Friday, June 14, 2013

የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ፀደቀ

(June 13, 2013, (አዲስ አበባ))--የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነትን ትናንት በሙሉ ድምፅ አፀደቀ። የስምምነቱን መጽደቅ አስመልክቶ እንደተገለጸው፤ ስምምነቱ የተፋሰሱን ሀገራት በናይል ወንዝ ፍትሀዊ ተጠቃሚ ለማድረግ ለተጀመረው ጥረት አጋዥ ነው ።

በስምምነቱ መሠረት ማንኛውም የተፋሰሱ አባል ሀገር በናይል ወንዝ ላይ የሚሰራቸውን የልማት ሥራዎች ለአባል ሀገራቱ የማሳወቅ ግዴታ አለበት። ስምምነቱ የተፋሰሱን አጠቃቀም ህጋዊ እንደሚያደርገውም ተጠቁሟል። ከዚህ በተጨማሪም የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ማንኛውም የተፋሰሱ አባል ሀገር በክልሉ ባለው የናይል ውሃ የልማት ሥራዎችን ሲያከናውን በተፋሰሱም ሆነ በሌላ ሀገር ላይ ጉዳት ያለማድረስ ግዴታ እንዳለበት ከግምት ውስጥ ያስገባ በመሆኑ መተማመንን ይፈጥራል።

ኢትዮጵያ ህጉን በምክር ቤቷ በማፅደቅ የመጀመሪያዋ አገር ሆናለች። ማዕቀፉ ከአጠቃላዩ የተፋሰሱ አባል ሀገራት መካከል በስድስቱ ህግ ሆኖ ከጸደቀ የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን ይቋቋማል። ስምምነቱን ያልፈረሙ አገራትም በዚህ ስምምነት እንደሚገዙ ተጠቁሟል።

የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን በማዕቀፍ ስምምነቱ ውስጥ ያሉ መብቶች እና ግዴታዎችን ፣ የውሃውን ፍትሀዊ አጠቃቀም እና ልማትን የመሳሰሉትን ጉዳዮች የሚያስፈጽም ተቋም ነው።

ማንኛውም የተፋሰሱ ሀገር ወንዙን አስመልክቶ ያሉ ጉዳዮችን ለሌሎቹ ማሳወቅ ያለበት በኮሚሽኑ በኩል መሆኑ የሁለት ሀገራት ድርድሮችን አስቀርቶ የጋራ መግባባትን እንደሚፈጥር ተጠቁሟል።
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment