Friday, September 16, 2011

በኢትዮጵያና በእሥራኤል መካከል ነባሩን የአየር ትራንስፖርት ግንኙነት ለማሻሻል ስምምነት ተፈረመ

(ቀን 2011-09-16, አዲስ አበባ (ኢዜአ)- በኢትዮጵያና በእሥራኤል መካከል ነባሩን የሁለትዮሽ የአየር ትራንስፖርት ግንኙነት ለማሻሻል የሚያስችል ስምምነት አዲስ አበባ ውስጥ ትናንት ተፈረመ።

ስምምነቱን የፈረሙት የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኮሎኔል ወሰንየለህ ሁነኛውና በኢትዮጵያ የእሥራኤል አምባሳደር ኦዴድ ቤን ሐይም ናቸው።

ዋና ዳይሬክተሩ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ ስምምነቱ በሁለቱ አገሮች መካከል የነበረውን ኢኮኖሚያዊ፣ ዲፕሎማሲያዊና የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር በበለጠ ያጠናክረዋል።

በኢትዮጵያ የእሥራኤል አምባሳደር ኦዴድ ቤን ሐይም በበኩላቸው ስምምነቱ በሁለቱ አገሮች መካከል ለረዥም ዓመታት የቆየውን ሁሉን አቀፍ ግንኙነት እንደሚያጠናክረው ጠቅሰው፣ ቱሪዝምን በማስፋፋት ረገድም የላቀ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል።

በኢትዮጵያና በእሥራኤል መካከል የሁለትዮሽ የአየር ትራንስፖርት ስምምነት የተፈረመው .. በየካቲት 1998 ሲሆን፣ ስምምነቱ በሁለቱ አገሮች መካከል በሳምንት ለሦስት ቀናት በረራ ለማድረግ የሚያስችል ነበር።

ትናንት የተፈረመው ስምምነትም ከዚህ ቀደም ለሦስት ቀናት የነበረውን ሣምንታዊ በረራ ወደ አምስት ከፍ ለማድረግ የሚያስችል ነው።

ስምምነቱ የወቅቱን የአየር ትራንስፖርት የእድገት ደረጃና የገበያ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ የተከናወነና ሙሉ በሙሉ ስምምነት የተደረሰበት መሆኑ ታውቋል።
የኢትዩጵያ ፕሬስ ድርጅት

No comments:

Post a Comment