Tuesday, April 21, 2015

በሊቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው ለመመለስ ጥረት እየተደረገ ነው

(ሚያዚያ 13/2007, አዲስ አበባ ))--በሊቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው ለመመለስ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

ሚኒስትሩ ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ይህን ያስታወቁት ዛሬ ከሞዛምቢክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጁሊዮ ማርኩዊዝ ጋር በተወያዩበት ወቅት ነው። የሞዛምቢኩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የአገራቸው ሕዝብና መንግሥት በኢትዮጵያውያኑ ላይ በደረሰው አሰቃቂ ድርጊት ማዘናቸውን ገልፀዋል።

ዶክተር ቴድሮስ እስካሁን 14 ኢትዮጵያውያንን ወደ አገር ቤት ለመመለስ ጥረት መጀመሩን ጠቅሰው በቀጣይም በካይሮ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አማካኝነት ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። "አሸባሪ ቡድኑ እስልምናን የማይወክልና በኃይማኖቶች መካከል መከፋፈልን በመፍጠር የአገራትን ሠላም ለማደፍረስ ቆርጦ የተነሳ መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም"  ነው ያሉት ሚኒስትሩ።

መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነቱን በማጠናከር የደረሰው አሰቃቂ አደጋ እንደማይበግረው ማሳየት አለበት ብለዋል። የሞዛምቢኩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በበኩላቸው በኢትዮጵያውያኑ ላይ የደረሰውን አሰቃቂ አደጋ የሞዛቢክ ሕዝብና መንግሥት እንደሚያወግዙት ገልጸዋል።

ቀደም ሲል በግብፅ፣ አሁን በኢትዮጵያ የደረሰውን ተመሳሳይ የሽብር አደጋ ለመግታት መንግሥታት በጋራ መስራት አለባቸው ያሉት ሚኒስትሩ የሽብር ጥቃቱ ዒላማ አንድ ብቻ ባለመሆኑ ሽብርተኝነትን መዋጋት የመላው ዓለም ኃላፊነት ነው ብለዋል።
ምንጭ: የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

No comments:

Post a Comment