Tuesday, January 13, 2015

ሜዳው ምቹ ነው፣ ፈረሳችሁን ኮርኩሩ (ክፍል አንድ)

ክፍል አንድ
(ጥር 4/2007, (አዲስ አበባ))--በኢትዮጵያ የተለያየ አመለካከትና አቋም ያላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፎ ወይም መድብለ ፓርቲ የኢፌዴሪ ስርአት መሰረት ነው። ከወታደራዊው ደርግ ውድቀት በኋላ አዲሲቷ ኢትዮጵያ የተመሰረተችው፣ ማለትም የአዲሲቱ ኢትዮጵያ መሰረት የተጣለው በአንድ ባላደራ ድርጅት ወይም ቡድን ሳይሆን የተለያየ አመለካከት ባላቸው ፓርቲዎች ነው። ይህ ሁኔታ የተለያየ ፓርቲዎችን ያሳተፈ ከኢፌዴሪ የመንግስት ስርአት አፈጣጠር ጋር የተቆራኘ የስርአቱ ምንነት መገለጫ መሆኑን ያመለክታል።

ግንቦት 1983 የመጨረሻው የአሃዳዊ የመንግስት ስርአት፣ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ባካሄዱት መራራ ትግል ከተገረሰሰ በኋላ፣ አዲስ የመንግስት ስርአት የመመስረቱን ኃላፊነት የወሰደውን የሽግግር መንግስት ስልጣን የተረከበው አንድ ቡድን ወይም ፓርቲ አልነበረም። ከዚህ ይልቅ አምባገነኑን የደርግ ስርአት ለማስወገድ የትጥቅ ትግል ሲያካሂዱ የነበሩ ሁሉም የነፃነት ንቅናቄዎች፣ እንዲሁም በውጭ ሃገራት የተቃውሞ እንቅስቃሴ ላይ የነበሩ በተለያየ አመለካከት የተደራጁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነበሩ።

ደርግ በተወገደ በአንድ ወር ያህል ጊዜ ውስጥ ሁሉም በሀገር ቤትና በውጭ ሀገራት የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች በአዲሲቱ ኢትዮጵያ መፃኢ እጣ ፈንታ ላይ ለመወሰን በአንድ አዳራሽ ታደሙ። ብሄራዊ የነፃነት ጥያቄ አንስተው ሲታገሉ የነበሩት ጭምር፣ ከመበታተን ይልቅ መብትና ነፃነታቸው ተከብሮ አብረው መኖር የሚችሉበት እድል ይኖር እንደሆነ በመምከር የኢትዮጵያን መፃኢ እጣ ፈንታ ለመወሰን የተጠራው ጉባኤ ታዳሚዎች ነበሩ።

ታዲያ የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ ለመወሰን የተሰባሰቡት የሀገሪቱ ፓርቲዎች አብዛኞቹ በብሄር ላይ ተመስረተው የተደራጁና ለብሄራዊ ነፃነት የትጥቅ ትግል ሲያካሂዱ የነበሩ ናቸው። የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ብሄራዊ መብትና ነፃነት፣ የፖለቲካ መብቶች፣ ሰብአዊ መብቶች በህገመንግስት የተረጋገጡባት ሁሉም በእኩልነት መኖር የሚችሉባት ሀገር ለመመስረት ተስማሙ። ወደዚህ መብቶችና ነፃነቶች ተከብረው በእኩልነት የሚኖሩበት ስርአት የሚያሸጋግራቸው የሽግግር መንግስት መሰረቱ። ሁሉም በሰኔ 1983ቱ ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ ካለማንም ውጪያዊ አካል ጣልቃ ገብነት ለመወሰን የተስማሙ ፓርቲዎች የሽግግር መንግስቱ አባላት ነበሩ።

ሁሉም ፓርቲዎች፣ በሚወክሉት ህዝብ ብዛትና የደርግን ስርአት ለማስወገድ በተደረገው ትግል ውስጥ ባበረከቱት አስተዋፅኦ ልክ የሽግግር መንግስቱ ትልቁ የስልጣን አካል በነበረው የተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ መቀመጫዎች - ስልጣን ነበራቸው። በዚህ የሽግግር መንግስት ውስጥ እንደ አንድ ፓርቲ ከፍተኛ መቀመጫ አግኝቶ የነበረው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ነበር። እርግጥ ኦነግ ሁሉም የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ራሳቸውን በራሳቸው እያስተዳደሩ ከሌሎች ጋር በእኩልነት የሚኖሩበት ሀገር የመመስረቱን ኃላፊነት ጥሎ ራሱን ከሽግግር መንግስቱ አግልሎ እንደነበር ይታወሳል።

ከኦነግ በስተቀር የተቀሩት የሽግግር መንግስቱ አባላት ድርጅቶች፣ የሽግግር መንግስቱ ዋነኛ ዓላማ የነበረውን ህገመንግስት የማዘጋጀት ስራ በታላቅ የህዝብ ተሳትፎ ተወጥተዋል። በዚህ ሕገመንግስት መሰረት አዲሲቱ ኢትዮጵያ - የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ተመስርታለች። በፅሁፌ መግቢያ ላይ መድብለ ፓርቲ ስርአት በህገመንግስት የተረጋገጠ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያ የተመሰረተችበትና ከምንነቷ የማይነጠል የተፈጥሮ መለያ ነው ያልኩት በዚህ ምክንያት ነው። እንግዲህ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ከኢትዮጵያ ጋር ያለው የባህሪ ቁርኝት ይህን ይመስላል።

የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት መሠረት የአመለካከትና ሃሳብን በነፃ የመያዝና የመግለፅ፣ የመደራጀት እንዲሁም የመምረጥና የመመረጥ መብቶችና ነፃነቶች ናቸው። ከመረቀቅ እስከመፅደቅ ያለው ሂደቱ የተለያየ አመለካከት ያላቸውን ፓርቲዎችና ምልአተ ህዝቡን በቀጥታ ያሳተፈው የኢፌዴሪ ህገ መንግስት እነዚህን መብቶች አረጋግጧል።

ዜጎች ያመኑበትንና የፈቀዱትን አመለካከት የመያዝ፣ አመለካከታቸውን የመግለፅ መብታቸው ባልተከበረበት ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ሊኖር አይችልም። የመድብለ ፓርቲ ስርአት ዋነኛ መሰረት የአመለካከት ነፃነት ነው። በኢትዮጵያ በዘውዳዊውና በወታደራዊ ደርግ የመንግስት ስርአቶች፣ ዜጎች የፈለጉትን አመለካከት የመያዝ መብት አልነበራቸውም። ወታደራዊው ደርግም ስርአቱ እከተለዋለሁ ብሎ ካወጀው ርዕዮተ ዓለም የተለየ አመለካከት ይዞ መገኘት፣ ርዕዮተ አለሙን መቃወም ወይም መተቸት የተከለከለ ነበር። ይህን አድርገው የተገኙ ወይም “አድርገዋል” ተበለው የተጠረጠሩ ሰዎች ይቀጣሉ። የተለየ አመለካከት በመያዛቸውና ይዘዋል ተብለው በመጠርጠራቸው ብቻ በርካታ ኢትዮጵያውያን ያልፍርድ ቤት ውሳኔ ለአመታት በዕስር ማቀዋል፤ ተገድለዋል። እናም የአመለካከት ነፃነት ባልተከበረባቸው ዘውዳዊና ወታደራዊ የመንግስት ስርአቶች የተለያየ አመለካከት ላይ የተመሰረቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች አልነበሩም - የመድብለ ፓርቲ ስርአት የሚባል ነገር አልነበረም።

ለመድብለ ፓርቲ ስርአት መኖር ከአመለካከት ነፃነት በተጨማሪ የመደራጀት መብት መረጋገጥን ይፈልጋል። የመደራጀት መብት በሌለበት ሁኔታ አመለካከትን ማራመድ፣ አባላትና ተከታዮች፣ ደጋፊ ማፍራት የማይታሰብ ነው። የኢፌዴሪ ህገመንግስት የመደራጀት መብትን አረጋግጧል። በህገመንግስቱ አንቀፅ 31 “የመደራጀት መብት” በሚል ርዕሰ ስር፤ ማንኛውም ሰው ለማንኛውም ዓላማ በማኅበር የመደራጀት መብት አለው፡፡ ሆኖም አግባብ ያለውን ሕግ በመጣስ ወይም ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በሕገ ወጥ መንገድ ለማፍረስ የተመሰረቱ ወይም የተጠቀሱትን ተግባራት የሚያራምዱ ድርጅቶች የተከለከሉ ይሆናሉ ተብሎ ተደንግጓል፡፡ ያመኑበትን አመለካከት የመያዝ መብት ያላቸው ዜጎች አመለካከታቸውን ለማራመድ መደራጀት ይኖርባቸዋል።

በዚህ መሰረት የተለያየ አመለካከት ያላቸው ኢትዮጵያውያን ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በሀገሪቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የፖለቲካ ፓርቲዎችን አደራጀተዋል። በአሁኑ ጊዜ በፌዴራልና በክልል መንግስታት ደረጃ የሚንቀሳቀሱ ከ70 በላይ ህጋዊ እውቅና ያላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች በሀገሪቱ ይንቀሳቀሳሉ። በዘንድሮው ምርጫ 60 ገደማ ፓርቲዎች በክልልና በሀገር አቀፍ ደረጃ ይወዳደራሉ።

ያመኑበትን አመለካከት መያዝና መደራጀትም በራሱ መድረሻ አይደለም። መድረሻው በአመለካከት ለፖለቲካ ስልጣን ተፎካክሮ በህዝብ ውክልና የመንግስት ስልጣን መረከብ መቻል ነው። ይህ ደግሞ ከመደራጀትም ባሻገር የመመረጥና የመምረጥ መብት መከበርን ይሻል። የኢፌዴሪ ህገመንግስት የመምረጥና የመመረጥ መብትንም አረጋግጧል። በኢፌዴሪ ህገመንግስት አንቀፅ 38 ላይ።

በዚህ በህገመንግስት በተረጋገጠው የመምረጥና የመመረጥ ሕገመንግስታዊ መብት ዜጎች ባቋቋሙትና አባል በሆኑበት የፖለቲካ ፓርቲዎች ውስጥ የፓርቲያቸው ሕገ ደንብ በሚያዘው መሰረት ለአመራርነት እየተወዳደሩ ሲመረጡ ቆይተዋል። ከዚሀ በተጨማሪ ፓርቲያቸውን በመወከልና በግላቸው ከቀበሌ እስከ ፌዴራል መንግስት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልነት ድረስ ውክልና ለማግኘት ሲወዳደሩና ሲወከሉ ቆየተዋል። መራጭ ዜጎችም በየደረጃው አማራጭ ይዘው ከቀረቡላቸው እጩ ተወካዮች መካከል ይጥቅመኛል ያሉትን እየመረጡ ውክልና ሲሰጡ ቆይተዋል።

ባለፉት ሃያ ዓመታት በተካሄዱት አራት ሀገራዊ ምርጫዎች ላይ በተለያየ አመለካከት የተደራጁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተወዳድረው በክልልና በፌዴራል መንግስት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶች ውስጥ የስልጣን ውክልና አግኝተዋል። በተለይ በ1997 ዓ.ም በተካሄደው 3ኛው ዙር ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለይ በፌዴራል መንግስት እንዲሁም በኦሮሚያና በአማራ ክልላዊ መንግስታት ውስጥ ከፍተኛ የስልጣን ውክልና መቀመጫዎችን ማግኘታቸው ይታወሳል። በ97ቱ 3ኛ ዙር ሀገራዊ ምርጫ በፌዴራል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከሚገኘው አጠቃላይ 547 መቀመጫዎች ኢህአዴግ እና አጋር ድርጅቶች አብላጫ መቀመጫ አግኝተው መንግስት መመስረት ቢችሉም ቅንጅት ለዴሞክራሲና ለፍትህ እንዲሁም የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ሕብረት በመቶዎች የሚቆጠሩ መቀመጫዎችን አግኝተው እንደነበረ ይታወቃል። ይህ ከዚያ ቀደም ከተካሄዱት ሁለት ምርጫዎች፣ ተቃዋሚዎች በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያላቸው ድርሻ እያደገ መምጣቱን ያመለክታል። ይህም የሀገሪቱ ዴሞክራሲ በአጭር ጊዜ ውስጥ መጎልበቱን ያመለክታል።

ይሁን እንጂ የቀድሞው ቅንጅት ሕዝብ በፌዴራል መንግስት ውስጥ ሕዝብ የሰጠውን ስልጣን ያጋራ ከፍተኛ ቁጥር ያለው መቀመጫ እንዲሁም አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉ የማስተዳደር የስልጣን ውክልና መቀበል አሻፈረኝ አለ። በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተገኘውን የስልጣን ውክልና አሻፈረኝ ብሎ ኢ-ዴሞክራሲያዊ በሆነ የኃይል መንገድ ስልጣን ለመመንተፍ ተንቀሳቀሰ። ስልጣን በውክልና የሰጡት ደጋፊዎቹ አደባባይ ወጥተው በማመፅ ስልጣን እንዲመነትፉለት የአመፅ ጥሪ አስተላለፈ። ሆኖም እንዳሰበው የመረጠው ህዝብ ሁሉ መንግስት ለመገልበጥ ‘ሆ’ ብሎ አደባባይ አልወጣም። ከዚህ ይልቅ በተመረጠባቸው አዲሰ አበባና አንዳንድ የሃገሪቱ ትላልቅ ከተሞች ደጋፊዎቹ ወጥተው ሁከት ቀሰቀሱ። ይህ ሁከት ሰላም በማስከበር ስራ ላይ ለተሰማሩ፣ እንዲሁም በቅንጅቱ ውዥንብር ተደናግረው ለሁከት አደባባይ ለወጡ ንፁሃን ዜጎችህይወት መጥፋት፣ አካል መጉደል ምክንያት ቢሆንም ጥቂቶች ከተሳተፉበት የጎዳና ላይ ሁከትነት ሳያልፍ ከሰመ።


ይህን ተከትሎ አዲስ አበባን ለማስተዳደር መረከብ የሚያስችል ቁጥር ያላቸው የቅንጅት አመራሮች ሳይገኙ ይቀራሉ። በፌዴራል መንግስት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥም ቢሆን ፓርቲው አሸንፎ ከነበራቸው መቀመጫዎች መካከል የተወሰኑት ብቻ የምክር ቤት መቀመጫቸውን ሲቀበሉ የተቀሩት ከውክልናው ውጪ ሆኑ። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በሃይል ለመናድ ሴራ የጠነሰሱትና ሁከቱን የመሩት የቅንጅት አመራሮች ላይ ክስ ተመስርቶ እንደነበረ እናስታውሳለን። አመራሮቹና አባላቱ አቃቤ ሕግ ያቀረበባቸውን የጥፋተኝነት ማስረጃ መከላከል ስላልቻሉ በተከሰሱበት ወንጀል ጥፋተኛ ተብለው ቅጣት ይወሰንባቸዋል። ይሁን እንጂ ቅጣት ከተወሰነባቸው በኋላ ጥፋተኝነታቸውን አምነው፣ ሕዝብና መንግስት ይቅርታ እንዲያደርጉላቸው ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት የይቅርታ ህግ በሚፈቅደው መሰረት ቅጣታቸው ተነስቶላቸው ነፃ ይወጣሉ።

አመራሮቹ ከእስር ሲወጡ፣ ቅንጅት የሚባለው ስብስብ በውስጡ በተፈጠረ አለመተማመንና አለመግባባት ተበትኖ ስለነበረና መልሶ ቅንጅቱን መፍጠር ስላልተቻለ ከእስር ነፃ የወጡት የቀድሞ ቅንጅት አመራሮችና አባላት ገሚሶቹ ወደእናት ፓርቲያቸው ሲመለሱ፣ የተቀሩት ደግሞ አዲስ ፓርቲ መሰረቱ። አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ የተሰኘው ፓርቲ የተፈረካከሰው የቀድሞ ቅንጅት አመራሮች ከመሰረቷቸው አዲስ ፓርቲዎች መካከል አንዱ ነው። ከተፈቱት የቀድሞው ቅንጅት አመራሮች መካከል ከሀገር የኮበለሉም አሉ። የተወሰኑት ግንቦት 7 በሚል ቡድን ተደራጅተው የኤርትራው ሻአቢያ ጉያ ስር ተወሽቀው በሽብር ጥቃት ህገመንግስታዊ ስርአቱን ለመናድ አውጀው ይህን እናሳካለን ብለው እየጣሩ ነው።

ይሁን እንጂ ከቀደሞው ቅንጅት መፈረካከስ በኋላ የተመሰረቱም ሆኑ ነባሮቹ ፓርቲዎች ጠንካራ ተፎካካሪ ሆነው መውጣት አልቻሉም። ከዚህ ይልቅ በአመራሮቹ መካከል እስከአሁን ድረስ ያለማቋረጥ በሚቀሰቀስ አለመግባባትና ውዝግብ እየተናጡ አቋማቸው በግልፅ የማይታወቅ ኮሳሳ ፓርቲዎች ሆነው ወጡ። በውስጣቸው የሚፈጠረውን አለመግባባት በዴሞክራሲያዊ መንገድ መፍታት ባለመቻላቸው በአመራሮቹ መካከል የሚነሳ ሹክቻ በዱላና በድንጋይ እስከመፈናከት የዘለቀ የዘቀጠ ሁኔታ ፈጥሮ እንደነበርም አስተውለናል። ይህ ሁኔታ በአጠቃላይ የተቃዋሚው ጎራ ከህዝብ ልብ እንዲርቅ አድርጓል።

በሌላ በኩል ኢህአዴግ ቀደመ ሲል ስራ ላይ ያዋላቸውና እስከ 1997 ዓ.ም በነበሩት ዓመታት ያልታዩ የገጠር ልማት ፖሊሲዎቹ እንዲሁም የከተማ ስራ አጥነትን ለማቃለል የተከተላቸው የአነስተኛና ጥቃቅን ተቋማት ልማት ሥራዎች ፍሬ አፍርተው በተጨባጭ ፋይዳ ያለው ሊተገበር የሚችል ፖሊሲ ያለው መሆኑን ህዝብ ተረዳው። ቀደም ሲል “ስራዬ ይናገራል” በሚል የዋህነት ችላ ብሎት ለነበረው የህዝብ ግንኙነት ስራ ትኩረት መስጠቱም ማንነቱን በስፋት ማሳወቅ አስችሎታል። ድርጅታዊ ቁመናውንም፣ አባላትን በማበራከት አጠናከረ። ከአምስት መቶ ሺ የማይበልጡ የነበሩ አባላትን ወደ ሚሊዮኖች አሳደገ። ከዚሁ ጎን ለጎን ቀደም ሲል ትኩረት ላልሰጣቸው ጉዳዮችና አካባቢዎች ትኩረት በመስጠት የደጋፊዎቹን ቁጥር ማሳደግ ቻለ።

በዚህ አኳኋን ተቃዋሚዎቹ ቁልቁል ሲወርዱ በሌላ በኩል ኢህአዴግ ሽቅብ እየተመነደገ ነበር ምርጫ 2002 ላይ የተገናኙት። በዚህ ምክንያት ኢህአዴግ ከምርጫው በፊት ከጠበቀው በላይ በከፍተኛ ድምፅ ተቃዋሚዎቹን ማሸነፍ ቻለ። በ2002 ምርጫ የነበረው የፖለቲካ ምህዳር ሰፊና የተደላደለ የነበረ ቢሆንም፤ ተቀዋሚዎቹና ኢህአዴግ የነበራቸው ጥንካሬ፣ ተጨባጭ የፖሊሲ አማራጭ፣ የአባላትና የደጋፊ ብዛት የሰማይና የምድር ያህል የተራራቀ ስለነበረ ፉክክራቸው የአንበሳና የጥንቸል ትግልን ያህል ነበር። በ2002 ምርጫ ኢህአዴግ በሰፊ ልዩነት ያሸነፈበት ምስጢር ይሄው ነው።

እናም ሊፎካከሩት ከቀረቡት ጋር ሲነፃፀረ እጅግ ብርቱ የነበረው ኢህአዴግ በተወዳደረባቸው አዲሰ አበባ፣ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይ፣ ደቡብ ክልሎች ከሁለት በስተቀር ሁሉንም መቀመጫዎች አሸነፈ። በአዲስ አበባ የአንድነት ተወካይ አቶ ግርማ ሰይፉ ሲያሸንፉ በደቡብ ቦንጋ ከተማ ላይ ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ በግል ተወዳድረው ማሸነፍ ችለዋል። በሃራሬ ክልል ከነበሩት ሁለት መቀመጫዎች አንዱን፤ በድሬዳዋ ከነበሩት ሶስት መቀመጫዎች አንዱን አሸንፏል።

 በእነዚህ የምርጫ ክልሎች የተቀሩትን መቀመጫዎች አጋር ድርጅቶቹ የሃራሬ ብሄራዊ ሊግ (ሃብሊ) እና የሶማሌ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ሶሕዴፓ) አሸንፈዋል። በተቀሩት ክልሎች፤ በሶማሌ፣ በአፋር፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በጋምቤላ አጋር ድርጅቶቹ ሶህዴፓ፣ አብዴፓ፣ ቤግህዴፓ፣ ጋሕዴን ሙሉ በሙሉ አሸነፉ። በዚህም ኢህአዴግ ከነአጋር ድርጅቶቹ 99.6 በመቶ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎችን አሸነፈ። በዚህም በመድብለ ፓርቲ ስርአት ውስጥ አውራ ፓርቲ (dominant) ሆኖ ለመውጣት በቅቷል።

አሁን 5ኛው ዙር ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ ሊካሄድ ከአምስት ወራት በታች የሆነ ጊዜ ቀርቶታል። በዚህ ምርጫ ላይ ለመፎካከር 60 የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ምልክታቸውን ወስደው እጩ ተወዳ ዳሪዎቻቸውን በማስመዝገብ ላይ ይገኛሉ። ከአንድ ወር በኋላ የምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ ይጀምራሉ።

ይሁን እንጂ አሁንም ከምርጫ 2002 በፊትና በምርጫው ላይ የተስተዋሉት ነገሮች ይታያሉ። “አሉ” የሚባሉት ፓርቲዎች በአመራር ሹክቻ ውስጥ ናቸው። ሹክቻው በሰላማዊ መንገድ እልባት ማግኘት ስላልቻለ፣ ተሿካቾቹ አመራሮች በየወገናቸው ደጋፊ አሰባስበው የስልጣን ሹም ሽር አድርገዋል። ይህን “ህገወጥ መፈንቅለ ስልጣን ነው” ያሉትም አሉ። ይህ ሹክቻ ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድም አስቸጋሪ ሁኔታን ፈጥሮ እንደነበረ እናስታውሳለን።

ለምሳሌ ምርጫ ቦርድ በአንድነትና በመኢአድ አመራሮች መካከል በተፈጠረ አለመግባባት አንዱ የአመራር ወገን ሌላውን “ህገወጥ ነው፤ አልቀበልም” በማለቱ ምክንያት የምርጫ ምልክታቸውን ለመመዝገብ ተቸግሮ እንደነበረ እናስታውሳለን። እስከአሁን ቦርድ ችግራቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ እንዲፈቱ እየመከረ ነው። እንግዲህ በዚህ ንቁሪያና ሹኩቻ ውስጥ የት ይደርስ ይሆን!? ሕዝባዊ ኃላፊነት አለብኝ የሚል የፖለቲካ ኃይል ሁሉ ራሱን መፈተሽ ያለበት ጥያቄ ነው።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment