Thursday, August 01, 2013

ከፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የደረሰን ሙሉ መግለጫ

(Aug 01, 2013, (አዲስ አበባ))--ለዜጎች መሰረታዊ ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶችና ነፃነቶች የተሟላ ዋስትናና ጥበቃ ያጎናፀፈው ዲሞክራሲያዊው ህገ-መንግስታዊ ስርዓታችን የሀይማኖትን ነፃነት እኩልነት ለማረጋገጥ የፀኑ ተቋማዊና ህጋዊ ዋስትናዎችን አበጅቷል፡፡

በዚህም መሰረት መንግስትና ሀይማኖት እንዲነጣጠሉ አድርጓል፡፡ በመሆኑም በሀገራችን መንግስታዊ ድጋፍን የሚያገኝም ሆነ አሉታዊ ተፅእኖና ጫና የሚያደርግ አንዳችም ሀይማኖት እንዳይኖርም ተደርጓል፡፡

በሀይማኖትና በፖለቲካ መካከል ግልፅ ልዩነትን ያበጀው ህገ መንግስታዊው ድንጋጌ በግልፅም ሆነ በስውር ሀይማኖት የፖለቲካ አጀንዳ ማራማጃ መሆን እንደማይገባው ያመላክታል፡፡ በሀይማኖት ጉዳይ የፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነትን የሚከለክለው ይህ መርህ የሀይማኖት ተቋማትም ራሳቸውን በፖለቲካ ውስጥ ጣልቃ ማስገባት የሌለባቸው መሆኑን በግልፅ ደንግጓል፡፡

ሀይማኖቶችን ከፖለቲካ ተፅዕኖ ለመጠበቅም ማንኛውም አይነት በህግ ፈቃድ የተሰጣቸው የድጋፍም ሆነ የተቃውሞ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎች፣ በፀሎትና በአምልኮ ቦታዎች ሀይማኖታዊ አገልግሎት ላይ አንዳችም ጫናና ተፅዕኖ ማድረግ በማይቻልበት ርቀት እንዲካሄዱ በህግ እንዲወሰን መደረጉ ይታወቃል፡፡

ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ በአዲስ አበባና በአንዳንድ የክልል ከተሞች ውስጥ እነዚህ ህገ-መንግስታዊ መርሆዎች በሚፃረር አካሄድ ዜጎች የእምነት ነፃነታቸውን በተረጋጋና በሰላማዊ ሁኔታ እንዳይተገብሩ እንቅፋት በሚፈጥሩ ወገኖች መስጊዶች ሲታወኩና ሲበጠብጡ በርካታ ህገ ወጥ ተግባራትም ሲፈፅሙባቸው መቆየቱ ይታወቃል፡፡

እንዲህ አይነቶቹን ህገ ወጥ ተግባራት ሲፈፅሙ የቆዩ በአፍቅሮ ነዋይ የታወሩና በገንዘብ ለሚደጉሟቸው ወገኖች የሚሹትን ብጥብጥና ትርምስ ለማስፈን ላይ ታች የሚሉ ጥቂት የሰለፊ/ወሃቢ እምነት ተከታይ የሆኑ አክራሪዎች መሆናቸውን ለህዝብ በይፋ ከማሳወቅ አልፎ መንግስት ከመላው ሰላም ወዳዱ ህብረተሰብ ጋር በመተባበር የእነዚህን አክራሪዎች መረን የለቀቀ ህገ ወጥ አካሄድ ለመቆጣጠር ያስቻሉ ተከታታይ እርምጃዎችን መውሰዱ ይታወሳል፡፡

እነዚህ በገንዘብ የታገዙ የሰለፊ/ወሃቢ አክራሪዎች ዜጎች መንፈሳዊ ተግባራት በሚያከናውኑባቸው መስጊዶችና የፀሎት ስፍራዎች የሽብር አድማዎችን በመጠንሰስና በአገር ሰላምና ፀጥታ እንዲሁም በሰላማዊ ዜጎችና ምዕመናን ላይ አስከፊ የወንጀል ጥቃቶችን ለመፈፀም ሲያሴሩ ተገኝተው ህጋዊ እርምጃ የተወሰደባቸው መሆኑም ይታወሳል፡፡

ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ለኢሬቴድ በላከው መግለጫ እነዚህ አክራሪ ወሃቢ/ሰለፊ ቡድኖች ከፍ ሲሉ በተጠቀሱ ህገወጥ ድርጊቶች ብቻ ሳይወሰኑ እነዚህን ነውረኛ ድርጊቶቻቸውን የተቃወሙና ያጋለጡ የሀይማኖት አባቶች በአደባባይ የመግደል የሽብር ሴራዎችን የጠነሰሱት ዜጎች ሀይማኖታዊ አገልግሎት በሚያገኙባቸው መስጊዶች ውስጥ ነበር፡፡

እነዚህ አክራሪዎች ህገ ወጥ የሽብር ተግባሮቻቸውን የሚቃወሙ ምዕመናንና የሀይማኖት አባቶችን ስምየያዘ ዝርዝርን እስከማዘጋጀም በመድረስ በህብረተሰቡ ሰላማዊ ፀጥታ ላይ የተጋረጡ አደገኛ አሸባሪዎች መሆናቸውን በይፋ አሳይቷል፡፡

ግልፅ ፀረ-መንግስት መፈክሮች እና ፖለቲካዊ የተቃውሞ ውርጅብኞችን እያሰሙ የፀሎት ስርዓቶችን በማወክና በመበጥበጥ በዜጎች ላይ ከፍተኛ እንግልት አድርሰዋል፡፡ በቅርቡም ፖለቲካን ከሀይማኖት ጋር በመደባለቅ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ከተዘጋጁ ፖለቲካዊ የተቃውሞ ሰልፎች ከማዳመቅ አልፈው የሀይማኖት አባቶችን በአሰቃቂ መንገድ የገደሉ አሸባሪዎች ላይ የሚደረገው የፍርድ ምርመራ ስራ እንዲደናቀፍ ለማድረግ ሲሞክሩ ተስተውለዋል፡፡

እነዚህ ህገ ወጥ ድርጊቶቻቸውን አጠናከረው የቀጠሉት እነዚህ ለገንዘብ የተገዙ የሰለፊ/ወሃቢ አክራሪዎች መላው ሰላም ወዳድ የሙስሊም ማህበረሰብ አመታዊው ታላቁን የረመዳን ፆም ወር ለማጠናቀቅ በመንፈሳዊ ዝግጅት ላይ ባለበት ባሁኑ ወቅት ሰላምን ለማወክና በየመስጊዶቹ ሁከትና ብጥብጥ ለመቀስቀስ በማሰብ በተለይ ዘመናዊ የመገናኛ ብዙሀን አውታሮችን በመጠቀም ህገ-ወጥ ቅስቀሳዎችን እያደረጉ ይገኛሉ፡፡

ሰፊው ሰላም ወዳዱ ሙስሊም ህብረተሰብ እነዚህ አክራሪ የወሃቢ/ሰለፊ ምንደኞች ቤተ እምነቶችን ወደ ግርግር፣ ሁከትና የትርምስ ቀጠናነት ለመለወጥ ዛሬ ረብሻ አንዋር ነው፣ ነገ ደግሞ በሌላ መስኪድ ነው በማለት በሚነዙት አፍራሽ የአድማ ቅስቀሳ ሳይዘናጉና ፀሎቱን በተለመደው አኳኋን በየአካባቢው በማካሄድ የአክራሪዎችን ሴራ እንዲያከሽፍ ፖሊስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

በመሆኑም እነዚህ ምንደኞችና አክራሪዎች በነገው ዕለት በሀይማኖት ሽፋን በመስጊዶች ውስጥ የሚያካሄዱትን የጥፋት ድርጊት ለማስቆም ፖሊስ ተገቢና አስፈላጊውን እርምጃ የሚወስድ መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን በጥብቅ ያሳስባል፡፡

መላ ኢትዮጵያውያን በተለይም ሰላም ወዳድ የሙስሊም ማህበረሰብ በስሙ እየማሉና እየተገዘቱ ከውጭ በሚላክላቸው ነዋይ ህሊናቸው ታውሮ አርብ በመጣ ቁጥር በተመረጡ መስጊዶች ውስጥ ሁከትና ብጥብጥ ለመፍጠር ጥረት በሚያደርጉ አክራሪ ወሃቢ/ሰለፊዎች ላይ ተገቢውን ክትትል በማድረግ ፖሊስ ለሚወስደው እርምጃ የተለመደ ድጋፍና ትብብሩን እንዲያደርግ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ለኢሬቴድ በላከው መግለጫ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ምንጭ፡ ኢሬቴድ

1 comment:

King Solomon said...

Kill them all and send them to jail in guantanamo,they are a cancer on the whole world

Post a Comment