Thursday, December 25, 2014

በሃና ላይ የመድፈርና የግድያ ወንጀል በፈጸሙ ተጠርጣሪዎች ላይ እስከ ሞት የሚያስቀጣ ክስ ተመሰረተ

(Dec 25, 2014, (አዲስ አበባ))--የፌዴራሉ ዐቃቤ ህግ በሃና ላላንጎ ላይ የመድፈርና የግድያ ወንጀል ፈጽመዋል ባላቸው አምስት ተጠርጣሪዎች ላይ እስከ ሞት የሚያስቀጣ አንቀጽ ጠቅሶ ክስ መሰረተባቸው፡፡

ፍርድ ቤቱ በህጉ ላይ ተመስርቶ የሚሰጠው ፍርድ እንደተጠበቀ ቢሆንም ዐቃቤ ህግ በተጠር ጣሪዎቹ ላይ ሁለት ክስ መስርቷል፡፡ በቀዳሚነት ጠቅሶ የመሰረተው ክስ በ1996ዓ.ም የወጣውን የኢፌዴሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 32 (1) (ሀ)ና 626(1)ስር የተደነገገውን በመተላለፍ ነው፡፡ በዚህ አንቀጽ ሥር ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆች ላይ የግብረ ሥጋ ድፍረት በደል ወንጀል በመፈጸም ተጠርጥረው ሲሆን፤ በዚህ አንቀጽ የተከሰሰ ሰው ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ በወንጀል ህጉ መሰረት ከሶስት እስከ 15 ዓመት ጽኑ እስራት ያስቀጣዋል፡፡

በሁለተኛነት በተመሰረተባቸው ክስም በ1996 ዓ.ም የወጣውን የኢፌዴሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 32(1)(ሀ)ና539(1) (ሀ)ስር የተደነገገውን መተላለፉ ነው፡፡ በዚህ ክስ ስር ከባድ የሰው መግደል ወንጀል የተረጋገጠበት ግለሰብ በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም በሞት እንደሚቀጣ ተደንግጓል፡፡

«በ16 ዓመቷ ታዳጊ ሃና ላላንጎ ላይ የመድፈር ወንጀል በመፈፀም ለሞት አብቅተዋታል» የተባሉት አምስት ተጠርጣሪዎች ሳምሶን ስለሺ፣ በዛብህ ገብረማርያም፣ በቃሉ ገብረመድህን፣ ኤፍሬም አየለና ተመስገን ጸጋዬ ሲሆኑ፤ ታህሳስ 7 ቀን 2007 ዓ.ም በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 3ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡

ችሎቱም የተከሳሾችን ማንነት አጣርቶ የተመሰረተባቸው ክስ እንዲደርሳቸውና ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ አዝዟል፣ «ጠበቃ የማቆም አቅም የለንም» ባሉት መሰረት መንግሥት ጠበቃ እንዲመደብላቸው አዝዟል፡፡ ክሱን ለማንበብም ለታህሳስ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ዐቃቤ ህግ የመሰረተው ክስ እንደሚያስረዳው መስከረም 20 ቀን 2007ዓ.ም በግምት 11፡00ሲሆን ሃና ላላንጎ ጦር ኃይሎች አካባቢ ታክሲ ስትጠብቅ ነበር፡፡ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን የግብረ ሥጋ ግንኙነት ለመፈጸም አስበው ታክሲ ከምትጠብቅበት ስፍራ አንደኛ ተከሳሽ ሳምሶን ስለሺ በሚያሽከረክረው ሚኒ ባስ በማስገባት ቀራንዮ አደባባይ አካባቢ ተጉዘው አብረው እስከ ምሽቱ ሁለት ተኩል ከቆዩ በኋላ ሁለተኛ ተከሳሽ በዛብህ ገብረማርያምን በስልክ ደውሎ ጠርቶታል፡፡

በዛብህ ገብረማርያምም በሚያሽከረክረው ሚኒባስ ታክሲ አራተኛና አምስተኛ ተከሳሾችን ኤፍሬም አየለንና ተመስገን ጸጋዬን ይዞ ከሳምሶን ስለሺ ጋር በመገናኘት ሟችን ወደ ቤቱ ወስዷታል፡፡ የሚያሽከረክረውን ታክሲ አቁሞ እንደሚመለስ ተነጋግሮ መለየቱንም ይገልጻል፡፡ ኤፍሬምም በዛብህና ሶስተኛው ተከሳሽ በቃሉ ገብረመድህን መኖሪያ ቤት ወስደዋታል፡፡ በግምትም ከምሽቱ አራት ሰዓት ጀምሮ ሌሊቱን በሙሉ ሁሉም ተከሳሾች እየተፈራረቁ በአሰቃቂ ሁኔታ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ሲፈፅሙባት እንዳደሩ ነው መዝገቡ የሚያትተው፡፡ በዚህም 18 ዓመት ባልሞላቸው ልጆች ላይ የሚፈፀም የግብረ ሥጋ ድፍረት በደል ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡

ድርጊታቸው ህገወጥና የሚያስቀጣ ውጤት ሊያስከትል እንደሚችል እያወቁ በግዴለሽነት እየተፈራረቁ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ፈጽመውባታል፡፡ ሟቿ የድረሱልኝ ጥሪ እያሰማች ማህፀኗም እየደማ ጨካኝነታቸውን፣ ነውረኝነታቸውንና አደገኝነታቸውን በሚያሳይ ሁኔታ ለአምስት ቀናት አቆይተዋታል፡፡

ከዚያም ከአምስት ቀናት በኋላ በዛብህ ገብረማርያም በበቃሉ ገብረመድህን አማካኝነት ሟችን ልዩ ቦታው ጦር ኃይሎች ሙሉ ወንጌል ቤተክርስቲያን አካባቢ ወስዶ ጥሏታል፡፡ ሟች በደረሰባት ጉዳት የሰውነት ክፍሎቿ ሥራ በማቆማቸውና ብዛት ያለው ደም ስለፈሰሳት ከቀናት በኋላ ህይወቷ በማለፉ በፈፀሙት ከባድ የሰው መግደል ወንጀል ተከስሰዋል፡፡
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

Related topics:  
«ለሃና ፈጣን እርዳታ አልተደረገም» ሲሉ አባቷ ተናገሩ

1 comment:

Unknown said...

አላህ ፍቱን ቅጣት ያውርድባቸው!!

Post a Comment