Sunday, November 24, 2013

የሳዑዲ አረቢያ ተመላሾች ቁጥር ከ50ሺ በላይ ሊደርስ ይችላል

(Nov 24, 2013, ( አዲስ አበባ))፦ ከሳዑዲ አረቢያ በመመለስ ላይ ያሉት ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከ50ሺ በላይ ሊደርስ እንደሚችል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ቴድሮስ አድሓኖም ትናንት ለጋዜጠኞች እንዳስ ታወቁት፤ ቀደም ሲል የተመላሾቹ ቁጥር ከሰባት አስከ አሰር ሺ ቀጥሎም 23ሺ እንደሚሆን የተገመተ ቢሆንም፣በአሁኑ ወቅት ካሉ መረጃዎች መገንዘብ እንደተቻለው የተመላሾቹ ቁጥር ከ50ሺ እስከ 80 ሺ ሊደርስ ይችላል።

ለግምቱ መለያየት ዜጎቹ በህገ ወጥ መንገድ ወደ አገሪቷ የገቡ በመሆናቸው የተደራጀ መረጃ ባለመኖሩ መሆኑን ገልጸው፤ ዜጎቹን የመመለሱ ሂደት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በቀን ወደ ሳዑዲ አረቢያ ስድስት ጊዚያት በረራ በማድረግ እስከ አራት ሺ ዜጎች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ እየተደረገ መሆኑን አመልክተው፤ እስከ ትናንት ማታ የተመላሾቹ ቁጥር 19ሺ ሊደርስ እንደሚችልም ገልጸዋል።

ተመላሾቹን ለማቋቋም ከክልሎች ጋር በመወያየት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ሚኒስትሩ አብራርተዋል። እንደ ዶክተር ቴድሮስ ገለጻ፤ መንግስት በሳዑዲ አረቢያ የሚገኙ ዜጎች ህጋዊ እንዲሆኑ አልያም ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ለማድረግ እንዲሁም ወደ አረብ አገራት የሚደረጉ ጉዞዎችን ለማስቀረት ትኩረት ሰጥቶ ሲሰራባቸው የቆዩ ጉዳዮች ናቸው።

የሳዑዲ አረቢያ መንግስት በሰጠው የአራት ወራት ቀነ ገደብ ከ38ሺ በላይ ዜጎች ህጋዊ እንዲሆኑ መደረጉን አመልክተው፤ በወቅቱ ከሳዑዲ አረቢያና ከየመን እስከ አምስት ሺ ዜጎች ወደ አገር ቤት ለመመለስ ጥረት ቢደረግም መመለስ የቻሉት 329 ብቻ መሆናቸውን ነው ያመለከቱት። «አሁን ከስደት እየተመለሱ ካሉ ዜጎች መረዳት እንደቻልነው ስደተኞቹ የሳዑዲ አረቢያ መንግስት እንዲህ ዓይነት እርምጃ ይወስዳል ብለው ስላልጠበቁ በተቀመጠው ቀነ ገደብ መመለስ አልፈለጉም»ሲሉም ነው ሚኒስትሩ ያብራሩት።

ከሳዑዲ አረቢያ ህገ ወጥ ስደተኞቹን ለመመለስ ጥረት በተጀመረበት ወቅት አንድ ኢትዮጵያዊ ወጣት በአገሪቷ ፖሊስ መገደሉን አስመልክቶ፤ መንግስት ከሳዑዲ መንግስት ማብራሪያ መጠየቁን አስታውሰዋል። «ከፖሊስ መሳሪያ ሊቀማ ሲል ነው የተገደለው» የሚል ምላሽ ከሳዑዲ አረቢያ በኩል መሰጠቱን ጠቅሰዋል። «ይሁንና እኛ በተሰጠን ምላሽ ባለመርካታችን ከወጣቱ ግድያ ጋር ተያይዞ ተጨማሪ ጥናት እንዲደረግ ጠይቀናል» ብለዋል።

በዜጎች ላይ የደረሰውን ችግር አስመልክቶ የሚታዩ የህግ አመራጮች ካሉ በቀጣይ እንደሚታዩ አመልክተው፤ «በአሁኑ ወቅት ግን ቅድሚያ የምንሰጠው ዜጎቻችን ወደ አገራቸው መመለስን ነው» ሲሉም ተናግረዋል።

«መንግስት ዜጎቹን ለመታደግ ጠንከር ያለ እርምጃ አልወሰደም ይባላል» የሚል ጥያቄ ከጋዜጠኞች የቀረበላቸው ሚኒስትሩ፤«እርምጃው ለስላሳ ነው ጠንካራ ከማለት ይልቅ ካጋጠመው ሁኔታ ጋር የሚመጣጠን እርምጃ እየተወሰደ ነው ወይስ አይደለም?» ብሎ መጠየቅ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። «ከሁኔታው ጋር ተመጠጣኝ እርምጃ እየወሰድን መሆናችንን በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል»ብለዋል።

ሳዑዲ አረቢያ በአገሯ የሚገኙ ህገ ወጥ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ያስተላለፈችውን ትዕዛዝ ተከትሎ ዜጎቹ ወደ አገራቸው እየተመለሱ መሆናቸው ይታወቃል።
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment