Thursday, September 05, 2019

የኢትዮጵያን አንድነት ከሚፈረካክሱ ድርጊቶች መታቀብ ይገባል!

(Sep 05, (አዲስ አበባ))--እንዳለመታደል ሆኖ ነው እንጂ ኢትዮጵያ ታላቅ አገር ነበረች፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብም በዓለም የታሪክ መዝገብ ደማቅ አሻራ ያሳረፈ ነበረ፡፡ አሁንም ከታሰበበት ኢትዮጵያን ታላቅ ማድረግ አያቅትም፡፡ ኢትዮጵያዊነትንም የኅብረ ብሔራዊነት ማጌጫ ማድረግ አያዳግትም፡፡ ነገር ግን ለማይረቡና ለማይጠቅሙ ጉዳዮች ከመጠን በላይ ትኩረት እየተሰጠ፣ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በማራከስ የተፈጸመው ነውረኛ ድርጊት ሥሩን እያስረዘመ ነው፡፡

ጥንታዊያን ኢትዮጵያዊያን በደምና በአጥንታቸው ያቆሙዋትን አገር የሚያሳቅቁ ክፉ ድርጊቶች እየበዙ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን በተለያዩ ዘመናት ክፉና ደግ ወቅቶችን በጋራ አሳልፈዋል፡፡ አኩሪ በሆኑ የጋራ እሴቶቻቸው አማካይነት ተደጋግፈው ኖረዋል፡፡ ለእናት አገራቸው በነበራቸው ከመጠን ያለፈ ፍቅር ምክንያት፣ ወራሪዎችና ተስፋፊዎች እንዳይደፍሯት አድርገዋል፡፡ ለእናት አገራቸው ክብር ሲሉም አንድ ላይ ተሰውተዋል፡፡ ይኼንን የመሰለ ኩሩ ታሪክ ያላት አገር አንድነቷ ተጠብቆ እንዲቆይ፣ ይህ ትውልድም ታሪካዊ አደራ አለበት፡፡ ኢትዮጵያ የሁሉም ልጆቿ እኩል እናት ሆና በነፃነት የሚኖሩባት አገር እንድትሆን፣ በተለይ የአሁኑ ትውልድ ትልቅ ኃላፊነት አለበት፡፡ ትውልዱ ኃላፊነቱን በብቃት መወጣት ካልቻለ ግን የወደፊቱ ትውልድና የታሪክ ተጠያቂ ይሆናል፡፡

የኢትዮጵያ አንድነት የሚያስፈልገው የበለፀገችና ዴሞክራሲያዊት አገር እንድትሆን ነው፡፡ ከምሥራቅ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን ከመላው አፍሪካ በተሻለ ዕምቅ የተፈጥሮ ሀብቷንና ጠንካራ የሰው ኃይሏን በብቃት መጠቀም የምትችል አገር መሆኗን ማስመስከር የሚቻለው፣ አንድነቷ የተጠበቀ ታላቅ አገር የመገንባት የጋራ ራዕይ ሲኖር ብቻ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያንን በብሔር፣ በሃይማኖት፣ በቋንቋ፣ በባህል፣ በመልክዓ ምድር፣ በፖለቲካ አቋምና በመሳሰሉት በመከፋፈል አገርን ማዳከም የሚጠቅመው ለጠላት ብቻ ነው፡፡ አገሩን የሚወድ ኢትዮጵያዊ ግን ልዩነትን አክብሮ የጋራ የሆኑ ጉዳዮች ላይ ይተባበራል፡፡

ከዚህ ውጪ ሕዝቡን የሚከፋፍሉ አጀንዳዎች እየፈጠሩ ማስተጋባት ፀረ ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ ልዩነትን እያራገቡ አንድነትን ማራከስ ጠላትነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአምባገነንነት መራቢያ የምትሆነው ከምክንያታዊነት ይልቅ በስሜታዊነት የሚነዱ ሲበዙ ነው፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች በትምህርት እየተኮተኮቱ ጠያቂና ሞጋች መሆን አለባቸው፡፡ በየጊዜው የሚጠነሰሱ ሴራዎች ሰለባ እንዳይሆኑ ንቃተ ህሊናቸው መጎልበት አለበት፡፡ ይህንን ማድረግ ሲቻል ማንም እየተነሳ አገር አያተራምስም፡፡

የኢትዮጵያ አንድነት መሠረቱ የተጣለው በጥቂት ወገኖች ነው የሚል ትርክት ውስጥ ያሉ ወገኖች ካሉ ተሳስተዋል፡፡ ኢትዮጵያዊነት የተገነባው በአራቱም ማዕዘናት ውስጥ በኖሩ ኢትዮጵያዊያን መስዋዕትነት ነው፡፡ ይህንን በመስዋዕትነት የተገነባ አንድነት በተለያዩ ዘዴዎች ለመፈረካከስ መሞከር፣ ጠቡ የሚሆነው የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኛል ከሚሉ ከመቶ ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን ጋር ነው፡፡ እነዚህ አስተዋይ ኢትዮጵያዊያን የትኛውም ብሔር፣ እምነት፣ ቋንቋ፣ ባህልና ሌሎች እሴቶች ጥቃት እንዲፈጸምባቸው አይፈቅዱም፡፡ ልዩነቶችን አክብረው፣ እርስ በርስ ተጋብተውና ተዋልደው እዚህ የደረሱት ኢትዮጵያዊያን አንዳቸው ለሌላቸው መከታ ናቸው፡፡ ይህ በጋራ እሴቶችና መስተጋብሮች የተገመደ አንድነት በቀላሉ አይበጣጠስም፡፡

አንዱን በሌላው ላይ በማስነሳት የጥፋት አጀንዳ የሚያራምዱ ይጠንቀቁ፡፡ ኢትዮጵያዊያን በጋራ ወራሪዎችንና ተስፋፊዎችን ድባቅ እየመቱ የኢትዮጵያን አንድነት ሲያስጠብቁ የኖሩት፣ እርስ በርስ በነበራቸው ከፍተኛ ፍቅር እንደሆነ ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህም አብያተ ክርስቲያናት፣ መስጊዶችና የተለያዩ ቅዱሳን ሥፍራዎች መከበር አለባቸው፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያዊያን በአንድነት የኖሩት በዚህ መንፈስ ነውና፡፡ የፍቅራቸው፣ የመከባበራቸው፣ የመደጋገፋቸውና የአብሮነታቸው መገለጫ ይህ መሰሉ ጨዋነት ጭምር ነው፡፡

ለኢትዮጵያ አንዳችም የረባ አስተዋጽኦ ያልነበራቸው ግለሰቦችና ስብስቦች፣ ይህንን የመሰለ ፀጋ ሊገፉ ሲነሱ ማስቆም የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ኃላፊነት ነው፡፡ ማንም ጥያቄ ያለው ግለሰብም ሆነ አካል ጥያቄውን በአግባቡ የማቅረብ መብት አለው፡፡ ይህ መብት ግን ገደቡን አልፎ ሄዶ የአገርን ህልውና ሲፈታተንና የሕዝብን ደኅንነት አደጋ ውስጥ ሲከት ዝም አይባልም፡፡

በነጋ በጠባ አዳዲስ አወዛጋቢ አጀንዳዎች እየፈበረኩ አገርን የሚያተራምሱ ወገኖች ይበቃችኋል መባል አለባቸው፡፡ የጥንቶቹ ኢትዮጵያዊያን ሕግ አክባሪ፣ ፈሪኃ ፈጣሪ ያላቸው፣ አስተዋዮችና ጨዋዎች እንደ መሆናቸው መጠን፣ የዚህ ዘመን ትውልድም በሞራልና በሥነ ምግባር ምሥጉን መሆን አለበት፡፡ መስመሩን ስተው የአገር አንድነት የሚፈረካክሱ ሲገኙም በሕግ አደብ እንዲገዙ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ በአገር ህልውና ድርድር የለም መባል ይኖርበታል፡፡ በተለይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የእምነት ተቋማትን በመነካካት ግጭት የሚቀሰቅሱ ኃይሎች በሕግ መባል አለባቸው፡፡ ለኢትዮጵያ አንድነት አደጋ አለውና፡፡

ኢትዮጵያዊያን በዚህ ዘመን ከፍተኛ ትኩረት መስጠት ያለባቸው ለአገራቸው አንድነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ የነፃነት፣ የእኩልነትና የፍትሕ አምባ መሆን አለባት፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን በክብር፣ በፍቅርና በደስታ የምታኖር አገራቸውን መገንባት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የምታድገው ሰላም ሲኖራት ነው፡፡ ሰላሟን እያደፈረሱ የትርምስና የግጭት መናኸሪያ ሊያደርጓት የሚፈልጉ ኃይሎችን ኢትዮጵያዊያን በጋራ ሊታገሏቸው ይገባል፡፡

የኢትዮጵያ አንድነትን የጠቅላይነት አባዜ አድርገው የሚመለከቱ ኃይሎችም ሆኑ ከእነሱ በተቃራኒ ነን የሚሉ ሊገነዘቡ የሚገባው፣ የምንነጋገረው ሁሉንም ኢትዮጵያዊያንን በጋራ አቅፋና ደግፋ መያዝ ስለሚኖርባት ኢትዮጵያ መሆኑን ነው፡፡ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን እናት ስለሆነችው ኢትዮጵያ ስንነጋገር የጥፋት እጆች ይሰብሰቡ እያልን ነው፡፡ ኢትዮጵያ ወደ ቁልቁለት የሚወስዳት ክፋት፣ ምቀኝነትና በቀልተኝነት ነው፡፡ ለኢትዮጵያ አንድነትና ዕድገት የሚማስኑ ኢትዮጵያዊያን ግን፣ ከእነዚህ አላስፈላጊ ከሆኑ ነገሮች ራሳቸውን ማራቅ አለባቸው፡፡ የኢትዮጵያ አንድነት መሠረቱ ፍቅር፣ መከባበር፣ መተሳሰብ፣ ለልዩነቶች ዕውቅና መስጠትና በእኩልነት የሚያኖር ሥርዓት ለማቆም የጋራ ራዕይ መያዝ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያን አንድነት ከሚፈረካክሱ ድርጊቶች መታቀብ ተገቢ ነው!
ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment