Thursday, June 06, 2013

የህዳሴው ግድብ - የግብጽ መገናኛ ብዙሃንና ፖለቲከኞች

(June 06, 2013, (አዲስ አበባ))--ከሰሞኑ በግብጻውያን ቤት ወሬው ሁሉ የዓባይና የህዳሴው ግድብ ጉዳይ ሆኗል። ኢትዮጵያ የዓባይን የፍሰት አቅጣጫ የማስቀየሯን ዜና ተከትሎ ከከፍተኛ የአገሪቱ ባለስልጣናት ጀምሮ ባለሙያዎች ናቸው የተባሉ ሁሉ አስተያየታቸውን መስጠታቸውን ቀጥለዋል።

የአገሪቱ የዜና አውታሮች አስተያየቶቹን እየተቀባበሉ ማስተጋባታቸውን ተከትሎም ጉዳዩ ተሟሙቋል። በተለይ ከአንዳንድ የፕሬዚዳንት ሞሀመድ ሙርሲ መንግስት ተቃዋሚዎች የሚደመጡት አስተያየቶች በአሁኑ ወቅት ልዕልና ካገኘው የፍትሐዊነት አካሄድ በጣሙን ያፈነገጡ መሆናቸው ነው የሚስተዋለው።

ያኔ - ድሮ ድሮ እንበለው - የዓባይ ባለቤትነት የግብጾቹ ብቻ ነበር። ኢ ፍትሃዊ በሆኑ የቅኝ ግዛት ስምምነቶች ተመክተው «እኛ (ግብጾች) የወንዙ ብቸኛ ባለቤትና ተጠቃሚ ነን» ሲሉ ኖሩ። ለዓመታት በተካሄዱት የዓባይ ተፋሰስ አገራት የድርድር መድረኮችም ላይ ይህንኑ አካሄድ በመከተላቸው የፍትሃዊነትን ጎጆ መቀለስ አልተቻለም። የኋላ ኋላ ግን ኢትዮጵያ መራሹ የላይኛው ተፋሰስ አገራት የፍትሃዊነት ንቅናቄ ልዕልና አገኘ፤ ኢትዮጵያም በዓባይ ላይ የህዳሴዋን ግድብ መገንባት ጀመረች።

ይኸኔም ቢሆን ግብጾች አልተኙም «ኢትዮጵያውያን በራሳቸው አቅም ግድብ መገንባት አይችሉም፤ የውጭ ብድርና እርዳታ ካላገኙ በስተቀር። እናም ለጋሾቻቸው እጃቸውን እንዳይዘረጉላቸው እናከላክል» በሚል ተንቀሳቀሱ፤ ተሳካላቸው። ኢትዮጵያውያን ግን በተባበረ ክንድ ግድባቸውን ለመገንባት ተረባረቡ። ገና ከወዲሁም የትብብራቸውን ፍሬ ሲንዠረገግ መመልከት ጀመሩ።

ዛሬ ደግሞ ለመላው የአባይ ጥቁር ልጆች አዲስ ምዕራፍ ተከፈተ። ለዘመናት ሲፈስ የነበረውን ታላቁን ወንዝ በቁጥጥር ስር ማዋልና አቅጣጫውን ማስቀየር ተቻለ። አሁን ኢትዮጵያውያን የህዳሴያቸውን ግድብ እውን ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማይሉ ቁርጥ ሆነ። ይህም በግብጻውያን ዘንድ የታወቀና የተረጋገጠ ሆነ። ካይሮም «የኢትዮጵያ ግድብ አይጎዳንም» በሚሉና «የኢትዮጵያ እንቅስቃሴ ግብጽን በእጅጉ የሚጎዳ ነው» በሚሉ ሁለት ጽንፎች ተሰቅዛ ተይዛለች።

አዲስ አበባ ደግሞ ለካይሮ የምታስተላልፈው መልዕክት ትናንትም፣ ዛቀሬም፣ ነገም ያው አንድና አንድ ሆኗል - «የህዳሴው ግድብ ግንባታ አንቺንም ሆነ ካርቱምን አይጎዳምና አትጨናነቂ» እያለቻት ነው። እንዲህም ሆኖ ካይሮ ከጭንቀት አልወጣችም። ካለፈው ሳምንት መጨረሻ ጀምሮም ከኢትዮጵያ፣ ከግብጽና ከሱዳን እንዲሁም ከዓለም አቀፍ ገለልተኛ ባለሙያዎች የተውጣጣውን የአጥኚ ኤክስፐርቶች ቡድን ሪፖርት በጉጉት ስትጠባበቅ ቆይታለች። ሪፖርቱም ለሶስቱ አገራት የተሰጠ ሲሆን፤ ግድቡ በግብጽና በሱዳን ላይ ጉልህ ጉዳት እንደማያደርስ ነው በባለሙያዎቹ የተረጋገጠው። ፕሬዚዳንት ሙርሲም የግብጽን ኮፕቲክ ቤተክርስትያን ጨምሮ መላ የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችንና ልሂቃንን በቤተ መንግስታቸው እንዲሰባሰቡ ጋብዘዋል - በሪፖርቱ ላይ ለመምከር።

ባሳለፍነው ግንቦት 22 ቀን 2005 ዓ.ም እትማችን «ካይሮ ምን አለች?» በሚል የዓባይን አቅጣጫ መቀየር ተከትሎ በግብጽ የተሰሙ ወሬዎችን አስነብበናችኋል። በዚህኛው እትማችንም ጉዳዩ መነጋገሪያ መሆኑን ተከትሎ በግብጽ ያሉትን መረጃዎች እንደሚከተለው እናስዳስሳለን። አልአህራም፣ አልማስሪ አልዩም፣ ኢጅፕት ኢንዲፔንደንት፣ ኢጂፕት ዴይሊ ኒውስና ሌሎቹም የአገሪቱ የብዙሃን መገናኛ አውታሮች ምንጮቻችን ናቸው።

የአህራም ኦን ላይን ዘገባዎችን እናስቀድም። «ኢትዮጵያና ግብጽ በህዳሴው ግድብ ዙሪያ የማይስማሙ ከሆነ ጉዳዩ ወደ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት መሄድ አለበት» ይላል አንዱ ዘገባ። ግብጽ እስከዛሬ በብቸኝነት ስትጠቀምበት የኖረችው የናይል የውሃ ድርሻ እንዲጠበቅ የማድረግ ፖለቲካዊ ብቻ ሳይሆን ህጋዊ መብትም እንዳላት አድርጎ በመግለጽ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት መውሰድ እንደምትችል ከመንግስት ምንጭ አገኘሁት ያለውን መረጃ ጠቅሶ ነው ድረ ገጹ ያስነበበው።

እርግጥ ነው በዓለም አቀፍ የፐብሊክ ህግ መሰረት በአገሮች መካከል የሚነሱ አለመግባባቶችን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ማዕቀፍ ስር ለተቋቋመው ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ማቅረብ ይቻላል። ይሁንና የግብጽና የኢትዮጵያ ጉዳይ ለፍርፍድ ቤቱ ለመቅረብ የሚችልበት ህጋዊ አስረጂ እንደማይገኝለት እሙን ነው። ግብጾች እ.ኤ.አ በ1929 እና በ1959 የተደረጉ የቅኝ ግዛት ውሎችን እያነሱ «ህጋዊና ታሪካዊ ተጠቃሚ ነን» በሚል ኢፍትሃዊን መስመር በህጋዊነት ለምድ ሸፍነው ቢንቀሳቀሱ ክርክራቸው ውሃ የሚያነሳ እንደማይሆን እርግጥ ነው - ፍትሀዊ የዓባይ ውሃ ተጠቃሚነት ልዕልና አግኝቷልና።

በጣም የሚያስገርመው ነገር ደግሞ 75 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ የሚይዘው የህዳሴው ግድብ ተገንብቶ ከተጠናቀቀ በኋላ ውሃው እስከሚጠራቀም ድረስ ግብጽ ለተከታታይ አምስት ዓመታት ከ20 በመቶ የሚልቅ የውሃ ጉድለት እንደሚገጥማት ተደርጎ መዘገቡ ነው። ይህ ዘገባ ዓለም አቀፍ የባለሙያዎቹ ቡድን ሪፖርቱን ሳያቀርብ የተሰጠ አሳሳች መረጃ ከመሆኑም በላይ «ግድቡ ማንንም አይጎዳም» እያለች ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ከገለጸችውና በባለሙያዎቹ ሪፖርትም ይፋ ከተደረገው እውነታ ጋር ፈጽሞ የሚጣረስ መሆኑን ለመረዳት አያዳግትም።

«የናይል ተፋሰስ ምንጭ እኛ ነን፤ የናይል ውሃችንን ለመውሰድ የሚደረገውን እንቅስቃሴ ሁሉ እንቃወማለን» የሚለው የግብጻውያኑ የሰሞኑ መፈክር ደግሞ በጣሙን ያስቃል። በሳምንቱ መጨረሻ በርካታ ግብጻውያን በግብጽ የኢትዮጵያ ኤምባሲ አካባቢ የተቃውሞ ትዕይንት ባካሄዱበት ወቅት ያሰሟቸው እነዚህ መፈክሮች አስገራሚ ሳይባሉ አይቀርም፤ «የናይል ተፋሰስ ምንጭ እነሱ...»

ይሄኛው ዘገባ ደግሞ ከግርምትም በላይ ነው። ሃምዲን ሰባሂ የተባሉት የግራ ዘመሙ ኢጂፕሽያን ፖፑላር _ከረንት ፓርቲ ኃላፊ የሰጡት አስተያየት እንዲህ ተጽፏል «የህዳሴውን ድግብ እንድትገነባ ኢትዮጵያን የሚደግፉ አገራት መርከቦቻቸው በስዊዝ ቦይ እንዳይተላለፉ ግብጽ መከልከል አለባት» ይላል። ኧረ እንዲያውም አህራም ኦን ላይን የእርምት ዘገባ አወጣበት እንጂ « የህዳሴውን ግድብ የግንባታ እቃዎች የጫኑ የኢትዮጵያ መርከቦች በስዊዝ ቦይ እንዳይተላለፉ ግብጽ በሯን መዝጋት አለባት» በሚል፤አስቀድሞ የተሰማው ወሬ ግን ሰበር ዜና ሆኖ ተሰራጭቶ ነበር።

ፖለቲከኛው በተለይ ጣታቸውን የቀሰሩት በቻይናና በኢጣሊያ ላይ ነው - የግድቡን ግንባታ ይደግፋሉ በሚል። ኢትዮጵያ የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየሯን ደግሞ ፕሬዚዳንት ሙርሲ ከአዲስ አበባ ከተመለሱ ከአንድ ቀን በኋላ መፈጸሙን በማውሳት «ይህ ግብጻውያንን ማዋረድ ነው» ሲሉ ገልጸውታል። ነገር ግን የግድቡ ግንባታም ሆነ በግንባታው ሂደት የሚከናወኑ ሁሉም የኮንስትራክሽን ምዕራፎች አስቀድሞ በተያዘላቸው መርሃ ግብሮች መሆኑን ጠንቅቀው ቢያውቁ ኖሮ ፖለቲከኛው ይህንን ሃሳብ ባልሰነዘሩ ነበር።

ሌላው የአህራም ኦን ላይን አስገራሚ ዘገባ ከግብጽ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች የተሰማው አስተያየት ነው። የአል ጋማ አል ኢስላም ቡድን አባል የሆነው ሼክ አብዱል አከር ሃማድ «የኢትዮጵያ ታላቁ ህዳሴ ግድብ እና የአባይ ፍሰት አቅጣጫ መቀየር 'ጦርነትን ማወጅ ነው'» ሲል ነበር የተናገረው። አያይዞም «ግብጽ ክብሯን ማስጠበቅ አለባት፤ የግድቡንም ግንባታ መቃወም ይኖርባታል» በማለት ገልጿል። ኢትዮጵያ በፍትሃዊነት ጎዳና ተጉዛ ሁሉም በፍትሃዊነት ይጠቀም በማለቷ ነው እንግዲህ ጦርነት አወጀች በሚል በሼክ ሃማድ ጣት የተቀሰረባት።

« የዓረብ አገራት ለኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ድጋፍ እያደረጉ ነው» ሲል ወቀሳ ያሰማውን ራህያ የተባለውን የፖለቲካ ፓርቲ መስራች ሀዘን ሳላህ አቢ ኢስማኤልን አስተያየት አስቀድመን ወደ አል ማስሪ አልዩም ዘገባዎች እናምራ። በዜና ምንጩ እንደተመለከተው ግለሰቡ በኳታር፣ ሳዑዲ አረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስን የመሳሰሉ የዓረብ አገራት ላይ ክሱን ያሰማል - ለህዳሴው ግድብ ድጋፍ እያደረጉ ነው በሚል። ይሁንና የህዳሴው ግድብ መሀንዲሶች፣ ግንበኞች፣ አናጢዎች፣ የወንዝ አቅጣጫ አስቀያሾች፣ ገንዘብ ለጋሾችና ባለቤቶች ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ጠንቅቆ ባለማወቅ የተሰጠ አስተያየት መሆኑ ሲታሰብ ፖለቲከኛው ጉንጩን አለፋ ከሚባል ውጪ ረብ ያለው ሀሳብ አቅርቧል አያስብለውም።

ይሄኛው አስተያየት ሰጪ ደግሞ ጀነራል ሙሀመድ አል ቢላል ይባላሉ። ባለፉት ወራት «ግብጽ የኢትዮጵያን ግድብ በአየር ልትደበድብ ነው፤ ግብጽ በሱዳን ግዛት ውስጥ የአየር ኃይል ማዕከል ለመገንባት ተዘጋጅታለች» ወዘተ የሚሉ አሉባልታዎች በተደጋጋሚ ሲደመጡ እንደነበር ይታወሳል። በገልፍ ጦርነት ወቅት የግብጽ ኃይል አዛዥ የነበሩት ጀነራል ቢላል ግን «ግብጽ የኢትዮጵያን ግድብ ደበደበች ማለት በመላው ዓለም ጥርስ ውስጥ ገባች ማለት ነው» ሲሉ ለአል አረቢያ ሳተላይት ቻናል መናገራቸውን ነው ኢጂፕት ኢንዲፔንደንት ያስነበበው።

ከአገራት ጋር ጦርነት ውስጥ የመግባትን ጣጣ በተለይም ለግብጻውያን የሚያስከትለውን ችግር ጠንቅቀው የሚያውቁት ጀነራሉ «. . . ደግሞም ኢትዮጵያ ግድብ የመገንባት መብት እንዳላት ዓለም አቀፍ መግባባት ተፈጥሯል» ሲሉ ነው የገለጹት። የደህንነትና ስትራቴጂ ኤክስፐርት ናቸው የተባሉት ሌላው አስተያየት ሰጪ ሜጀር ጄነራል አህመድ አብዱል ሀሊምም «ዲፕሎማሲያዊ አማራጭን መጠቀም ከሁሉም የሚበልጠው አካሄድ ነው» ሲሉ የጀነራል ቢላልን ሃሳብ አጠናክረዋል።

የግብጽ ግራ ዘመም ፖለቲከኞች ኢትዮጵያ ከነፋስና ከጸሀይ ኤሌክትሪክ ማመንጨት እየቻለች አባይ ላይ ትኩረት ማድረጓ ግብጽን ለመጉዳት ካላት ፍላጎት ነው የሚል ሃሳብ ይሰነዝራሉ። እርግጥ ነው ኢትዮጵያ ከነፋስ ኃይል፤ከጸሀይና ከምድር ውስጥ እንፋሎትም (ጂኦተርማል) እንዲሁ ቀላል የማይባል ኤሌክትሪክ ማመንጨት ትችላለች። ነገር ግን እነዚህ ሁሉ አማራጮች ቢኖሩም ሁሉም በአንድ ጊዜ ሊለሙ አይችሉም። የነፋስ ሀይል ማመንጫ አስተማማኝ አይደለም፤ ኤሌክትሪክ የሚገኘው ሲነፍስ ብቻ በመሆኑ። ነፋስ በፍጥነት የሚነፍሰው በደረቅ ወራት ነው። በእነዚህ ወቅቶች ደግሞ የውሃ መጠን ይቀንሳል። ስለዚህ የኃይል አማራጮች መኖራቸው ለመደጋገፍ ይጠቅማል።

ከውሃ የኤሌክትሪክ ሃይልን የማመንጨት ቴክኖሎጂ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከረጅም ዘመናት ጀምሮ ጥቅም ላይ እየዋለ ያለና ሳይንሱም የበሰለ አማራጭ ነው። በወጪ ረገድም ዝቅተኛ ነው። ኤሌክትሪክ ከማመንጨትም ሌላ ተጓዳኝ ጥቅሞችም አሉት። ከሁሉም በላይ አስተማማኝ በመሆኑ ቅድሚያ ተመራጭ ያደርገዋል። ለዚህ ነው ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቶቿን በማልማት ላይ ቅድሚያ ትኩረት የሰጠችው። 
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment