Saturday, June 30, 2018

መደመር ሲባል

(June 30,(አጀንዳ ))--የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሕመድ የመደመር ጽንሰ ኃሳብ ሰፊና ጥልቅ ነው፡ ፡መደመር መደመር ነው መቸም መቀነስ አይሆንም፡፡ ከመበታተን ከመከፋፈል ወደ ትናንሽነት ከመለወጥ ተደምረን እንደኖርን ሁሉ አሁንም ያለን ብቸኛው አማራጭ እንደ ሀገር ሁላችንም ተደምረን መዝለቅ ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ በአብዛኛው ሕዝብ ዘንድ ሰፊ ተቀባይነት ያገኘና የሰረጸ ነው፡፡ የመደመር ጉዞ ሀገራችንን ወደፊት ያራምዳል፡፡

ከመደመር ውጭ ሀገራችንን በአብሮነት በአንድነት በሕብረት ከመታደግ ሌላ አማራጭ የለንም፤ሊኖረንም አይችልም፡፡ ያለችን ብዝሀነትን ያቀፈች የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች ባሕሎች ኃይማኖቶች ቋንቋዎች ለሁላችንም የጋራ የሆነች ሀገር ናት፡፡ ያለን አንድና አንድ እድል በጋራ ሁነን ሀገራችንን ማልማት ማሳደግና መጠበቅ ነው፡፡ ብዝሀነታችንና ልዩነቶቻችን ውበቶቻችንና የጥንካሬአችን ምንጮች ናቸው፡፡ መቼውንም ለመለያየት ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም፡፡

የሁሉም ዜጋ ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶች በእኩልነት የተከበሩባት በነጻነት ያለምንም ተጽእኖ የሚኖሩባት የጋራ ሀገርን በመደመር መንፈስ ማጎልበት ነው የሚገባን፡፡ ዘመኑ የመደመር፣ የፍቅር፣ የይቅርታ፣ የምሕረት፣ የመቻቻልና የአብሮነት ነው ሲባል ትርጉሙ ሰፊ ነው፡፡ ዛሬም የመደመር መንፈስ የመደመር አላማና ምንነት ያልገባቸው፤ በስም ብቻ ተደምሬአለሁ፤ ተደምራለች፤ ተደምረዋል፤ እያሉ የሚያላግጡ ወገኖችን መስማት የተለመደ ሆኖአል፡፡

‹‹እነእከሌ ከእኛ አይደመሩም፡፡ እነእከሌ እንዲህ ናቸው፤እንዲያ ናቸው›› የሚሉ የመደመርን ምንነትና ታላቅ ኃይልነት ጭርሱንም የማያውቁ ሰዎች ከሚገምቱት በላይ መደመርን መገንዘብ ይገባቸዋል፡፡ በመሰረቱ አሁን በሀገራችን የመጣው ለውጥ እንዲሳካ ትልቁን ትግልና ግፊት ያደረገው የመብቴ ይከበርልኝ ጥያቄ ያነሳው ሕዝብና ልጆቹ ናቸው፡፡ ችግሩን በጥልቀት በመፈተሽ ስር ነቀል በሆነ ሁኔታ የሕዝቡን ጥያቄ የሚመልሱ ተግባራዊ እርምጃዎችን መውሰድ እንዳለበት ቁርጠኛ አቋም በመያዝ በለቀቁት ጠቅላይ ሚኒስትር ምትክ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሕመድን በስራ አስፈጻሚው መርጦ ለመሪነት ያመጣው ኢሕአዴግ ነው፡፡

በአጭሩ በጠቅላይ ሚኒስትሩ መሪነት የተመዘገቡት ለውጦች በሙሉ ኢሕአዴግ እንደ መሪ ድርጅት በጋራ መክሮ ተነጋግሮ የደረሰባቸው ውሳኔዎች ውጤቶች መሆናቸው ሊሰመርበት ይገባል፡፡ በአዲስ ትጋት አዲስ ለውጥ ማድረግ መደመር ማለትም አንዱ ይሄ ነው፡፡ ለውጥን አምኖ መቀበል ግድ ነው፡፡

የመደመር ጥልቅ ሀሳብ ከቂም በቀልና ከጥላቻ፣ ለዘመናት ሲያባላን ከነበረው፣ ሲከፋፍልን ከኖረው ክፋት፣ ተንኮልና ምቀኝነት መላቀቅም ነው፡፡ መደመር ትናንት በታሪካችን ውስጥ በተደጋጋሚ ሲከሰቱ ከኖሩት ኋላቀር አስተሳሰቦች መናቆሮች ድምርና የተናጠል ጥላቻዎች መውጣት ማለት ነው፡፡ መደመር ማለት ዘረኝነትንና ጎጠኝነትን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን በማስወገድ ለሰው ልጅ ሰው በመሆኑ ብቻ ለክብሩና ለነጻነቱ ለመብቱ መከበር ዘብ መቆም ነው፡፡

መደመር የዜጎች የትም ተንቀሳቅሶ የመኖርና የመስራት ሀብት የማፍራት፤ የመረጡትን የፖለቲካ እምነት በነጻነት የማመን፣ የመከተል መብታቸው በሕገመንግስቱ የተከበረና የተረጋገጠ በመሆኑ በአንድነትና በአብሮነት በመቀጠል ባለን ላይ በመጨመር ወደከፍታው መዝለቅ ማለት ነው፡፡ መደመር ማለት ትናንት ከኖርንበትና ዘመናት ከገፋንበት የእርስ በእርስ ሽኩቻ፣ ጥላቻ፣ ትንቅንቅ፣ መጠፋፋት፣ መወነጃጀል፣ የቂም በቀል ኋላቀር ፖለቲካ ሙሉ በሙሉ መውጣት ነው፡፡ ሁሉንም የትናንትን መጥፎ ቅሪቶች በማራገፍና በመርሳት በአዲስ መንፈስ፣ ለአዲስ ሀገራዊ ግንባታ በሰላም፣ በፍቅር፣ በወንድማማችነት እጅ ለእጅ ተያይዘን መነሳት ማለት ነው፡፡

መደመር ማለት ኢትዮጵያ ለሁሉም ዜጎችዋ የምትበቃ ሀገር ናትና ያለምንም ልዩነት አንዱም ሳይቀርና ሳይነጠል በጋራ ጸንተን እንቁም፤መለያየቱ፣ መከፋፈሉና መበታተኑ አይበጀንም፤ ይህ ኋላ ቀር አስተሳሰብ ይብቃን ማለት ነው፡፡ አንድ ስንሆን አቅም፣ ጉልበትና ብርታት ይኖረናል፡፡ እንደ ሀገር እንደ ሕዝብም እንከበራለን፡፡ ደካሞች ሆነን ከተከፋፈልንና በሕብረት መቆም ካልቻልን ትርፉ ስደትና ተዋራጅነት ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ ለሀገራችን እድገትና ብልጽግና ለሕዝባችን ከድህነት መላቀቅና መውጣት የተሻለ ሕይወት መኖር ሁላችንም ተደምረን በአንድነት መቆም ይኖርብናል፡፡

መደመር ወደላቀው ሀገራዊ እድገት መወንጨፍ እንችል ዘንድ የሚያሸጋግረን መወጣጫ መሰላል ነው፡፡ የመደመርን ትርጉምና ምንነት በቅጡ አለመገንዘብ ሀገራዊ ጉዳቱ ከምንችለው በላይ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡

የመደመርን ስሌት በቅጡ ካለመረዳት በአንዳንድ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ባሉት ዳያስፖራዎች እንዲሁም በሶሻል ሚዲያው የሚታየው የበቀል ስሜትን ያጋተ ጥላቻ እነእከሌ ከእኛ ጋር አይደመሩም፤አትደመርም የሚለው ቁርሾን ያዘለ የቂም አካሄድና አመለካከት፤እኛ ነን ይሄን ለውጥ ያመጣነው ስለዚህ ማንም ከእኛ ጋር አይደመርም የሚለው አግላይ የኋላቀሩ የጥንት ፖለቲከኞች እሳቤ ዛሬም ለሀገራዊ ሰላምና እርቅ የሚያስገኘው ፋይዳ የለም - ውሀ ቢወቅጡት እምቦጭ ነው፡፡ ዘጭ እምቦጭ እንዲሉ፡፡ እንዲህ ነው ለዘመናት የተጓዝነው፡፡ በዚህ ደግሞ እልፍ ፈቀቅ አላልንበትም፡፡ የመደመር እሳቤ ከዚህ ውጭና በእጅጉ የላቀም ነው፡፡ ለመደመር ከበቀል፣ ከቂምና ከጥላቻ ፖለቲካ መጽዳትን ይጠይቃል፡፡

ኋላቀር የፖለቲካ አስተሳሰብ ለሀገራችንም ሆነ ለሕዝባችን ያስገኘው አንድም ምንም ትሩፋት የለም፡፡ እርስ በእርስ በመጠፋፋት፤ በመተላለቅ፤ በመገዳደል፤ በሴራ ፖለቲካ በመጠላለፍ ሀገርን ከመጉዳት ውጭ የተገኘ ትርፍ የለም፡፡ በዚህ ትውልድ ገዳይ በሽታ መንስኤነት ለድሀ ሀገራቸው በእጅጉ ሊጠቅሙ ይችሉ የነበሩ፤ የላቀ እውቀት የነበራቸውን እጅግ ብዙ ምሁራን አጥተናል፡፡ አልጠቀመንም፤ አይጠቅመንም፡፡ የመደመር እሳቤና ፖለቲካ ብቻ ነው የሚበጀን፡፡

የመደመር ፖለቲካ ከቀደመው ትውልድን ከበላውና ከገደለው ኋላቀር ፖለቲካ ተላቀን የትኛውም አይነት ሀሳቦች በልዩነት እንዲንጸባረቁ እንዲንሸራሸሩ፤ መጠፋፋት መወነጃጀል እንዲቀር፤በውይይትና በምክንያት በመነጋገር ማመን፤ልዩነትን በልዩነት ይዘን ግን ደግሞ ለጋራ ሀገራችን ሁላችንም በሕብረት ተጋግዘን ቆመን መስራትን ይፈልጋል፡፡

የአንድ ሀገር ልጆች በፖለቲካ አመለካከት በመለያየታቸው ብቻ እንደጠላት የሚተያዩበት ለመጠፋፋት የሚፈላለጉበት አሳዳጅና ተሳዳጅ፤ ገዳይና ሟች ሁነው ያሳለፉትና የኖሩበት የታሪክ ምእራፍ መዘጋት አለበት፡፡ በፍቅር በይቅርታ በምሕረት ያለፈውን ሁሉ ትተን ይቅር ብለን በአዲስ መንፈስ ለሀገራችንና ለሕዝባችን ለመስራት በአንድ ላይ መደመር ይኖርብናል፡፡

ከትወልድ ትውልድ የሄድንባቸው የተሳሳቱ መንገዶች ይታረሙ፡፡ ለልጆቻችን ለልጅ ልጆቻችን የፍቅርና የሰላም ሀገር እናውርስ ነው የመደመር ትልቁ ትርጉሙ፡፡ ስለዚህም በመደመር ሀገራዊ ሂደቱ ውስጥ እከሌ ከእከሌ ተብሎ ተነጥሎ የሚቀር የሚወገዝ በትናንት እሳቤ የሚገለል የለም፤ አይኖርምም፡፡ በሁሉም መስክ ከተከሰቱት የመውደቅና የመነሳት ታሪኮች በገዢው ፓርቲም ሆነ በተቃዋሚው ጎራ ከመካሰስ ከመወነጃጀል ተላቀን አንዱ በሌላው ላይ ጣት ከመቀሳሰር ወጥተን በአዲስ መንፈስ ትጋትና ብርታት ሁላችንም በአንድ ላይ ተደምረን ለሀገራችን አዲስ የዛሬና የነገ ታሪክ እንስራ ነው መደመር ማለት፡፡

ኋላ ቀር ከሆነው የፖለቲካ ግብግብ ወጥተን ዘመኑ የሚከተለውን ስልጡን ፖለቲካ እንከተል፡፡ በመወያየትና በመነጋገር ልዩነቶቻችንን አቻችለን በአንድ ላይም ተደምረን ሀገራችን ኢትዮጵያን ወደቀደመው ገናና ስልጣኔዋ ተረባርበን እንመልሳት፤ እንታደጋት ነው የመደመር ፍቺው፡፡

ሁሉም ዜጋ ሀገሩንና ወገኑን ይወዳል፡፡ ጥልቅ ፍቅር አለው፡፡ ይሄንን አቅም ተጠቅመን ጥላቻና መጠፋፋትን ዘረኝነትን አስወግደን በአንድ ላይም ተደምረን ታላቅ ሀገር እንፍጠር፡፡ ሀገራችን ለልጆችዋ በቂና ከበቂም በላይ ናት፡፡ ስንሻኮትና ስንናቆር ተጠላልፈን ስንወድቅ ሀገራዊ ድህነትና ችግራችንን አራዘምነው እንጂ አልፈታነውም፡፡ ይህ የታሪክ ምእራፍ ይዘጋ፡፡ በጋራ ተደምረን አዲስ ታሪክ እንስራ፡፡

ኢሕአዴግ በሀገር ደረጃ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት ኢኮኖሚው እንዲያድግ ከነችግሮቹ የላቁ ሀገራዊ ስራዎችን ሰርቶአል፡፡ እስከዛሬ ሰርቶ ካሳየው የበለጠ ችግሮቹን ፈቶ ስህተቶቹን አርሞ ሙስና፣ ብልሹ አሰራር የመልካም አስተዳደር ችግር በስልጣን ያአለአግባብ የመጠቀም ነውርን አስወግዶ ግልጽነት ተጠያቂነት የሕግ የበላይነት ያለው አሰራር እንዲያሰፍን ዜጎችም የበኩላቸውን ድርሻ ሊወጡ ይገባል፡፡ ወደላቀ ምእራፍ ለመሸጋገር ሁላችንም በአንድ ላይ እንታደም፤እንደመር፡፡

መደመር መላቅና ወደከፍታው መጓዝ ነው፡፡ መደመር ኃይልና ጉልበት ነው፡፡ ‹‹ከአንድ ብርቱ ሁለት መድኃኒቱ›› እንዲሉ አባቶች የሚሊዮኖች በአንድ ላይ መደመር ተአምር ይፈጥራል፡፡አዲስ ታሪክ ይሰራል- በመደመር ጉዞ ወደፊት !
የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (መሐመድ አማን )

No comments:

Post a Comment