስለማያሳስባቸው፣ ለአገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን ፈተና ናቸው፡፡ ይህም ብርቱ ጥረት ይፈልጋል፡፡ ሦስተኛው የፖለቲካ ጥበብ ያልገባቸው ወገኖች ጉዳይ ነው፡፡ እነዚህ ለውይይትና ለድርድር ከመዘጋጀት ይልቅ፣ በረባ ባልረባው ጉዳይ መነታረክ የሚወዱ የዜሮ ድምር ፖለቲከኞች ናቸው፡፡

ዴሞክራሲን ያነበንቡታል እንጂ በተግባር አይኖሩትም፡፡ ሁሌም ፀብ አጫሪነት፣ ጥላቻ፣ ቂም በቀልና ሴረኝነት ብቻ ናቸው የሚቀናቸው፡፡ እርስ በርስ ሲጣሉም ገመና መደባበቅ አይችሉም፡፡ እነዚህን ገርቶ ፈር ማስያዝ ትልቅ ጥረት ይፈልጋል፡፡ ከላይ የተገለጹት የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ መገለጫ ናቸው፡፡

መተማመን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ሁሉም ወገኖች ኃላፊነት አለባቸው፡፡ መንግሥት የሕዝብን ደኅንነትና የአገርን ጥቅም ከማስጠበቅ ባለፈ፣ አገር በሕግና በሥርዓት እንድትመራ የማድረግ ትልቅ ኃላፊነት አለበት፡፡ የሕግ የበላይነት በተግባር መረጋገጥ ሲጀምር ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ከሕገወጥ ድርጊቶች ይታቀባሉ፡፡

ተቋማትን በሚፈለገው መጠን ማጠናከርና የሕግ ማዕቀፎችን ከወቅቱ የለውጥ ቁመና ጋር ማመጣጠን ሲቻል፣ የፍርድ ቤቶች ነፃነት በሕዝብ ዘንድ አመኔታ ማግኘት ሲጀምር፣ የመንግሥትና የፖለቲካ ፓርቲ ሚና መደበላለቁን ሲያቆም፣ የፀጥታ ኃይሎች ገለልተኝነት ጥርት ብሎ ሲታይ፣ ለአድልኦና ለመድልኦ በር የሚከፍቱ ብልሹ አሠራሮች ሲወገዱና ሐሳቦች በነፃነት ያለ ከልካይ ሲንሸራሸሩ መብትና ግዴታ ተወራራሽ ይሆናሉ፡፡ ጉልበት አለኝ ብሎ የሚመካው በሕግ ሲገታና ሥርዓተ አልበኝነት ለማስፈን የሚሯሯጠው አደብ እንዲገዛ ሲደረግ፣ በሕዝብና በመንግሥት መካከል መተማን ይፈጠራል፡፡ ይህ መተማመን በፖለቲካ ፓርቲዎች፣ በታዋቂ ሰዎች፣ በተቋማትና በግለሰቦች ጭምር እየሰረፀ ውይይትና ድርድር ባህል መሆን ይጀምራሉ፡፡ ለዓመታት ጀርባ የተሰጣጡ ሳይቀሩ ፊት ለፊት ተቀምጠው ለመነጋገር ዳገት አይሆንባቸውም፡፡ ዕውነታው ይኼ ነው፡፡

ለኢትዮጵያ መፃኢ ዕድል መቃናት ዋናው መሠረት የልጆቿ መስማማት ብቻ ነው፡፡ ከበፊት ጀምሮ በፖለቲካው ውስጥ የተፈጠረው ሽኩቻና የእርስ በርስ ትግል የፈየደው እንደሌለ አንዱ ማሳያ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ከያዙ በኋላ የተፈጠረው ክስተት ነው፡፡ በኢትዮጵያ እስር ቤቶች ውስጥ የታጎሩ በርካታ ሺዎች ተፈቱ፡፡ ይህ ነው በሚባል የጦር ሜዳ ትግላቸው የማይታወቁ ኤርትራ ውስጥ ተጠልለው የነበሩ ግለሰቦችና ስብስቦች በሰላም ተመለሱ፡፡ አውሮፓና አሜሪካ ሲንከራተቱ የነበሩ በሰላም ገቡ፡፡

እስር ቤቶች ውስጥ የነበሩትም ሆኑ ከኤርትራና ከተለያዩ አገሮች የተመለሱ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች በመገለላቸው ምክንያት፣ ኢትዮጵያ ያጣችው መልካም አጋጣሚ ያንገበግባል፡፡ እነዚህ ወገኖች ለአገራቸው ማበርከት የሚገባቸውን እንዳያደርጉ ተገፍተው በመገለላቸው የደረሰው ሰቆቃ አይዘነጋም፡፡ ይኼ ጉዳይ ሲነሳ ያ አስከፊ ታሪክ መደገም የለበትም መባል አለበት፡፡

አሁንም ጊዜው አልረፈደምና የተጀመረው ለውጥ ግቡን እንዲመታና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሠረት ለመጣል መተማመን ያስፈልጋል፡፡ ለኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት ሰላም፣ ዴሞክራሲና ብልፅግና ነው የሚባለው እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በነፃነት፣ በፍትሐዊነትና በእኩልነት መኖር ስላለበት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ምቹ ሥርዓት ለመፍጠር ደግሞ ከግለሰብ ጀምሮ እስከ መንግሥት ድረስ መተማመን ያስፈልጋል፡፡ መተማመን ካልተቻለ አብሮ መራመድ አይቻልም!
ሪፖርተር ርዕሰ አንቀጽ

No comments:

Post a Comment