Friday, September 16, 2011

መንግሥት የዊኪሊክስን መረጃና የመረጃ ምንጮች መሠረተ ቢስ ናቸው አለ

(15 September 2011, ሪፖርተር)--የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት በአዲስ አበባ ተቀማጭ ከነበሩ የአሜሪካ አምባሳደሮችና በየጊዜው ወደ ኢትዮጵያ ከመጡ ኃላፊዎች ጋር አደረጉት የተባለው ውይይት፣ በቅርቡ በዊኪሊክስ ድረ ገጽ ቢወጣም ተገኘ የተባለው መረጃና የመረጃ ምንጮቹ መሠረተ ቢስ ናቸው ሲል መንግሥት አስተባበለ፡፡

ሪፖርቱ አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካን ኤምባሲ / መረራን አስተማማኝ የመረጃ ምንጭ አድርጎ ‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት ራሱ ከገደላቸው በኋላ ለአሸባሪነት ሥራ ያዘጋጁት ፈንጂ በእጃቸው ላይ እያለ ፈንድቶ የሞቱ በማስመሰል ለማደናገር ሞክሯል በማለት›› ካቀረበው ወሬ ጀምሮ፣ በተለያዩ የመረጃ ምንጮቹ አገኘሁት የሚለው መሠረተ ቢስ መረጃ ይዞ የቀረበ ነው ሲል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሐምሌ 2 ቀን 2001 .. ለአሜሪካኖች ‹‹የበሽርን መንግሥት አስወግዱ›› የሚል ምክር እንደሰጧቸው በማስመሰል በዚሁ የዊክሊክስ ህትመት ላይ ኤምባሲው ዋቢ ተደርጎ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኤምባሲው ወደ አገሩ ባስተላለፈው በዚያው መልዕክት ላይ በአንድ እራስ ሁለት ምላስ እንዲሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹የበሽርን መንግሥት የማስወገድ አማራጭ የማይሠራ እንደሆነ›› ማውሳታቸውን ገልጿል፡፡

 ከዚህም በመነሳት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ለአሜሪካን መንግሥት ተወካዮች መንግሥታቸው ‹‹የሱዳን መንግሥት በደቡብ ሱዳንና በዳርፉር ጉዳይ ላይ ሊያከብረው የሚገባውን ግልጽ መዳረሻ በማስቀመጥ፣ የሱዳን መንግሥት የመከበብ መንፈስ እንዳይሰማው ማድረግ እንዳለበት›› መምከራቸውን ያወሳል ይላል በጽሕፈት ቤቱ የወጣው መግለጫ፡፡

‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት ለዓለም ግልጽ ባደረገው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲው፣ የአንድን ሉዓላዊ አገር መንግሥት በሌላ የመተካት ኃላፊነት የየአገሩ ሕዝብ እንጂ የማንም ውጫዊ ኃይል ተልዕኮ እንዳልሆነ በግልጽ አስቀምጧል፡፡
 
በዚህ ጥያቄ ላይ የመንግሥት ለውጥን ወይም ግልበጣን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲው አንድ አካል አድርጎ ከሚመለከው የአሜሪካ መንግሥትም ጋር መሠረታዊ ልዩነት አለው›› ያለው መግለጫው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በጉዳዩ ላይ ከአሜሪካ መንግሥት ጋር በተወያዩበት ጊዜ ያቀረቡት ይህንኑ የኢትዮጵያ መሠረታዊ ፖሊሲና አቋም ብቻ ነው ብሏል፡፡
 
‹‹ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ‹‹አሜሪካኖች በሱዳን ሕዝቡን ተክተው የበሽርን መንግሥት የማስወገድ ሚና ሊጫወቱ እንደማይገባ›› አጥብቀው ከማውሳታቸውም በላይ፣ የመንግሥት ለውጥ ወይም ግልበጣ ፖሊሲን ኢትዮጵያ እንደምትቃወም ደጋግመው ግልጽ አድርገዋል፡፡
 
ከውጭ የሚደረግ ማንኛውም የመንግሥት ግልበጣ ሱዳንን ብቻ ሳይሆን አካባቢያችንን የማተራመስ ውጤት እንደሚኖረው ጭምር የሚገነዘበው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ ከመልካም ጉርብትና ባሻገር በአጎራባች አገሮች የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ የመግባትም ሆነ ከሌሎች ጣልቃ ገቦች ጋር የመተባበር አቋም የለውም፤›› በማለት መግለጫው የኢትዮጵያ መንግሥን አቋም አስረድቷል፡፡

‹‹ኢትዮጵያም ሆነች ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የውጭ ኃይሎች ፕሬዚዳንት ኡመር አልበሽርን በዓለም አቀፍ የወንጀለኞት ፍርድ ቤት ከሰው ለማስቀጣት ያደረጉትን የተሳሳተ እንቅስቃሴ በጥብቅ ተቃውመዋል፡፡ በዚህም ሳይወሰኑ በአፍሪካ ላይ ማንኛውም ዓይነት የውጭ ሞዴል ለመጫን የሚደረገውን ጥረት እንደማይቀበሉ ደጋግመው አስታውቀዋል፡፡
 
በዊኪሊክስ በተለቀቀው ሪፖርት መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ከአሜሪካን መንግሥት ተወካዮች ጋር ዴሞክራሲን በተመለከተ ሐምሌ 2 ቀን 2001 .. ባደረጉት ውይይት ያላቸውን አቋም ሲያብራሩ፣ ‹‹የምዕራቡ ዓለም ዴሞክራሲና የልማት አቅጣጫ ከውጭ መጥቶ በሌሎች አገሮች ላይ በግድ ሊጫን የማይችልና የማይገባው ነው›› በማለት በአፅንኦት ገልጸዋል፡፡
 
በተጨማሪ በዚሁ በዊኪሊክስ ላይ ሪፖርት እንደተደረገው ‹‹የተባበረው የአሜሪካ መንግሥት የቆየ አቅጣጫ የተሳሳተና በአፍሪካ ውስጥ አገር በቀል ዴሞክራሲ እንዳይስፋፋ ዕድል የሚከለክል ነው፤›› በማለት ለአምባሳደሮቹ እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ መቼም ይሁን የትም ከውጭ የሚገፋን የመንግሥት ለውጥና ግልበጣን ደግፋ እንደማትቆም ያላትን አቋም ግልጽ ታደርጋለች፤›› ብሏል፡፡

‹‹ይህንን የመሰለ አቋም ያለው መንግሥት የአሜሪካን የመንግሥት ለውጥ ወይም ግልበጣ አቅጣጫ ከመቃወም በመለስ የመደገፍ ቅኝትም ሆነ ሙከራ ሊኖረው ይችላል ተብሎ አይጠበቅም፡፡  

ሊበሏት የፈለጓትን አሞራ እንደሚባለው በወቅቱ ሪፖርቱን ለአገራቸው መንግሥት ለማሳለፍ የቸኮሉትና የተጣደፉት አምባሳደር፣ ለመንግሥት ቅየራ ፖሊሲያቸው በጥድፊያ አጋር ሲያፈላልጉ የተነገረውን በደንብ ስላልተገነዘቡ ካልሆነ በስተቀር፣ ኢትዮጵያ የሱዳንንም ሆነ የየትኛውንም የጎረቤት አገር ሕዝብ በመተካት የመንግሥት ለውጥ ለማምጣት አስባ አታውቅም፤›› ሲል መግለጫው የዊኪሊክስን ሪፖርት አጣጥሏል፡፡
ሪፖርተር

Related topics:
 

No comments:

Post a Comment