Thursday, September 15, 2011

የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ጉባዔ በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ነው

(መስከረም 2 ቀን 2004 (አዲስ አበባ, ኢዜአ)--የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ጉባዔ ከትናንት ጀምሮ በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ነው።

ጉባዔውን ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ሊቃነ ጰጳሳት ዘኢትዮጵያና የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሲከፍቱ እንደተናገሩት ጉባዔው ዐብያተ ክርስቲያንን በሚመለከቱ ዓበይት ጉዳዮች ላይ በመነጋገር ጠቃሚ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል።

ኢትዮጵያ ያለችበት መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ ባህላዊ፣ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ እሴቶች በስፋት የሚንጸባረቁበት በመሆኑ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ስትራቴጂያዊ ጠቀሜታ እንዳለው አመልክተዋል።

አገሪቱ ለቀይ ባህር ባላት ቅርበት፣ የአባይ መነሻ በመሆኗ በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ባላት አቀማመጥ እምነቶች በአካባቢው አገሮች ካላቸው የረጅም ዘመናት ታሪክ ጋር ተዳምሮከፍተኛ ሥፍራ እንደሚያሰጧት ፓትርያርኩ መግለጻቸውን የኢ ዘገባ ያስረዳል።

ኢትዮጵያ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1948 የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ምክር ቤት አባል መሆኗንና በዚህም ለአፍሪካ ዐብያተ ኅብረት ምክር ቤት ምስረታ ዋነኛ መሠረት እንደሆነችም ገልጸዋል።

ኅብረቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቀጣዩን ጠቅላላ ጉባዔ ለማስተናገድ ያቀረበችውን ጥያቄ እንዲቀበል አቡነ ጳውሎስ ጠይቀዋል።

የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ዋና ፀሐፊ ዶክተር ኦላቭ ፍይክሴ ትቪዪት በበኩላቸው በእምነቱ የረጅም ዘመናት ታሪክ ያላት ኢትዮጵያ የምክር ቤቱን ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በማስተናገዷ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ምክር ቤቱ ዓለም የገጠሟትን የምሥራቅ አፍሪካን ድርቅና የሰሜናዊ አፍሪካ የፖለቲካ ቀውስ የመሳሰሉ ቸግሮችን በማንሳት በስፋት እንደሚወያይም አስታውቀዋል።

ዋና ፀሐፊው ለኢትዮጵያ ሕዝብ መልካም አዲስ ዓመት እንዲሆን ተመኝተዋል። የመላው አፍሪካ ዐብያተ ክርስቲያናት ኮንፍረንስ ዋና ፀሐፊ ዶክተር አንድሬ ካራማጋ የሰው ልጅ መገኛ በሆነችው አህጉር የሚካሄደው የምክር ቤቱ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ የምክር ቤቱን ሐይማኖታዊ ተልዕኮ ለመወጣት እንደሚያስችለው እምነታቸውን ገልጸዋል።

በዚህም የዛሬዋ ዓለም የምትፈልገውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመወጣት በሚደረገው እንቅስቃሴ ኮንፍረንሱ ድርሻውን ለማበርከት ዝግጁ መሆኑን ማረጋገጣቸውን የዘገበው የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ነው። የዓለም ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት 349 የሃይማኖት ተቋማት አሉት።
የኢትዩጵያ ፕሬስ ድርጅት

Related topics:
ለምሥራቅ አፍሪካ ለድርቅ ተጐጂዎች የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አስታወቀ  

No comments:

Post a Comment