Sunday, January 01, 2012

አዲስ የኢትዮጵያዊነት ‹‹ሶፍት ዌር›› ያስፈልገናል!!

(Sunday, 01 January 2012, Reporter)--እኛ ኢትዮጵያዊያን ራሳችንንና ኢትዮጵያዊነትን ግለጹ ብንባል የምንገልጽባቸው የተለመዱ ዘዬዎችና ቃላት አሉ፡፡ እንግዳ ተቀባይ ሕዝብ፣ አይበገሬ ሕዝብ፣ ጨዋ ሕዝብ፣ አልገዛም ባይ ሕዝብ፣ ኩሩ ሕዝብ፣ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው ሕዝብ፣ ወዘተ እያልን እንገልጻለን፡፡

በዚህም ራሳችንን ለራሳችን የምንገልጽበት የኢትዮጵያዊነት መገለጫ ባህርይ ላይ ሁለት ዓበይት ጥያቄዎችን ማንሳት እንችላለን፡፡ ይገባልም፡፡  ጥያቄ አንድ፡- እውነት እነዚህ ባህርያት በአሁኑ ጊዜ በእኛ በኢትዮጵያውያን ውስጥ አሉ ወይ? ጥያቄ ሁለት፡- በአሁኑ ጊዜ ባለው አገራዊ፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታስ እነዚህ ባህርያት ብቻ ዳር ያደርሳሉ ወይ?

እነዚህን ጥያቄዎች አስተሳስረን እንመልሳቸው፡፡ እንግዳ ተቀባይነቱም፣ ጨዋነቱም፣ ኩሩነቱም፣ ፈሪሃ እግዚአብሔርነቱም፣ አይበገሬነቱም እየተመናመነ ነው ያለው፡፡  ቅናት፣ ምቀኝነት፣ መጠላለፍ፣ አሸባሪነት፣ አገርንና ሕዝብን መሸጥ፣ መስረቅ፣ መዝረፍ፣ በእጅጉ በኅብረተሰባችን ውስጥ እየተስፋፋና ሥር እየሰደደ ነው ያለው፡፡

የምን ጨዋነት? በአሁኑ ጊዜ ጉቦ አስፈሪ መሆኑ ቀርቷል፡፡ ጉቦ ለመቀበልም መደበቅና መሸሸግ እየቀረ ሁለት ነን አይበቃም፤ አሥር ነን ያንሳል ማለት ተጀምሯል፡፡ ለጉቦ ደረሰኝ ይቅረብ ቢባል በማን ስም ላድርገው የሚል እንጂ የሚያፍርና የሚፈራ እየጠፋ ነው፡፡

ለቤተሰብ፣ ለወገን፣ ለዜጋ መልካሙን መመኘት እየጠፋ ነው፡፡ እኔን ሀብታም ማድረግ ካልቻልክ ሌላውን ደሃ አድርግልኝ፣ እኔን ጤናማ ማድረግ ካልቻልክ ሌላውን በሽተኛ አድርግልኝ የሚል ፀሎት እየበዛ ነው ያለው፡፡ የወገን መልካም ውጤት የሚያናድደውና የወገን ውድቀት የሚያስፈነጥዘው ዜጋ እየተበራከተ ነው፡፡

የምን አልገዛም ባይነት? የምን ኩራት? ለገንዘብና ለጥቅማ ጥቅም ብሎ ራሱን ለሽያጭ የሚያቀርብ ወገን እየበዛ ነው፡፡ ደሃውም ሀብታሙም፣ የታቹም፣ የላዩም፣ ተራው ሰውም፣ ባለሥልጣኑም፡፡ ለጥቅማ ጥቅም ብሎ የአገር ሚስጥር የሚያወጣና የሚሸጥ አለ፡፡ ለግል ጥቅም ብሎ የአገር ክብር የሚያዋርድ አለ፡፡ የግል ፍላጎትን ለማርካት ብሎ ከጠላት ጋር የሚሰለፍ አለ፡፡ ለግል ጥቅም ብሎ ኢትዮጵያውያንን እየጎዳ፣ ከኢትዮጵያውያንም እየነጠቀ ለውጭ ዜጋ አሳልፎ የሚሰጥ አለ፡፡

እኔ የሌለሁበት ፀሎት በመንግሥተ ሰማያት አይሰምርም፡፡ መስመርም የለበትም ብሎ የአገርን ዕድገትና ልማት ከማየትና በዚያ ከመኩራት ይልቅ፣ የአገርን ጥፋት የሚፈልግና ውድቀቷ የሚያዝናናው ዜጋም እየታየ ነው፡፡ ራሳችን አናታልል፡፡ ራሳችን ለራሳችን ያስቀመጥነው የባህርይ መለኪያ እየተሸረሸረ፣ እየደበዘዘና እየጠፋ ነው፡፡

ችግሩ  ግን እሱ ብቻ አይደለም፡፡ የነበሩን ባህርያት አሁንም ቢኖሩ እንኳ ላለው አገራዊ፣ አኀጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ በቂ አይደሉም፡፡ በዓለም ላይ የተሳካለት አገርና ሕዝብ ሆነን ለመገኘት የነበሩት ብቻ ‹‹የብቃት ማረጋገጫ›› አይሆኑም፡፡  የበለፀገ፣ ፍትሕን የተላበሰ፣ ዴሞክራሲያዊ አመለካከት ያለው፣ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀምና የሚያጣጥም ሕዝብ መባል ይገባናል፡፡  አይ አተኳኮስ፣ አይ አስተጣጠቅ፣ አይ ዘራፍ ሲል ሲያምርበት፣ አየ በሳንጃ አንጀት ሲዘከዝክ፣ ወዘተ እያልን እርስ በርስ የምንሞጋገስበት ወቅት እያለፈ ነው፡፡

ለፍትሕ ሲቆረቆር፣ የወገን መበደል ሲያንገበግበው፣ ለእኩልነት ያለው እምነት፣ ለፕሬስ ነፃነት ያለው አቋም፣ ለሰብዓዊ መብት መከበር ያለው ተነሳሽነት፣ ለዴሞክራሲ ያለው ታማኝነት፣ ለሕገ መንግሥቱና ለሕግ ያለው ክብር እያልን ዜጋን የምንመዝንበትና መደናነቅ የሚገባን ዘመን ላይ ነን፡፡ ለዚህም ሲባል ነው አዲስ ‹‹ሶፍት ዌር›› ያስፈልገናል የምንለው፡፡

ጌትነትን፣ የአሽከርና የሎሌ ብዛትን የምናደንቅበት ወቅት ላይ አይደለንም፡፡ ከድህነት መላቀቅን፣ ኑሮ ማሻሻልን፣ ኤክስፖርት ማሳደግን፣ በቴክኖሎጂ ማደግን፣ የውስጥ ሀብት መፍጠርን፣ ከጥገኝነት መላቀቅን፣ ወዘተ የምናደንቅበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ለዚህም አዲስ ‹‹ሶፍት ዌር›› ያስፈልጋል፡፡

አዲስ ‹‹ሶፍት ዌር›› ሲባልም ‹‹ዲስክ›› ወይም ‹‹ፍላሽ›› አስመጥቶ የመጫን ጉዳይም አይደለም፡፡ ከትምህርት ቤት መጀመር ያለበት ነው፡፡ በዕለታዊ ኑሯችን ተግባር ላይ የምናውለው ሊሆን ይገባል፡፡ በመገናኛ ብዙኀን የምንለማመደውም የምንተገብረውም ነው፡፡ በተቋማት የሚተገበር ነው፡፡ በሕግና በመመርያ የሚደገፍ ነው፡፡ ሒደት ነው፡፡ ጊዜ የሚወስድ ጉዞ ነው፡፡

ስለሆነም ከአሁን ጀምሮ በዚህ አዲስ ‹‹ሶፍት ዌር›› የታነፀ ትውልድ ለመፍጠር አስፈላጊው ዝግጅት ይደረግ፤ ጉዞውም ይጀመር፡፡ ካለፈው ይዘነው መቀጠል ያለብንን ባህርይ (ወይም ‹‹ሶፍት ዌር››) እየገለጽን እናጠናክር፡፡ በዚህም ላይ ከወቅቱ ሁኔታ ጋር የሚጣጣም አዲስ ‹‹ሶፍት ዌር›› እንምረጥ፣ እንወቅና እንጫን፡፡

ይህ የሁላችንም ኃላፊነት ነው፡፡ የመንግሥትም፣ የግሉ ዘርፍም፣ የሲቪል ማኅበረሰቡም፣ የተቋማትም፣ የቤተሰብም፣ የመላው ሕዝብም ኃላፊነት ነው፡፡  ስለፍትሕ፣ ስለዴሞክራሲ፣ ስለልማት፣ ስለቴክኖሎጂ፣ ከድህንነት ስለመላቀቅ፣ ወዘተ የሚያስብ ባህርይ ከፈጠርን በዚህ ላይ አይበገሬነትና የነፃነት ቀናዒነት ይመጣል፡፡ ያለውና የነበረውም ይጠናከራል፡፡

ትልቁ ቁምነገር ግን ራሳችንን አናታልል፡፡ ራሳችን በፈጠርነው የራስ መገለጫ ባህርይ አንኮፈስ፡፡ አገራዊ፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተጨባጭ ሁኔታን በመገምገም በዚህ ዘመን በአሸናፊነት የሚያዘልቁንን ባህርያት እንያዝ እናጠናክር፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment