Thursday, June 06, 2013

የህዳሴው ግድብ በግብፅና ሱዳን አሉታዊ ተፅእኖ እንደማያስከትል ዳግም ያረጋገጠ ሪፖርት

(June 06, 2013, (አዲስ አበባ))--ለዘመናት የማይደፈር የሚመስለው ሲደፈር ብዙዎች ማመን አቃታቸው፡፡ ግራ በመጋባት ስሜት ውስጥ የተዋጡም አልጠፉም፡፡ በቅዠት እንጂ በእውናዊው ዓለም ውስጥ መኖራቸውን የተጠራጠሩም ጥቂት አይደሉም፡፡ ብቻ ብዙዎች በተደበላለቀ ስሜት ውስጥ ሆነው ነበር ዜናውን የተከታተሉት፡፡ መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መሰረት ሲጣልና የግድቡ ግንባታ መጀመር ሲበሰር፡፡

የግድቡ ግንባታ በይፋ ሲጀመር ሥራው ለአፍታም ሳይቀዛቀዝ በፍጥነት እንደሚከናወን ተገለፀ፡፡ ይህም በተግባር ተረጋገጠ፡፡ እንደተባለውም አገራዊ ርብርቡ በደንብ ተጠናክሮ ግንባታው ተጧጧፈ፡፡ የህዝቡ ድጋፍም ተጋጋለ፡፡ በኢትዮጵያውያን ሙሉ አቅም ለኢትዮጵያውያን የሚከናወነው ግዙፉ የኃይል ማመንጫ አባይን ለልማት ማዋል እንደሚቻል ዋናው ማሳያ ሆነ፡፡

የኢትዮጵያውያን የራስን ሀብት በራስ አቅም ማልማት የመቻል ተምሳሌትነትንም አረጋገጠ፡፡ ሙሉ ወጪው በኢትዮጵያውያን የሚሸፈነው ይህ  ሜጋ ፕሮጀክት ግንባታው ሲጠናቀቅ ስድስት ሺ ሜጋ ዋት በማምረት ለኃይል አቅርቦቱ ዕድገት አስተማማኝ ደጀን ይሆናል፡፡

ቁጭትን ባነገቡና የአይቻልም መንፈስን በሰበሩ የአባይ ልጆች በአባይ ላይ የሚገነባው የኃይል ማማ ጉዞው ባይገታም የተወሰኑ የተቃውሞ ድምፆችን ማስተናገዱ አልቀረም፡፡ በተለይም በግብፅ በኩል የሚቀርበው ቅሬታ አሁንም አልተገታም፡፡ የግድቡ መገንባት በግብፅ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር በተደጋጋሚ ሲገለፅ ይደመጣል፡፡ እውነታው ደግሞ የዚህ ተቃራኒ መሆኑ በተጨባጭ መረጃዎች ቀርቧል፡፡ ግድቡ የተፋሰሱን አገራት ተጠቃሚ እንደሚያደርግ በባለሙያዎች ጥናት ተረጋግጧል፡፡ ፍትሃዊ የአባይ ውሃ ክፍፍልን መሰረት ያደረገ ፕሮጀክት መሆኑም ተወስቷል፡፡

ይህም ሆኖ ግን አሁንም ለግብፆች እውነታው አልተዋጠላቸውም፡፡ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ውሃ የማይቋጥርና ሚዛን የማይደፋ ቅሬታ ማቅረቡን ተያይዘውታል፡፡ ከአባይ ውሃ ፍትሃዊ ክፍፍል ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያን ጨምሮ ስድስት የላይኛዎቹ የወንዙ ተፋሰስ አገራት የደረሱበትን ስምምነት ያልፈረመችው ሱዳን በግድቡ ግንባታ ላይ ያቀረበችው ቅሬታ የለም፡፡

ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ ዓለማየሁ ተገኑ በአንድ ወቅት ከጋዜጣው ሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ የግብፅና የሱዳንን አቋም «…ሱዳን የግድቡን ግንባታ በከፍተኛ ደረጃ ትደግፋለች፡፡በግብፅ በኩል ቀድሞ ከነበረው አቋም የተለየ ነገር አይታይም፡፡ነገር ግን ኢትዮጵያ ባስቀመጠችው አቅጣጫ መሰረት ውይይቶች እየተካሄዱ ነው፡፡ ጥናትም እየተካሄደ ነው፡፡

ከውይይቶቹና ከጥናቱ ውጤት በኋላ ያለውን ነገር ማየት ይሻላል» በማለት ምላሽ ሰጥተው ነበር፡፡ ምንም እንኳን የግድቡ መገንባት በተፋሰሱ አገራት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተፅዕኖ አለመኖሩ በኢትዮጵያ በኩል ቀድሞ የታወቀና በጥናት የተረጋገጠ ቢሆንም በታችኞቹ የተፋሰሱ አገራት ዘንድ ግልፅነትና በቂ ግንዛቤ እንዲኖር ዓለምአቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ተዋቅሮ ጥናት እንዲያካሂድ ተደርጓል፡፡ ይህም በሶስቱ የተፋሰሱ አገራት (ኢትዮጵያ፤ግብፅና ሱዳን)ትብብር የተዋቀረ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት ተነሳሽነትም ከፍተኛ ነበር፡፡ ዓለምአቀፉ የባለሙያዎች ቡድን ከየአገራቱ የተውጣጡ ስድስት ባለሙያዎችና በሶስቱ አገራት በጋራ የተመረጡ አራት ዓለም አቀፍ ባለሙያዎችን ያካተተ ነው፡፡

የባለሙያዎቹ ቡድን ለአንድ ዓመት ያህል የተጣለበትን ኃላፊነት ለመወጣት ተገቢውን የማጣራትና የመገምገም ሥራ በከፍተኛ ጥንቃቄ ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ በዚህም  የታላቁን የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ የጥናትና የዲዛይን ሰነድ በመመርመር ፣በግንባታው ቦታ በመገኘትና ሂደቱን በመቃኘት፣ በሶስቱ አገሮች ውስጥ ለስድስት ጊዜ ያህል በመሰባሰብና በተነሱ ጉዳዮች ላይ በመወያየት እንዲሁም ከግድቡ የግንባታ ተቋራጮችና አማካሪዎች ጋር በመመካከር የደረሰበትን የመጨረሻ የጥናት ውጤት ሰሞኑን ይፋ አድርጓል፡፡ የጥናት ውጤት ሪፖርቱንም ለሶስቱ አገሮች መንግስታት ግንቦት 23 ቀን 2005 ዓ.ም አቅርቧል፡፡

 የሶስቱም አገራት ተወካዮችና ዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ተስማምተው የፈረሙበት የቡድኑ የመጨረሻ ሪፖርት ለኢፌዴሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ደርሷል፡፡ ሚኒስቴሩም የሪፖርቱን ጥቅል ይዘት አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ በባለሙያዎቹ ቡድን  እንደተረጋገጠው የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በተፋሰሱ አገራት ላይ የሚያመጣው ጉዳት የለም፡፡ ይልቁንም ተጠቃሚነታቸውን ያሳድገዋል፡፡

የቡድኑ ውጤት ሶስት ነጥቦችን በጉልህ ማስቀመጡን የሚኒስቴሩ መግለጫ ያስረዳል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ የታላቁ የህዳሴ ግድብ የዲዛይን ስራ ዓለም አቀፍ ደረጃውን በጠበቀ የዲዛይን መመዘኛና መርሆች ላይ የተመሰረተ መሆኑን በቀዳሚነት ያስቀምጣል፡፡ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ለሶስቱም አገራት ከፍተኛ ጥቅም የሚሰጥ መሆኑም በቡድኑ ሪፖርት በግልፅ ተቀምጧል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በሁለቱ ተጋሪ አገራት (ግብፅና ሱዳን) ላይ ጉልህ ጉዳት የማያደርስ መሆኑን ቡድኑ ማስታወቁን ነው ሚኒስቴሩ በመግለጫው ያመለከተው፡፡

ሪፖርቱን መሰረት አድርጎ የተሰጠው መግለጫ እንደሚያስረዳው በግድቡ መገንባት የሚገኙ ጥቅሞችና ሊደርሱ የሚችሉ ችግሮች ካሉ አንዳንድ ተጨማሪ ጥናቶች እንዲጠኑ የአጥኚዎች ቡድኑ ጠይቋል፡፡ የግድብ ግንባታ ለተፋሰሱ አገራት የተሻለ ጥቅም እንዲሰጥ የሚረዱ ሃሳቦችንም አቅርቧል፡፡ ኢትዮጵያ የባለሙያዎችን ቡድን በማቋቋም ከሁለቱ አገራት ጋር መተማመንን ለመፍጠር የወሰደችው እርምጃ በቡድኑ አድናቆት ተችሮታል፡፡

የቡድኑ ሪፖርት ኢትዮጵያ የግድቡ ግንባታ የታችኞቹን የተፋሰሱን አገራት የሚጠቅም እንጂ የማይጎዳ መሆኑን በተደጋጋሚ ስትገልፅ የነበረውን እውነታ የሚያጠናክር ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ለህዳሴው ግድብ ጉዳት አልባነትም ዳግም ዕውቅና የሰጠ ሰነድ ሆኗል፡፡ ኢትዮጵያ ለዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ከግድቡ ግንባታ ጋር በተያያዘ እየሰጠች ያለው መረጃ ትክክለኛና በእውነተኛ ጥናት ላይ የተመሰረተ ለመሆኑም ማጠናከሪያ ነው፡፡ የአባይ ወንዝን በፍትሃዊነት ለመጠቀም እያስተጋባች ላለው የጠራና የፀና አቋም ትልቅ ደጀንም ሆኗል።

የህዳሴው ግድብ የግንባታ ጉዞ አሁንም ልጓሙ አልተገታም፡፡ በኢትዮጵያውያን የተባበረ ክንድና አገራዊ ስሜት ግንባታው የተለያዩ ምዕራፎችን እየተሸጋገረ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት የግንባታው ሥራ ከ20 በመቶ በላይ ደርሷል፡፡ ግድቡ በሚገነባበት ቦታ ላይም የወንዙን ተፈጥሮአዊ የፍሰት አቅጣጫ የማስቀየር ሥራ ተከናውኗል፡፡ ይህም በግንባታው ሂደት ወሳኙ ምዕራፍና ቁልፉ ተግባር ነው፡፡ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በግንባታው ሥፍራ በመገኘት የወንዙን አቅጣጫ የማስቀየር ተግባር ሲያስጀምሩ «…የዓባይ ወንዝ አቅጣጫ መቀየር ለእኛ ኢትዮጵያውያን ያለው ትርጉም ዘርፈ ብዙና ቀለመ ደማቅ ነው…» ነበር ያሉት፡፡

ይህ የተፋፋመ ግንባታ እየተከናወነ ባለበት ሁኔታ የዓለም አቀፉ ባለሙያዎች ቡድን ሪፖርት ይፋ መሆን ለኢትዮጵያውያን ትልቅ የምስራች ነው፡፡ ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብም ኢትዮጵያ ትክክለኛ የልማት ጎዳናን ተከትላ እያለማች እንደምትገኝ ያበሰረ ነው፡፡ የባለሙያዎቹ ቡድን ሪፖርትን ተከትሎ የተለያዩ መገኛኛ ብዙኃን ሰፊ ሽፋን ሰጥተውታል፡፡ የሶስቱን ተፋሰስ አገራት አቋምም በተወሰነ መልኩ ለማንፀባረቅ ሞክረዋል፡፡ ከግድቡ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ቅሬታ ስታቀርብ የነበረችው ግብፅ የሪፖርቱን  ይዘት ከማጣጣል ወደ ኋላ አላለችም፡፡

የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ሙርሲ ሪፖርቱን «…ደረጃውን ያልጠበቀና በዝርዝር ያልቀረበ…» በማለት በቃል አቀባያቸው በኩል መግለፃቸውን የግብፁ አህራም ድረ ገፅ በዘገባው አስታውቋል፡፡ በአገሪቷ ውስጥ ከሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ከግብፅ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን የሃይማኖት አባቶች ጋርም ፕሬዚዳንቱ በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውን ድረ ገፁ ጨምሮ ገልጿል፡፡ በዚህ ወቅትም ፕሬዚዳንቱ የተለየ አቋም አላሳዩም፡፡ «…ሪፖርቱ ግድቡ የሚያስከትለውን ጉዳት አላካተተም…» በማለት ሪፖርቱ ክፍተት እንዳለበት የያዙትን አቋም አጠናክረዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ እንዲህ ቢሉም የአገራቸውን አደራ ተቀብለው በጥናቱ የተሳተፉት ግብፃውያን ባለሙያዎች ከቡድኑ አባላት ጋር በመሆን ለአንድ ዓመት ያህል ትኩረት ሰጥተው ያከናወኑትን ሥራ የመጨረሻ ሪፖርት ትክክለኛነት በፊርማቸው አረጋግጠው አቅርበዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ እውነታውን መቀበል ቢያቅታቸውም እውነታው ግን በባለሙያዎቹ ሪፖርት በግልፅ ሰፍሯል፡፡

ፕሬዚዳንት ሙርሲ የሚሰነዝሩትን አስተያየት ተከትሎ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በድረ ገፆች ላይ አስተያየታቸውን ሲገልፁ ተስተውሏል፡፡ «…የአባይ ውሃ የተፈጥሮ ስጦታ ነው፡፡ ለናይል ተፋሰስም ከ86 በመቶ በላይ የሚሆነውን የውሃ ድርሻ የምታበረክተው ደግሞ ኢትዮጵያ ናት፡፡ በዚህ ስሌት ኢትዮጵያ ከወንዙ በከፍተኛ ደረጃ የመጠቀም አቅጣጫ መከተል ነበረባት፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውሃውን በፍትሃዊነት እንጠቀም ነው እያለች ያለችው፡፡ ግብፅ ይህን አቋም በደስታ መደገፍ ሲገባት ቅሬታ ማቅረቧ ተገቢ አይደለም፡፡

«…አባይን በፍትሃዊነት ለመጠቀም በትብብር መስራት ይገባል፡፡ የባለሙያዎቹ ቡድን የደረሰበትን የመጨረሻ ሪፖርት መቀበልም ተገቢ ነው፡፡ እውነታዎችን ለመሸፋፈን መሞከርና መሯሯጥ ተቀባይነት የለውም፡፡ ግብፅ እውነታውን ተቀብላ የግድቡ ግንባታ የሚያመጣው ጉዳት አለመኖሩን ተረድታ በፍትሃዊነት ለመጠቀም የተጀመረውን መንገድ ብትከተል ጠቀሜታው የጎላ ነው…» የሚሉና ሌሎች አስተያየቶችም በስፋት እየተሰነዘሩ ይገኛል፡፡

No comments:

Post a Comment