Tuesday, March 11, 2014

ስደት የውርደት ምልክት

(Mar 11, 2014, (አዲስ አበባ)--ስለ ስደት ለማውራትም ይሁን ለመጻፍ ብዕራችንን ስናነሳ ምናልባትም በዚያች ቅፅበት ውስጥ እንኳን ምን ያህሉ ሕዝብ በየብስ በበረሃ ሐሩር ከባህር ማዕበልና ከበረሃው አውሎ ነፋስ ጋር ምንኛ ትግል ውስጥ እንዳለ በምናባችንና በእዝነ ልቦናችን ማሰባችን አይቀርም፡፡ አዳምና ሔዋን አትብሉ የተባሉትን ዕፀ-በለስ በሥልጣናቸውና በፈቃዳቸው በሉ ! የስደት ሀሁ የጀመረው ከእዚህ ይሆን እስራኤል ዘነፍስ በግብፅ በባርነት በስደት ኖሩ ( ሙሴ እየመራ ነፃ እስኪያወጣቸው ድረስ ) የስደት ሁነኛ መነሻ ውሉ የቱ ይሆን? ለነገሩማ ማጣፊያ የሌለው ባዘቶ ምንስ ውል አለውና? ይሁን እንጂ አስኳላ ቀለም ስቀስም ያነበብኳትን ለዛሬ ፅሑፌ ትሆነኝ ዘንድ የመረጥኳት መነሾ በምናውቀውና ሁላችንንም ሊያግባባን በሚችል ቋንቋ የስደትን የመነሻ ጥግ ሊያመለክተን ይችል ይሆናል ብዬ አሰብኩና ጀመርኩ፡፡

አውሮፓ፡- አውሮፓ በአፍሪካ ጫንቃ ላይ የእድገት ቀንበሯን ከጫነችበት እንደጐርጐሪዮሳውያኑ የዘመን ቀመር 1870 ጀምሮ አህጉሪቱን ወደ ዘመናዊው የእድገት ማማ ጫፍ ለማቆናጠጥ ሲሉ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ የአፍሪካ ብርቅዬ ልጆች የስደት ጽዋን በፍላጎታቸው ሳይሆን በግዴታቸው ሲቀምሱ ቆይተዋል፡፡ በመሆኑም አውሮፓውያኑ የአፍሪካውያኑን ጉልበት በፈለጉት የሥራ መስክ ያለምንም ሰብዓዊነት ሲገለገለቡት ቆይተዋል፡፡ ይህ ሂደት እስከ ኢንዱስትሪ አብዮት ድረስ ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ ብዙ አፍሪካውያንን ሰለባ አድርጓል፡፡ በተለያዩ የአውሮፓ ከተሞች በመቀጣጠል ላይ የነበረው የኢንዱስትሪ አብዮት በመጠኑም ቢሆን የሰውን ጉልበት በተለያዩ ማሽኖች መተካት የቻለ በመሆኑ በአፍሪካውያኑ ላይ የነበረውን ጫና ለመቀነስ አስችሎ ነበር፡፡ ከኢንዱስትሪው አብዮት ጋር ተያይዞ እ.አ.አ. በ1887 ዓ.ም በእንግሊዝ መንግሥት አማካኝነት ለመጀመሪያ ጊዜ ተደንግጐ የነበረው የፀረ-ባርነት ሕግ በሥራ ላይ መዋል ጀምሮ የነበረ መሆኑም የአፍሪካውያንን በደል በመቀነሱ ረገድ ጉልህ አስተዋፅኦ ነበረው ለማለት ያስችላል ፡፡ ልብ በሉ ይህ የፀረ-ባርነት ሕግ ከወጣ ወደ 200 ዓመት ገደማ ሆነው ማለት ነው፡፡

ሃያ አንደኛው ክፍል ዘመን ፡- አሁን በምንገኝበት የ 21ኛው ክፍል ዘመን ከ200 ዓመታት በፊት ከነበረው ባርነት ባልተናነሰ መልኩ ስደት ዘመናዊ ካባውን ደርቦ በብዙኃኑ የህብረተሰብ ክፍል ልብ ውስጥ ሰተት ብሎ ገብቷል ማለት ይቻላል። ሰው ሁሉ አካባቢውን በአግባቡ መቃኘት እስኪያቅተው ድረስ ህሊናውን ሰውሮ የያዘ ጉዳይም ሆኗል። ሰው በአገሩ ከወገኑ ጋር አብሮ መቸገርን፣ ተባብሮ ችግርን ማሸነፍን፣ የአገሩን ሀብት በጥቅም ላይ ማዋልን አሸፈረኝ አለ ፡፡ ስደት... ስደት... ስደትን የሁልጊዜውም አማራጩ አደረገ ፡፡ በእርግጥ ስደት በተለያዩ ምክንያቶች ሊከሰት ይችላል፡፡ በድርቅ፣ በጦርነትና በግጭት፣ በተፈጥሮ ሰው ሰራሽ አደጋዎች ወዘተ...... ግን የእኛ ከየትኛው ይመደብ ይሆን? ብሎ መፈተሽ ከመንግሥትና ዜጎች የሚጠበቅ ይመስለኛል።

አፍሪካ፡- በእዚህ ክፍለ ዘመን በአፍሪካ ያለው የስደት መጠን በየትኛውም ዓለም ካለው የስደት መጠን እጅጉን ይለያል፡ ፡ ምክንያቱን ስንመለከት በድርቅ ወይም በጦርነት አልያም በኢኮኖሚ ስደትና ሳቢያ የሚፈጸም ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የሚከሰተው ስደት ግን የእርስ በእርስ ጦርነትን መነሻ ያደረገ ሆኖ ይታያል፡፡ ታዲያ አፍሪካና ሕዝቦቿ ይህን ችግር ለማየት ለምንስ ተሳናቸው? በራሳቸው ጉዳይ ላይ ተባብረው ለመሥራትስ ምነው አቅም አጠራቸው? የተማረ የሰው ኃይል? ዘመናዊ ቴክኖሎጂ? የተፈጥሮ ሀብት እጥረት? ካፒታል ምንድነው ያጠራቸው? አፍሪካውያን የራሳቸውን ዕድል በራሳቸው ለመወሰን ይረዳቸው ዘንድ በአንድ ጥላ ስር መሰባሰባቸውን! በሁለት ዓመት አንዴ እንደአስፈላጊነቱም በተለያዩ ጊዜያቶች ሲመካከሩም ይስተዋላል፡፡ ድምር ውጤቱ ገና የሚያጠግብ ነው ባይባልም ጅምሩ አለ።

ስደት የተለያዩ መጥፎ ገፅታዎች አሉት፡፡ አሉታዊ የሆኑ ጐኖቹም ይበዛሉ። ስደት በፈጠረው ጣጣ የሰው ልጆች ከተሰጣቸው ክብር ተዋርደው እንደ ሸቀጥ ከአንዱ አገር ወደሌላኛው ተላልፈው እየተሸጡና እየተለወጡ ይገኛሉ፡፡ የአሁኑን ወይም የእዚህን ክፍለ ዘመን የስደት ሁኔታ ለየት የሚያደርገው ዘመናዊ መሆኑ ብቻ ነው፡፡ የተለያዩ ምሁራንና የሚመለከታቸው ተቋማት ከስደት ጋር በተያያዘ የተለያዩ ጥናቶችን በተለይ በሴቶችና በሕፃናት ላይ በማድረግ መንስኤና ውጤቶችን እንዲሁም መፍትሔ ይሆናል ያሉትን ሃሳብ ሲያስቀምጡ ቆይተዋል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህን ጥናቶች ተመስርቶ የተለያዩ ተግባራትን ከማከናወን ይልቅ ጥናቶቹ የላይብራሪ መደርደሪያዎችን ማሞቂያ ሲሆኑ የታያል፡፡ የሚታዩና የሚጨበጡ ውጤቶች ባለመኖራቸውም በሕገ-ወጥ መንገድ ተላልፈው የሚሸጡ ሴቶች፣ሕፃናትና ወጣቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየተበራከተ ይገኛል፡፡

ኢትዮጵያ፡- አገራችን ኢትዮጵያም ልክ እንደ ሌሎቹ የአፍሪካ ሀገራት ሁሉ የእዚህ ችግር ሰለባ ናት፡፡ ልዩነቱ በእኛ አገር የሚከሰተው የስደት ችግር መነሻው የእርስ በርስ ግጭትና ጦርነት ሳይሆን አሁን ካለንበት የዕድገት ዘመን ጋር በተያያዘ የተሻለ ሕይወት ለመኖር ከመፈለግ የሚመነጭ ነው። በመሠረቱ የሰው ልጅ ፍላጎት ማብቂያ የሌለው በመሆኑ የተሻለ ሕይወትን መፈለጉ ምንም ኃጢያት የለውም ችግሩ የሚጀምረው ግን ሕገ - ወጥነትን በተላበሰ መልኩ ለመሰደድ መመኘት የተጀመረ ጊዜ ነው፡፡

በሌላ በኩል በዕደጉት አገራት አካባቢ የተመቻቸ የሥራ አካባቢና በቂ የሆነ የሥራ ክፍያ ይኖራል የሚል የተዛባና የተጋነነ አመለካከት በህብረተሰባችን ውስጥ በስፋት ተንሰራፍቶ ይገኛል። በእዚህም አብዛኛው ህብረተሰብ ማለት በሚቻልበት ሁኔታ በአገር ቤት ካሉት ችግሮች ጋር ተጋፋጦ ከመሥራትና ለመለወጥ ከማሰብ ይልቅ ቤተሰቡም ይሁን እራሱ የቋጠራትን ጥሪት ለደላላ ሰጥቶ መንጎድን ይፈልጋል። ካለመውም ሳይደርስ በበረሃ የአውሬ ሲሳይ ሲሆን፤ዕድል የቀናውም በሰው አገር በሰቀቀን ሕይወቱን ሲገፋም ይኖራል፡፡ በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ የመዳረሻ አገሮች በተለያዩ የሥራ መስኮች ተሰማርተው ካሉ ሴት ኢትዮጵያውያን መካከል ብዙዎቹ የእዚህ ችግር ተጠቂዎች በመሆናቸው ሥነ-ልቦናዊ ፣አካላዊ እና ጾታዊ ጥቃቶች እንዲሁም የጉልበት ብዝበዛ እና ሌሎችም ዓይነት በደሎች ይደርስባቸዋል፡፡

በቅርቡ በሳውዲአረብያ በሚኖሩ ዜጎቻችን ላይ ተፈፅሞ የነበረውም ድርጊት የእዚሁ ችግር ማሳያ ነው፡፡ ምንም እንኳን በሳውድአረቢያ ችግሩ ጐልቶ ይውጣ እንጂ በሌሎች የአረብ አገራት በሚኖሩ ዜጎቻችን ላይ በድብቅ የሚፈፀሙ ወንጀሎች የትየለሌ ናቸው፡፡ በመሆኑም በመንግሥት በኩል ችግሩን ለመፍታት የተጀመሩ ጥረቶች መልካም ቢሆኑም የችግሩን ስፋት ተረድቶ የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴ ግን አሁንም ቢሆን ይቀረዋል፡፡ መንግስሥ የዜጎችን ደህንነት የመጠበቅ ኃላፊነት ያለበት ከመሆኑ ጋር ተያይዞም በሳውድአረቢያ በዜጐቻችን ላይ የደረሰው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊትን እስከመጨረሻው ድረስ ገፍቶ በመጠየቅ በኩልም የተካሄደው ርቀት አጥጋቢ አይደለም፡፡ ስለሆነም የሚመለከተው አካል በሙሉ ዜጎችን ወደ አገራቸው ለመመለስ ያላሰለሰ ጥረትና ርብርብ ያደረገውን ያህል የተፈፀመውን ድርጊት በማጣራቱና ለሕዝብ ይፋ በማድረጉ ረገድም ቢሆን የቤት ሥራውን መወጣት ይኖርበታል።

በአጠቃላይ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ስደትን የመጨረሻ አማራጩ ከማድረግ ይልቅ በእናት አገሩ ሠርቶ መለወጥን ብሎም መበልጸግን መሪ ዓላማው ቢያደርግ ይበጃል። በአገራችን ያለውና እየተፈጠረ ያለው ምቹ ሁኔታም ለእዚህ የሚጋብዝ እንደሆነ ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ መንግሥትም ቢሆን በመዋቅሩ የሚታየውን የመልካም አስተዳደር ችግር በመፍታት ለሥራ ወደ ውጭ አገር ለመሄድ የሚፈልጉ ዜጎች በሚሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ተፈላጊ ሙያና ክህሎት እንዲኖራቸው ማድረግ አለበት።

ስለሚሄዱበት አገር ትክክለኛ መረጃ አገኝተው በራሳቸው ፍላጎትና ውሳኔ ሕጋዊ መንገድን ተከትለው በመሄዳቸው ሊያገኙ የሚችሉትን ጥቅም ማሳየትም ተገቢ ነው። በተለይ በሕገ-ወጥ መንገድ ለመሄድ መሞከር ያለውን የመብት ጥሰትና በደል በሚገባ በማስተማር ኃላፊነቱን መወጣት አለበት፡፡ በሌላ በኩል አጠቃላይ የኢኮኖሚ ሁኔታው ሥራ አጥነትንና ሌሎች ማህበራዊ ችግሮችን መፍታት በሚችልበት ማዕቀፍ ውስጥ እንዲሽከረከር ማደረግ አለበት፡፡ እርግጥ እዚህ ላይ ባለሀብቶች መላው ሕዝብና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም የየድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል።
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment