Friday, June 14, 2013

ተቃዋሚ ፓርቲዎች በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ የያዙት አቋም በተግባርም ሊገለጽ ይገባል

(June 13, 2013, (አዲስ አበባ))--ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ያላትን ፍትሐዊ መብት በመጠቀም  የታላቁን የህዳሴ ግድብ  በሕዝቦቿ የጋራ ክንድ  በመገንባት ላይ ትገኛለች ።  ከተጀመረ ከሁለት ዓመት በላይ ያስቆጠረው የግደቡ ሥራ ሰሞኑን ወደ አዲስ ምዕራፍ ተሸጋግሯል ። 

የአባይ ወንዘ ለግንባታው አመቺነት ሲባል በሌላ አቅጣጫ እንዲፈስ ተደርጓል ። ከእዚሁ ጎን ለጎን የግድቡ ግንባታ በግብፅና በሱዳን ላይ ሊያደርስ የሚችለውን ተፅእኖ እንዲያጠና የተቋቋመው የባለሙያዎች ግብረ ኃይል በሦስቱም አገራት በመዘዋወር ሲያካሂድ የነበረውን ጥናት አጠናቅቆ ግድቡ በታችኞቹ የተፋሰሱ አገራት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እንደማይኖረው የሚያሳየውን ሪፖርቱን ይፋ አድርጓል ።

እነዚህን ወቅታዊ ሁነቶች   ተከትሎ የግብፅ ፕሬዚዳንት ከአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ከባለሥልጣናትና ከሃይማኖት መሪዎች ጋር ባደረጉት ውይይት በኢትዮጵያ ያሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በማጠናከር የግድቡ ግንባታ እንዲስተጓጎል ማድረግ ይቻላል የሚል ሃሳብ አንፀባርቀዋል። ይህን አመለካከት በአገር ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እያወገዙት ሲሆን፤ ኢትዮጵያውያን በወሳኝ አገራዊ ጉዳይ ላይ ያላቸውን የጋራ አቋምና አንድነት የሚያሳይ መልካም ጅምር  በማሳየት ላይ ናቸው።

በአገር ውስጥ  በሰላማዊ የትግል መድረክ  የሚሳተፉ የተለያዩ ፓርቲዎች ኢትዮጵያ የምትከተላቸው ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፖሊሲዎች ላይ ግልጽ ልዩነት እንዳላቸው ቢያስቀምጡም የግብፅ መንግሥት   ተቃዋሚዎችን በመጠቀም  የራሱን አጀንዳ ለማስፈጸም የሚያራምደውን አቋም የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደሚቃወሙት በግልጽ እያስቀመጡ ነው ።

«የአባይ ወንዝ መነሻዋ ኢትዮጵያ እንደመሆኗ መጠን አገሪቱ  እንደማንኛውም ተፈጥሯዊ ሀብት የሌሎች ን ጥቅም በማይጎዳ መልኩ የመጠቀም መብት አላት» የሚል የጋራ አቋም የያዙት የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥያቄው የመንግሥትና የፓርቲ ሳይሆን የሕዝብ መሆኑን አንፀባርቀዋል ።  ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ የግብፅ መንግስት ፍላጎት ምንም ይሁን ምንም የጋራ ተጠቃሚነትን  መሠረት ያደረገው የህዳሴው ግድብ  ግንባታ የሕዝብ ሀብት በመሆኑ ፍፃሜውን ለማየት በገንዘቡ፣ በእውቀቱና በጉልበቱ የበኩሉን እየተወጣ ካለው ኢትዮጵያዊ ጋር በጋራ እንደሚሠሩ ማሳየታቸው ይበል የሚያሰኝ ቁርጠኛ ውሳኔ ነው ።

የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ በታችኞቹ የተፋሰስ አገራት ላይ ምንም አሉታዊ ተፅእኖ እንደማያሳድር የተቋቋመው የጋራ የባለሙያዎች ቡድን ባረጋገጠበት ሁኔታ ከግብፅ መንግሥት እየተንፀባረቀ ያለው አቋም ጠብ አጫሪነትና ማን አለብኝነት የሚያሳይ ነው የሚሉት አንዳንድ  ተቃዋሚ ፓርቲዎች  ግድቡን ከፍፃሜ ለማድረስ በሚደረገው ማንኛውምዓይነት እንቅስቃሴ ተሳትፏቸውን እንደሚለግሱ መግለጻቸው የሚበረታታ ብቻ ሳይሆን በቀጣይ በተግባምር መረጋገጥ ያለበት ነው።

በእዚህ ረገድ ከእዚህ ጠንካራው ኢትዮጵያዊ ኅብረት ታሪካዊ የፅናት አቋም ውጪ ገባ ወጣ የሚል ሃሳብ የሚያራምዱ ወገኖች ካሉም አካሄዳቸውን ሊፈትሹ ይገባል፡፡
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment