Friday, November 22, 2013

ባለሀብቶች «ከስደት የተመለሱ ወገኖቻችንን የመደገፍ ጉዳይ የእኛም ነው» አሉ

(Nov 22, 2013, (አዲስ አበባ))-- በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከሳዑዲ አረቢያ ተመላሽ ወገኖች ወደ ቤተሰቦቻቸው እስከ ሚሸኙ ድረስ እንዲያርፉ አንድ ማዕከል ተቋቁሟል። በእዚህ ማዕከል 250 የሚደርሱ ሕፃናትና ሴቶች ይገኛሉ፡፡

በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በሚገኘው ማዕክል «ከጎናችሁ ነን እንደግፋችኋለን» ያሉ የግሉ ዘርፍ ባለሀብቶች ያዘጋጁትን ምሳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶክተር ቴድሮስ አድሀኖም በተገኙበት ትናንት ከተመላሾቹ ጋር አብረው ተመግበዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ቴድሮስ አድሀኖም እንደተናገሩት፤ ድንገተኛው አጋጣሚ ከተፈጠረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን በመንግስት በኩል በጀት ተመድቦ ዜጎችን ወደ አገራቸው የመመለሱ ሂደት እየተከናወነ ነው፡፡ እስከ ትናንት በስቲያ ድረስም 10ሺ707 ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ «አጋጣሚው ደራሽ ስለነበር መንግስት ጊዜ ሳይሰጥ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ገብቷል» ያሉት ዶክተር ቴድሮስ፤ ሂደቱ የሌሎች ድጋፍ እንዲኖር በመንግስት በኩልም ፍላጎት ያሳደረ መሆኑን ነው ያመለከቱት፡፡

ሥራው ከተጀመረ በኋላ የግል ዘርፉን በመወከል «ወገኖቻችንን ወደ አገራቸው በማስገባቱ ሂደት እኛም ድጋፍ ማድረግ እንፈልጋለን» በሚል ባለሀብቶች በተወካዮቻቸው አማካኝነት ከትናንት በስቲያ ወደ ቢሯቸው ተገኝተው ከእርሳቸው ጋር ሰፊ ውይይት ማድረጋቸውን ነው ያስታውሱት፡፡

«የባለሀብቶቹ ተወካዮች በራሳቸው ተነሳሽነት ችግሩ የሁላችንም ነው፤ በመፍትሄው ላይ መንግስት ብቻ ሳይሆን እኛም መረባረብና ተመላሾችን መደገፍ አለብን፤ እንደ ዜጋ እኛም የበኩላችንን እናድርግ» በሚል ጥያቄ ማቅረባቸውን አስታውሰው፤ በዚህ በጣም መደሰታቸውንና የኮሩባቸው መሆኑንም ነው ሚኒስትሩ የሚናገሩት። ባለሀብቶች ለተመላሽ ወገኖቻቸው ማድረግ ለሚፈልጉት ድጋፍ መንግስት ከጎናቸው እንደሚቆም በውይይቱ ወቅት እንዳረጋገጡላቸው ይናገራሉ፡፡

የጋራ ኮሚቴ በማቋቋም እቅድ በማዘጋጀት ለተመላሾች አቀባበል ከማድረግ አንስቶ እስከ ማቋቋም ባለው ሂደት በግሉ ዘርፍ፣ በመንግስትና በሌሎች አካላት የሚሰጡ ድጋፎችን የማስተባበር ሥራ ለመስራት ከጎናችን እንዲቆሙ ከባለሀብቶቹ ተወካዮች ጋር ስምምነት ላይ መደረሱንም አመልክተዋል፡፡

«ባለሀብቶቹ ቃል በገቡ ማግስት ለተመላሽ ወገኖቻቸው ድጋፍ ማድረግ ጀምረዋል» ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ይህ ተግባራዊ እንቅስቃሴአቸው ባለሀብቶቹ ወገኖቻቸውን ለመደገፍ ያላቸውን ጽኑ እምነት እንደሚያ መለክትም ነው የተናገሩት፡፡ የግል ዘርፉን ወክለው ተመላሾቹ ያረፉበት ቦታ በመገኘት መወያየታቸውና የምሳ ግብዣ ማድረጋቸው አጋርነታቸውን የሚያረጋግጥ እንደሆነና እንደተደሰቱበትም ነው የተናገሩት። ይህ የባለሀብቶቹ አርአያነት ያለው ተግባር በቀጣይም የግል ዘርፉም ሆነ ሌሎች የህብረተሰቡ ክፍሎች ለተጀመረው ሥራ ድጋፍ እንዲያደርጉ የሚያነሳሳ ነው ፡፡

የባለሀብቶቹ ተወካዮች በበኩላቸው የአሁኑን አጋጣሚ ያላገኙት ሌሎች ባለሀብቶች ለተመላሾቹ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ምንም ጥርጥር እንደሌላቸው ነው ያረጋገጡት። «ማንኛውም ሥራ በራስ ተነሳሽነት የሚጀምር አካል ይፈልጋል» ያሉት ተወካዮቹ፤ በመንግስት የተጀመረውን ሥራ በጽኑ የወገንተኝነትና የተነሳሽነት ስሜት መደገፍ እንደሚኖርባቸውም ነው ያመለከቱት።

«ሰው የመሆናችንና ኢትዮጵያዊነታችን ትርጉሙ ይህንን የመሰለውን ደራሽ ችግር በመፍታት ላይ ካልተገለጠ የመስራትና የመኖር ትርጉሙ ምንድን ነው» በሚል በሁሉም ላይ የተፈጠረውን ጥያቄ ለመመለስ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር በመነጋገር በፍጥነት ወደ ተግባር መግባታቸውንም ነው የሚናገሩት፡፡ «ወገኖቻችን በሰላም አገራቸው ተመልሰው እየተጨዋወትን ምሳ በመብላታችን በጣም ተደስተናል፡፡ በዚህ ጭንቅ ሰዓት ከእነሱ ጋር አብሮ እንደመሆን የሚያስደስተን ነገር የለም» ብለዋል፡፡

ስብስቡ «ኢትዮጵያውያን ለኢትዮጵያውያን» በሚል ሃሳብ ወገኖችን ለመደገፍ በማሰብ የተጀመረ መሆኑን ተወካዮቹ ጠቅሰው፤«ዋናው መነሻቸውም ለዚህ አስቸኳይና የድረሱልኝ ጥሪ እንደ ዜጋ አስቸኳይና የአጭር ጊዜ መፍትሄ የሚጠበቅብንን ለመወጣት ነው» ብለዋል። በቀጣይም ዘለቄታዊነት ባለው መልኩ ችግሮቹን ሙሉ ለሙሉ ማስቆም ባይቻልም በህብረተሰቡ ዘንድ የአስተሳሰብ ለውጥ ለመፍጠር አቅም በፈቀደ መልኩ እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል፡፡

ከባለሀብቶቹ ተወካዮች አንዱ አቶ ሀብታሙ አዱኛ «ችግሩ የሁላችንንም ቤት ያንኳኳ ነው» ይላሉ። ችግሩን ለመፍታት ሁሉም መረባረብ አለበት እንጂ ሥራውን በመንግስት ላይ ብቻ መተው እንደማይገባው የገለጹት ባለሀብቱ፤ «የተነሳሳነው በጊዜያዊ ስሜት ብቻ ሳይሆን ከመንግስት ጎን በመቆም ዘለቄታዊ መፍትሄ ለመስጠትም ነው» ሲሉ አጋርነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡

ሀገር አቀፍ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ወደ አገራቸው የሚመለሱትን «በተለያዩ የሥራ ዘርፎች ተሰማርተው የተረጋጋ ኑሮ እንዲኖሩ እናደርጋለንም» በማለት ቃል ገብተዋል፡፡
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment