Monday, March 16, 2015

ስደት ይብቃ ! በሀገር ውስጥ ሰርቶ መለወጥ ይቻላል !

(መጋቢት 7, 2007, (አዲስ አበባ))--«ኢትዮጵያ ለዜጎቿ ካንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ የመዘዋወር መብትን በሕግ ካረጋገጡ ሀገሮች አንዷ ናት። ዜጎች ለሥራ፣ ለትምህርት፣ ለኑሮ በሚያመቻቸው ቦታ ላይ ተዘዋውረው የመኖር መብት አላቸው። ሕጋዊ በሆነ መልኩም ከሀገር ለተለያዩ ተግባር እንዲወጡም ሕጉ ይፈቅዳል። ይሁን እንጂ አሁን የሚታየውና ዜጎችን ለሞትና እንግልት እየዳረገ ያለው አሳሳቢ ጉዳይ በደላሎች አማካይነት በሕገወጥ መንገድ የሚደረግ የሰዎች ዝውውር ነው። የተለያዩ እርምጃዎች ቢወሰዱም ለውጡ አበረታች አይመስልም፡፡

ዜጎች በሳውዲ አረቢያ፣ በየመን፣ በኳታር፣ በደቡብ አፍሪካና በሌሎችም አገሮች በስፋት በሕገወጥ ሰዎች አዘዋዋሪዎችና ሕጋዊ መንገድን ሽፋን ባደረጉ ኤጀንሲዎች አማካይነት ይሄዱ እንደነበር ይታወቃል። በሕገወጥ መንገድ የሚወጡ ዜጎች በጉዟቸው ላይ ከሚደርስባቸው ስቃይና እንግልት በተጨማሪም በሄዱበት ሀገርም ለጉልበታቸው ተመጣጣኝ ያልሆነ ክፍያ እየተከፈላቸው፣ ለረጅም ሰዓት ሥራ እንዲሰሩ እየተገደዱ፣ እየተራቡና እየተጠሙ ከዚያም አልፎ ተርፎ የሰሩበትን ገንዘብ በመነጠቅና ሕይወት እስከማጣት የሚደርሱ አደጋዎች ሲያጋጥማቸው እንደነበር በተለያዩ ጊዜያት ዜጎች በአንደበታቸው መስክረዋል።

ስደተኞቹ የሚሄዱበትን ሀገር ባህል፣ እምነት፣ ቋንቋና ሌሎች ማወቅ የሚገባቸውን በአግባቡ ሳያውቁ በመሄድ የሚደርስባቸው ችግር የከፋ ነው። ወደ ተለያዩ አገራት የሚሄዱበት መንገድ ሕገወጥነትን የተከተለ መሆኑም ባለፈው ዓመት በመንግሥትና በዓለምአቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይ ኦ ኤም) ጥረት ከሳውዲ አረቢያ ወደ ሀገር ቤት እንዲመለሱ የተደረጉት ስደተኞች ከ170 ሺ በላይ ናቸው።

ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሄድ በሚልም 453 ዜጎች ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በሞያሌ በኩል ወጥተው በታንዛኒያ መንግጭት ድንበር ጠባቂዎች በመያዛቸው ምክንያት ከሰባት እስከ ሦስት ዓመታት በሚደርስ እስር ከተቀጡ በኋላ በያዝነው ዓመት መንግሥት ከታንዛኒያ መንግሥት ጋር በተደጋጋሚ ባደረገው ድርድር ወደ አገራቸው እንዲገቡ ተደርጓል። በአይ ኦ ኤም ና በሌሎችም የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፤ በሕገወጥ መንገድ ከሚሄዱት መካከል 80 በመቶ የሚሆኑት በጉዞ ወቅት አስከፊ ነገሮች እንደሚያጋጥማቸው የሚያውቁ ናቸው። በበረሀና በባህር ላይ የሚቀሩት ብዘዎች መሆናቸውን በመገናኛ ብዙኃን የሰሙ ናቸው።

እ.አ.አ በ2014 ስድስት ወራት ብቻ በምሥራቁ የሀገሪቱ ክፍል በኩል በየመን ወደ ሳውዲ አረቢያ ለመሄድ ሞክረው 48ሺ ዜጎች የመን መድረሳቸው ተረጋግጧል። ከእነዚህ መካከል ስምንት በመቶ የሚሆኑት ደግሞ የሳውዲ አረቢያ ተመላሾች ናቸው፡፡ እንዲሁም በሰሜኑ አቅጣጫ በመተማ አድርገው በሱዳን ሊቢያ ከዚያም ወደ ኢጣሊያ በማምራት ወደተለያዩ የአውሮፓ ሀገራት ለመሄድ ሕገወጥ መንገዱን የተከተሉ በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች አሉ።

ጥናቱ እንደሚያመለክተው፤ በአፋር ክልል በኩል ወደ ጅቡቲ በሚሻገሩት ላይ ሕገወጥ ዝውውሩ ጨምሯል። ከሚያዝያ 2006 እስከ መስከረም20/2007 ዓ.ም ድረስ ባሉት ስድስት ወራት ሦስት ሺ602 ዜጎች ሊወጡ ሲሉ ተይዘው ወደ ቤተሰባቸው እንዲመለሱ ተደርጓል። ከእነዚህም መካከል 1ሺ200 የሳውዲ አረቢያ ተመላሾች ናቸው።

የየክልሎቹ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ኤጀንሲዎች እንዳረጋገጡት፤ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ከአምስት ሺ955 የሳውዲ ተመላሾች መካከል 70 በመቶ ያህሉ ለማቋቋም ጥረት ቢደረገም አሁንም ከአገር ለመውጣት የሚሞክሩ አሉ። ከኦሮሚያ ክልል ከ31ሺ ተመላሾች መካከል አንዳንዶቹ ያቋረጡትን ትምህርት እንዲቀጥሉ ተደርጓል። አንዳንዶችን ደግሞ ሥልጠና በመስጠትና ወደ ሥራ በማሰማራት ከ11ሺ በላይ ተመላሾች ወደ ሥራ እንዲገቡ ጥረት ተደርጓል። ይሁን እንጂ አሁንም ከየአቅጣጫው የሚደመጠው ስደትን የሚናፍቁ ወጣቶች ቁጥር ከፍተኛ መሆኑ ነው። ሰርቶ ማደግ የሚቻለው በውጭ አገር ብቻ አድርጎ ማለም አለ። በሕገወጥ አዘዋዋሪዎችም የሚከፍሉት ገንዘበ ከሃምሳ እስከ ዘጠና ሺ ብር ነው። ይሄ ገንዘብ በሀገር ቤት ሰርቶ ለመቀየር የሚያስችላቸው መሆኑን አልተገነዘቡም።

ከስደት ናፋቂዎቹ በተቃራኒው ደግሞ በርካታ ወጣቶችና ሴቶች በተለያየ ጥቃቅንና አነስተኛ ሥራ ላይ ተሰማርተው ዛሬ የመካከለኛ ኢንዱስትሪ ባለቤት ለመሆን በቅተዋል። በሚሊየን የሚቆጠር ገንዘብ ማንቀሳቀስ ችለዋል። በዚህም በሀገር ቤት ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል አሳይተዋል። ሆኖም ግን ይሄ ግንዛቤ የሌላቸው፤ ቢኖራቸውም ውጭ ሀገር «ገንዘብ በገፍ ይገኛል» በአጭር ጊዜ ራስን መለወጥ ይቻላል በሚል የተሳሳተ ስሜት ለጉዳት እየተዳረጉ ይገኛሉ። ራስን በሀገር ለመቀየር ያላቸው ዝግጁነትም ዝቅተኛ ነው፡፡

በእርግጥ በየክልሉ በሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ኤጀንሲዎች አማካይነት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ እየተሠራ ይገኛል። አሁን ያለውን የስደት ቀጣይነት ሲታይ ግንዛቤ የማስጨበጫ ሥራው በበቂ ሁኔታ ተሰርቷል ለማለት አያስደፍርም። ከባዶ ተነስተው አንቱ የተባሉ ውጤታማ ወጣቶችን ሞዴል አድርጎ ማስተማር በሥልጠና ማገዝ፣ የሚሰሩበትን ቦታ መስጠትና የቅርብ ክትትል ማድረግ አሁንም ተጠናከሮ ሊሰራ የሚገባው ጉዳይ ነው። የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መቅረፍና ለሁሉም ተገቢ ዕድል መፍጠርም ለነገ የሚባል ሥራ አይደለም፡፡

አሁን አብዛኛውን ወጣት ለስደት ያነሳሳው ከስንት ሺ ስደተኛ መካከል ጥቂቱን የተሳካለትን በማየት ነው። በተለይ ስደተኞች በብዛት የሚታየው ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች፣ ኦሮሚያና አማራ ክልሎች በመሆኑ ጉዳዩ የሚመለከተቻው አካላት በማህበረሰብ ውይይትና በሌሎችም ማህበራዊ ትስስሮች ስደትን ማውገዝ ያስፈልጋል። በዚህ በኩል ዜጎችን በጠንካራ ትምህርት የመቀየር ትልቅ የቤት ሥራዎች ይጠብቃል። ኢትዮጵያ ለዜጎቿ የመዘዋወር መብትን አጎናፅፋለች። በውጭ ሀገር ለመስራት ብቃትና አቅሙ ያለው ዜጋ አሁንም በሕጋዊ መንገድ በመሄድ ላይ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ሊሄድም ይገባል፡፡ አስከፊው ስደት ግን ይቁም! ለዚህም ሁላችንም እንትጋ!!
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment