Wednesday, April 25, 2012

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሃይማኖት ላይ

(Sunday, 22 April 2012)--በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሚያዝያ 9 ቀን 2004 ዓ.ም. የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከእንደራሴዎች ለቀረበላቸው ልዩ ልዩ ጥያቄዎች ምላሽ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡

ከተነሡት ጥያቄዎች መካከል አንደኛው ከሃይማኖት ጋር ጣልቃ ገብነት የተያያዘ ነው፡፡ አቶ መለስ ምላሻቸውን የጀመሩት ሕገ መንግሥቱን በመንተራስ ነው፡፡ “መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው፡፡ የእስላም መንግሥት የለም፤ የክርስቲያን መንግሥት የለም፤ የዋቄፈታ መንግሥት የለም፡፡ ያለው የኢትዮጵያ ሕዝቦች መንግሥት ብቻ ነው፡፡ አንደኛ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፡፡ ሃይማኖትም እንደዚሁ፡፡ ሁለተኛ ማንኛውም ሰው የፈለገውን ሃይማኖት ማራመድ ይችላል፡፡ ግልጽ ነው፡፡ ሦስተኛ ማንኛውም ዜጋ ሕገ መንግሥቱን የማክበር ብቻ አይደለም፤ የማስከበርም ግዴታ አለበት፤” በማለት አብራርተዋል፡፡

ወቅታዊውን ገጽታ ሲፈትሹትም በተለያዩ ሃይማኖቶች የተለያዩ የጽንፈኝነት ምልክቶች መታየታቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአገላለጻቸው በተለይ በጥምቀት በዓል አዲስ አበባ ከታዩት መፈክሮች አንዱ “አንድ አገር አንድ ሃይማኖት” ነው፡፡ ፀረ ሕገ መንግሥትም ነው፡፡

መፈክሩን የያዙት ጥቂቶች ናቸው፡፡ “አንድ አገር አንድ ሃይማኖት” የሚል ሕገ መንግሥት የለንም፡፡ አንድ አገር የፈለገው ዓይነት ቁጥር ያለው ሃይማኖት ሊኖረው እንደሚችል ሕገ መንግሥቱ ይደነግጋል፡፡ ስለዚህ በዚህ ዙርያ የክርስቲያን መንግሥት እንዲኖር፣ ሕገ መንግሥቱን ከዚህ አኳያ ለመሸርሸር የሚፈልጉ በጣም ጥቂቶች ቢሆኑም እንዳሉ ያሳየናል ብለው ያስረዳሉ፡፡ እነዚህ ባብዛኛው የሕገ መንግሥት ግንዛቤ ችግር ያለባቸውና በማስተማር ሊመለሱ የሚችሉ መሆናቸውን ያክላሉ፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በእስልምና ሃይማኖት ዙርያ ችግሮች ይታያሉ፡፡ በአገራችን በሁሉም ክልሎች ለረዥም ጊዜ የቆየ ነባሩ የእስልምና እምነት ሱፊ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሙስሊም መቶ በመቶ ሱፊ ነበረ እንጂ ሺኣ የሚባል የለም፡፡ ሰለፊ የሚባለው እምነትም ባለፉት 20 እና 30 ዓመታት የመጣ ነው፡፡ እነዚህ የሱፊ እምነት ተከታዮች ከክርስትናው ጋር ለብዙ ሺሕ ዓመታት አብረው ኖረዋል፡፡ ሥርዓቶቹ የነበራቸው የአድልኦ ፖሊሲ እንደተጠበቀ ሆኖ በእስላምና በክርስቲያኑ መካከል በየትኛውም ዓለም፣ በየትኛውም አገር ካለው የተሻለ መቻቻልና አብሮ መኖር ታይቶበታል፡፡ ኅብረተሰቡ ምንያህል ተቻችሎ ተከባብሮ እንደኖረ የሚያሳይ ገጠመኝም ተናግረዋል፡፡

እንደርሳቸው አነጋገር፣ በቅርቡ አንድ ሰው በወሎ ስላጋጠመው ነገር ሲነግረኝ ነበር፡፡ ክርስቲያኖቹም፣ ሙስሊሞቹም አብረው የሚኖሩበት መንደር ነው፡፡ በድርቅ በተጎዱ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን በአግባቡ መያዝ ማስተዳደር ስላልቻሉ ነቅለው ለመሔድ ወስነው ታቦቱን በመንቀል ወደሌላ ቦታ ለማዞር ክርስቲያኖቹ ተመካክረው እንቅስቃሴ ሲጀምሩ ጎረቤቶቻቸው ሙስሊሞቹ ያ ታቦት ሊነቀል ነው የሚል ወሬ ይሰማሉ፡፡ መንደራችንና አገራችንን ልታጠፉ ነው? ወይ ምን እየሠራችሁ ነው ብለው ይጠይቋቸዋል፤ ስለጨነቀን ተጠቃለን ሌላ ቦታ ልንሔድ ነው ታቦታችንን ትተን አንሔድም ይሏቸዋል፡፡

ታቦቱ እናንተ ብታመልኩበትም በጋራ መንደራችን ውስጥ የነበረ ባህላችን፣ ሀብታችን ነው፡፡ የምታመልኩበት፣ የምታምኑበትም እናንተ ክርስቲያኖች ናችሁ፡፡ ግን የኛ መስጊድ የዚህ መንደር አንዱ ክፍል ነው፡፡ ይኸን መንደር የሚያውቅ ሰው ይህችን መስጊድ እንደ መንደሯ አንድ ክፍል አድርጎ መውሰድ አለበት፡፡ ይኸን መንደር የሚያውቅ ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችሁን እንደ አንድ የመንደሩ ክፍል አድርጎ መውሰድ አለበት፡፡ ስለዚህ ቀድሞ ነገር እኛን ሳታማክሩ ታቦቱን ይዛችሁ መሔድ አትችሉም፤ ተመካክረን ታቦቱ በነበረበት የሚቀጥልበት መንገድ ካለ እናያለን ብለው ተመካክረው የጨረሱበት ሁኔታ እንደነበር መስማታቸውን ገልጸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚናገሩት፣ የሰለፊ እምነት ተከታዮች ነፃ የሚሉት አንዳንዶቹ ከዚህ የተለየ አቋምና አመለካከት አላቸው፡፡ ብዙዎቹ የአልቃይዳ አሸባሪዎች ከእምነት አኳያ የሰለፊ እምነት ተከታይ ናቸው፡፡ ሰለፊዎች በሙሉ አልቃይዳ ናቸው አይባልም፤ ስህተትም ወንጀልም ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመርያ ጊዜ የአልቃይዳ ሕዋስ ተገኝቷል፡፡ በአብዛኛው ባሌና አርሲ፡፡  የዚህ ሕዋስ አባል የነበሩት በሙሉ ሰለፊዎች ናቸው፡፡ ይኸ ማለት ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሰለፊዎች አልቃይዳ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ በጣም የሚበዙት አይደሉም፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አንዳንድ የሰለፊ እምነት (አንዳንዶቹ ወሐቢያ ይሏቸዋል ትክክለኛ ቃል ላይሆን ይችላል) በተለያየ መንገድ አንዳንድ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት የሚያራምዱትን ግልባጭ ሲያራምዱ ታይተዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ውስጥ አብዛኛው ሕዝብ ሙስሊም ነው፡፡ ስታቲስቲክስ ያቀረበው መረጃ ውሸት ነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ ሙስሊም ስለሆነ የእስላም መንግሥት ነው መቋቋም ያለበት” የሚል ቅስቀሳ በሰፊው እነዚህ አክራሪዎች ያካሒዳሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚያሰምሩበት፣ አንዳንዶቹ ሰለፊዎች ሥራቸው በሙስሊሙና በክርስቲያኑ መካከል የቆየውን መቻቻል ማውገዝ ማጥፋት ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ከሰለፊዎቹ ጫፍ የወጡት ምን እንደሚያደርጉ፣ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ምልክቱ በአገራችን  እየታየ ነው በማለት ምሳሌ የሚያደርጉት በየመን፣ ግብፅ፣ ሊቢያ፣ ሶርያ፣ ቱኒዝያ ላይ ምን እየሠሩ እንደሆነ በማመልከት ነው፡፡ 

‹‹ግብፅ 24 በመቶ ድምፅ ያገኘው አልኑር ፓርቲ ሰለፊ ነው፡፡ ምን እየሠራ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ በሙሉ የጥፋት ኃይል ናቸው ባንልም፣ ከሰለፊ ውስጥ መቻቻል የሚደግፍ ኃይል እንዳለ ብንገነዘብም፣ ከነዚህ ውስጥ ግን ልክ ከኦርቶዶክስ ጥቂቶቹ “አንድ ሃይማኖት አንድ አገር” ብለው መፈክር እንዳራገቡት ሁሉ እንዲያውም ከሰለፊዎቹ ጥቂቶቹ፣ ይልቁንም  መፈክር ካሰሙት ኦርቶዶክሳውያን በቁጥር የሚበልጡ ሥራ እየሠሩ እንደሆነ ይታወቃል፤” ብለዋል፡፡ ይኸ ነገር በእንጭጩ ካልተቀጨ ነገ ምን ውጤት እንደሚያመጣ ብዙ ርቀት መሔድ እንደማያስፈልግ የመንና ግብፅን ማየት በቂ እንደሆነም ይጠቁማሉ፡፡

ከተፈጠረው ነገር በመነሣት ሃይማኖታዊ ተግባሩ ከሕገ መንግሥቱ ጋር መጋጨት እንደሌለበት፣ ሙስሊሙ ኅብረተሰብ ሕጉን ማክበር፣ ሃይማኖትና መንግሥት መለያየት እንዳለበት በደንብ እንዲጨብጥ በመንግሥት ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ “ኡላማዎቹ [ምዕመኖቻችንን] እናስተምራለን፣ ሕገ መንግሥቱን እናስጨብጣለን፡፡ ድርጊቱ ከእምነታችን ጋር አይሔድምና ብትመጡ ጥሩ ነው ብለው ስለጋበዙን በሚያደርጉት ስብሰባ ሁሉ ሕገ መንግሥቱን እናስተምራለን፡፡ መብቱም አለን፡፡ ስለ ሃይማኖቱ ችሎታውም መብቱም ያላቸው የሃይማኖቱ መሪዎች” ናቸው ሲሉም አስረድተዋል፡፡

አቶ መለስ አያይዘውም ያነሡት ነጥብ ስለ አሕበሽ ነው፡፡ “መንግሥት ‘አሕበሽ’ የሚባል ነገር አመጣብን” የሚል በተለይ ከሰለፊዎቹ መምጣቱ ተገቢ ሆኖ አይታየኝም፡፡ አንደኛ ነባሩ የእስልምና ተከታዮች እንደሚገልጹት አሕበሽ የሚባለው ከውጭ የመጣ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያዊው የሐረር እስልምና አዋቂ ሼሕ አብዱላሂ በአገራቸው መኖር ስላልቻሉ ወደ ሊባኖስ ሔደው የሱፊ እምነት አስተምህሮ ያራመዱበት እንደሆነ ከነባሩ የእስልምና ሊቆች እንደሚነገር አውስተዋል፡፡

ለማሳያነትም ያመጡት ዐረፍተ ሐሳብም አለ፡፡ እንዲህም አሉ፡፡ እንደሚነገረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ተከታይ የሆኑ ሕንዶችን ከሕንድ አስመጥቶ በቲኦሎጂ ኮሌጅ እንዲያስተምሩ ያደርጋል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ማስተማር የሚችሉት ሁሉም ኦርቶዶክሶች አይደሉም፤ ከኦርቶዶክስ ውስጥ የተወሰኑት የግብፅ፣ የሕንድ፣ ሶርያ፣ ኦርቶዶክስ ብቻ ናቸው፡፡

ስለዚህ ከሕንድ አስመጥቶ ስላስተማረ ለምን ሕንድ አስመጣህ ብለን እኛ ልንከሰው ነው? ከሃይማኖት መሪዎች በላይ እኛ አዋቂ ሆነን ይኸን ለምን አመጣህ ብለን ልንጠይቅ ነው? በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ የእስልምና እምነት መሪዎች ልክ እንደኛ ዓይነት አቋምና እምነት አላቸው ብለው የሚያስደስቷቸውን ሰዎች ከውጭ በአስተማሪነት ሲያመጡ ልንከለክላቸው ነው? እንደመንግሥት ለመሆኑ ይኸ አሕበሽ የሚባለው እምነት የውጭ፣ አዲስና መጤ ቢሆን መከለከል እንችላለን እንዴ? በኢትዮጵያ ያለውን ኢቫንጄሊካል (ወንጌላውያን) ክርስቲያኖችን ኢትዮጵያ ውስጥ እንዳይሰብኩ መጤናቸው ብለን ልናግድ ነው? አንችልም መብት የለንም፡፡ መጤ ነው፣ ነባር ነው፣ የሕዝቡ የመወሰን መብት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹መከልከል ብንችል ኖሮ ሰለፊዎቹን መጀመርያውኑ አዲስ እምነት ሆነው ለምን አልከለከልናቸውም? ሕገ መንግሥቱን እስካልተፃረሩ ድረስ የማምለክ፣ የማመን የማስፋፋት መብታቸው ነው፡፡ ይኸ ለእነርሱ የጠየቁትን መብት ለሌላው መከልከል አይችሉም፡፡

ሕገ መንግሥቱ አይፈቅድም፤ እኛ እንደመንግሥት አሕበሽ ይምጣ አይምጣ፣ የሕንድ ኦርቶዶክስ ፈላስፋ ይምጣ አይምጣ ጉዳያችን አይደለም፡፡ የኛ ሥራ አይደለም፡፡ የሃይማኖት መሪዎቹ ሥራ ነው፡፡ እውቀቱም የለንም እውቀቱ ያላቸው የሃይማኖቱ መሪዎቹ ናቸውና›› በማለት አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

‹‹እኛ የምናስከብረው መብቱን ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ሺአም ቢመጣ፣ ሰለፊም ቢመጣ ሌላም ቢመጣ እሰብካለሁ ካለ መብቱ ነው፤ ኢትዮጵያዊ ከሆነ ልንከለክለው አንችልም፡፡ መታየት ያለበት በዚህ መልኩ ነው፤›› ያሉት አቶ መለስ፣ ችግሩ እየመጣ ያለው ጥቂት ሰለፊዎች፣ አሁን በአዲስ ጉልበት ብቅ ብቅ ማለት የጀመረው አክራሪነት በየመን፣ በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በቱኒዚያና በሶርያ ብቅ ያለውን አዲስ የአክራሪነት ማዕበል በማያያዝ ኢትዮጵያም ውስጥ ማዕበል መፍጠር እንችላለን የሚል ግምት ይዘው የሚያደርጉት ሙከራ መሆኑን፣ እዚህም በግብር፣ በንግድ፣ በመሬት ምክንያት ያኮረፈ አንዳንድ ነጋዴም ትርፍ እስካገኘበት ጊዜ ድረስ እንደገባበትና ይኸንኑ ችግር ለመቋቋምም እየተሞከረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም አጽንኦት እንደሰጡበት፣ ችግሩ እየመነጨ ያለው መንግሥት ጣልቃ በመግባቱ አይደለም፡፡ መንግሥት ያስከበረው ሕገ መንግሥት ነው፤ መንግሥት ያስተማረው ሕገ መንግሥትን ነው፤ የማንኛውም ዜጋ የማመን መብት የሰለፊዎቹንም ጭምር የእምነት ነፃነት ነው ያስከበረው፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment