Thursday, January 01, 2015

በህገ ወጥ የገንዘብ አዘዋዋሪዎችና ተሳታፊዎች ላይ ጥብቅ እርምጃ ይወሰዳል

(ታህሳስ, 23/2007, (አዲስ አበባ))--በአገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ገንዘብ ሲልኩም ሆነ ሲቀበሉ ህጋዊ የፋይናንስ ተቋማትን ብቻ እንዲጠቀሙ የፋይናንስ ደህንነት የመረጃ ማእከል አሳሰበ። ፖሊስ በበኩሉ በህገ-ወጥ መንገድ የሚካሄደውን የገንዘብ ዝውውርና ምንዛሬ ተከታትሎ በወንጀሉ በሚሳተፉ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል።

የፋይናንስ ደህንነት መረጃ ማእከል ዋና ዳይሬክተር አቶ ገመቹ ወዩማ እንደገለፁት፤ ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር የአገርን የፋይናንስ ስርዓት ጤናማ እንዳይሆን ከማድረግ ባሻገር የሽብርተኞች መጠቀሚያ በመሆን በዜጎችና በአገር ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያስከትላል።

የወንጀሉን ምንጮች በአግባቡ በመከታተል ህብረተሰቡና የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ትኩረት ሰጥተው እንደሰሩም አስገንዝበዋል። እንደ አቶ ገመቹ ገለፃ፤ ዜጎች በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ገንዘብ ከባንክ አሰራር ውጭ ሲልኩም ሆነ ሲቀበሉ ምንም አይነት ዋስትና ስለማይኖረው የገንዘባቸውና የራሳቸው ደህንነት ስጋት ላይ እንደሚወድቅ ሊረዱት ይገባል።

ማእከሉ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የአገሪቱ የፋይናንስ ስርዓት ጤናማና የተረጋጋ እንዲሆን እንዲሁም የሽብርተኞች መጠቀሚያ እንዳይሆን ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል።

«ህጋዊ ባልሆነ መንገድ የሚደረገው የገንዘብ እንቅስቃሴ ወንጀል መሆኑን ህብረተሰቡ ተገንዝቦ በጋራ ሊከላከል ይገባል» ሲሉም አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ በበኩሉ « ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ከሃገር ሲወጣና ሲገባ የአገሪቱን ገቢ የሚያሳጣ እና ሽብርተኝነትንና አክራሪነትን ለመደገፍ ሊውል ይችላል» ሲል ገልጿል።

አንዳንድ ግለሰቦች በህጋዊ የምንዛሬ ቢሮዎች (ባንኮች) ባለመጠቀማቸው ገንዘባቸውን የመዘረፍና ሃሰተኛ የብር ኖቶችን በመግዛት ለከፍተኛ ኪሳራ እየተዳረጉ መሆኑንም አመልክቷል።

ከውጭ አገር የሚላክ ሐዋላን በተመለከተ ባንኮች ከተለያዩ አለም አቀፍ የሐዋላ ድርጅቶች ጋር በጋራ ስለሚሰሩ ዜጎች ያለምንም ክፍያ ገንዘባቸውን ከአስተማማኝ ዋስትና ጋር በተላከበት ቀን መረከብ እንደሚችሉ ገልጾ፣ ለህገ-ወጥ አዘዋዋሪዎች ከሚከፈል ከፍተኛ ኮሚሽንና ከአጭበርባሪዎች የመታለል አደጋ ራሳቸውን እንዲጠብቁ አሳስቧል።

ብሔራዊ ባንክ ለባንኮች፣ለአየር መንገዶች፣ ለሲቪል አቪዬሽን እንዲሁም ለአስጎብኚ ድርጅቶች አገልግሎታቸውን በውጭ ምንዛሬ እንዲሰጡ መመሪያ ማውጣቱንና የውጭ ምንዛሪ የመቀበል ወይም የመያዝ ፈቃድ ያልተሰጠው ድርጅት ወይም ግለሰብ ይዞ ቢገኝ የሚቀጣበት አዋጅና መመሪያ በግልፅ መቀመጡን አስታውቋል።

በአዲሰ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የከባድ ልዩ ልዩ ወንጀል ምርመራ ሃላፊ ምክትል ኮማንደር አበራ ቡሊና እንደገለፁት፤ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች በሚፈፀመው ህገ-ወጥ ምንዛሪና የገንዘብ ዝውውር ላይ ጥናት በማድረግ እርምጃ ይወስዳል።

« ወንጀሉን ለመከላከል ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትና ከህብረተሰቡ ጋር ተቀናጅቶ መስራትን ይጠይቃል » ያሉት ሃላፊው፣ ህብረተሰቡም በራሱ እና በአገሩ ላይ ሊደርስ የሚችልን የወንጀል አደጋ መከላከል እንደሚኖርበት አሳስበዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ    

No comments:

Post a Comment