Tuesday, October 07, 2014

«ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን በሰላምና ደህንነትም አፍሪካን እየመራች ነው»- የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ

(መስከረም 27/2007, (አዲስ አበባ))--በ69ኛው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በአጋጣሚው ከተለያዩ አገራት መንግሥታት ጋር ውይይት አካሂደው ነበር። ከእነዚህ መካከል የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አንዱ ነበሩ።



የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ከአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጋር የሁለትዮሽ ውይይታቸውን ያደረጉት በኋይት ሃውስ ሲሆን፤ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ አተኩረው እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ።

በውይይቱ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ የተለያዩ የኢትዮጵያ ሚኒስትሮችና ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በአሜሪካ በኩልም ከባራክ ኦባማ በተጨማሪ የተለያዩ የአሜሪካ መንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።

የኋይት ሃውስ ጽሕፈት ቤት በድረ ገጹ በአፍሪካ እየታየ ስላለው ብሩህ ተስፋና መሻሻሎች ሲነገር በኢትዮጵያ እየተካሄደ ካለው በላይ የተሻለ ምሳሌ አይገኝም፤ በአንድ ወቅት ራሷን እንኳን መመገብ ተስኗት የነበረች ሀገር አሁን ግን በዓለም በፍጥነት ኢኮኖሚያቸውን በማሳደግ ላይ ከሚገኙ አገራት አንዷ ሆናለች ሲሉ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ መግለጻቸውን አስነብቧል።

በግብርና ምርት ከፍተኛ መሻሻሎች እያሳየች ነው። ከግብርናው በተጨማሪ በኃይል ማመንጨት ዘርፍም እያደረገችው ባለው ልማት ከአካባቢው አገራት ቀዳሚ በመሆን ላይ ትገኛለች። የኤሌክትሪክ ኃይል ወደ ውጭ እስከመላክ እየደረሰች ነው። እናም ኦባማ እንደገለጹት ኢትዮጵያ አሁን በግብርና ብቻ ሳይሆን በኃይል አቅርቦትም ራሷን በማሳደግ በለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች።

«አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ጠንካራ የንግድ ሸሪክ ነች። በቅርቡ የአሜሪካ ቦይንግ ኩባንያን ከኢትዮጵያ ጋር ስምምነት ፈጽሟል። ይህ ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ የሥራ ዕድል ይፈጥራል» በማለት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለው ግንኙነት ወደ ኢኮኖሚያዊ ትስስር ማደግ መጀመሩንም ያስረዳሉ።

በሌላ በኩል ፕሬዚዳንቱ ያመለከቱት ጉዳይ ኢትዮጵያ በአህጉራዊ ሰላም ማስፈንና ማስከበር በኩል እያበረከተች ያለውን አስተዋፅኦ ነው። ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከባን ኪ ሙን ጋር ሰላም ማስከበር እና ግጭት አፈታት ላይ ያለውን የአፈፃፀም ውጤታማነት መሻሻልን ሲነጋገሩ ኢትዮጵያ ሰላም ለማስፈን ከዓለም ምርጦቹ አገራት አንዷ እንደሆነች ማውሳታቸውንና ይህንንም እንደሚያደንቁ ለኢትዮጵያውያኑ የልዑካን ቡድን አስረድተዋል።

በሰላም ማስከበር ብዙ አስተዋፅኦ ከሚያበረክቱ አገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ከመሆኗ ባሻገር የሀገሪቱ ሠራዊት በጣም አስቸጋሪ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ ተመድቦ እንኳን ውጤታማ ተዋጊና ግጭት አስወጋጅ መሆኑን ነው ባራክ ኦባማ የተናገሩት።

ስለዚህ ኢትዮጵያ አህጉሩን የምትመራው በኢኮኖሚ እድገት ብቻ ሳይሆን በሰላምና ደህንነት ጭምር ነው። ለእዚህ መገለጫው በአህጉሪቱ ለረጅም ጊዜያት የዘለቁ ግጭቶችን ለመፍታት በምታደርገው ጥረት ነው። ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን በሰላምና ደህንነትም አፍሪካን እየመራች መሆኑ በሁሉም ዘርፍ የእስካሁኑ ውጤቷ አመለካች ነው።

ፕሬዚዳንቱ የደቡብ ሱዳን ጉዳይ ዓለም አቀፍ ማህበረሰብ በጋራ ጠንክሮ ሊሠራበት የሚገባ ተግዳሮት መሆኑን ገልጸው፤ ውይይቱ ጤና፤ ኢኮኖሚና ግብርና ላይ ከማተኮር በተጨማሪ ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳን ውስጥ ያሉትን ሁለቱን ወገኖች ለማቀራረብ ከፍተኛ ትግል እስከምታደርግበት ድረስ ይዘልቃል ብለዋል።

በመጨረሻ ፕሬዚዳንቱ በግልፅ እንደሚታወቀው ስለ ሽብርተኝነት ብዙ እየተባለ መሆኑን አስታውሰው፤ አሁን ትኩረታቸው በኢራቅና ሶሪያ አካባቢ የሚንቀሳቀሰውና የዓለም የሰላም ስጋት የሆነው በአይ.ኤስ.አይ.ኤል ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በሌላ በኩል በሶማሊያ የአልቃይዳ ክንፍ የሆነው የሽብር ምንጭ አልሸባብ ሲሆን፤ ይህም በኢትዮጵያ በኩል ካለው አመራር ጋር ተባብሮ መሥራት በመቻሉ ምክንያት ቡድኑ ከህዝቡ እንዲነጠል ተደርጓል።ይህ ውጤት እንዲገኝ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ሥራ ሠርታለች። በዚህም ልትመሰገን ይገባል ሲሉ ነው የገለጹት። ከኢትዮጵያ ጋር የተመሰረተው የፀረ ሽብርተኝነት ትብብርና አጋርነት አጠቃላይ ሽብርተኝነትን ለመደምሰስ ለሚደረገው ጥረት ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል።

የደቡብ ሱዳን አይነት አንገብጋቢ የሆኑ ጉዳዮች ላይ ለመመካከርና በዚህ ላይ በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት የሚጠናከርበት መንገድ በጥልቀት የመምከር ዕድል ውይይቱ ፈጥሯል።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትርና መንግሥት በዚህ ዓመት ምርጫ ያካሂዳሉ። የአሜሪካም የምርጫ ዘመኑ እየተቃረበ ነው። ስለሆነም ስለ ሲቪክ ማህበራትና አስተዳደር ጉዳዮች እንዲሁም በኢትዮጵያ ያለው ለውጥና አርአያነት ላይ ውይይት ይደረጋል። በውይይቱ የሲቪክ ማህበራትም እንዲስፋፉ ከማድረግ በተጨማሪ በመላ አፍሪካ ዴሞክራሲን ለማስፈን ስለሚደረገው ጥረት ለመወያየት አጋጣሚ ይፈጥራል በማለት ውይይቱ ፖለቲካዊ ብቻ ሳይሆን ኢኮኖሚዊ ነው ብለዋል።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝም በበኩላቸው ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ላለው ግንኙነት ትልቅ ዋጋ ትሰጣለች፤ ኢትዮጵያ እያደገች ነው የተባለው እውነት መሆኑን አረጋግጠዋል። የአገሪቱ ኢኮኖሚም በለውጥ ውስጥ መሆኑን እና ለቀጣይ ሥራዎችም የዩናይትድ ስቴትስ ድጋፍ ከፍተኛ መሆኑንም ነው የተናገሩት።

ኢትዮጵያን ለማበልፀግ በዋናነት የሚያስፈልገው የሰው ኃይል አቅም ነው የሚሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዩናይትድ ስቴትስ በተለያዩ መርሃ ግብሮች አማካኝነት ጤናው የተጠበቀ አምራች ዜጋ ለመፍጠር የተደረገውን ጥረት አግዛለች ብለዋል። ለማስረጃነትም ግብርና ዋናው የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ምንጭ ነው። ይህ ሊሆን የቻለው አርሶ አደሩን በምርት ወቅት አምራቹን ኃይል ከስራ ውጪ ሲያደርግ ከነበረው የወባ በሽታ ነፃ ማድረግ በመቻሉ ነው። የወባ በሽታን ለመከላከል ደግሞ አሜሪካ በከፍተኛ ሁኔታ እገዛ በማድረጓ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ አሜሪካ ለኢትዮጵያ እድገት ድጋፍ እያደረገች ነው ማለት ይቻላል ብለዋል።

«ኢትዮጵያ የግል ባለሀብቱን እንድትስብ ዩናይትድ ስቴትስ ያደረገችው ድጋፍም ከፍተኛ ዋጋ አለው። በተለይ የኦባማ ኢንሼቲቭ የፓወር አፍሪካ ፕሮግራም በዋናነት የሚጠቀስ ነው። መቀራረቡም ዘመናዊ ሲሆን በግብርና ዘርፍ የተሰማሩና ለኢትዮጵያ የግብርና እድገት መሰረት የሚሆን በአነስተኛ ማሳ ላይ የሚደረገውን ልማት እያገዙ ያሉ በርካታ አሜሪካውያን ባለሀብቶች በሀገሪቱ አሉ» ሲሉ በውይይቱ ወቅት ገልጸዋል።

በተጨማሪ ማንኛውንም አይነት ልማት ለማምጣት ሰላምና ደህንነት ወሳኝ ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፤ በዚህ መንፈስ አካባቢውን፤ አህጉሩን እንዲሁም የአፍሪካ ቀንድን ሰላማዊ ለማድረግ በሰላምና በደህንነት ጉዳዮች ላይ ኢትዮጵያ ከአሜሪካን ጋር ተባብራ መሥራቷ በአካባቢው ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን ማስቻሉንም ነው የገለጹት። አሁንም ይህንን ጥረት አጠናክሮ በማስቀጠል አካባቢውንና አህጉሩን ሰላማዊ ማድረግ ያስፈልጋል። በርግጥም በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ጉዳዮችም ላይ ተባብሮ መሥራቱን አጠናክሮ መቀጠል አለብን ብለዋል።

አሜሪካ በዓለም ያላት ሚና ከፍተኛ በመሆኑ የግሎባላይዜሽን የኢኮኖሚ ሕግጋትን የምትወስን አገር ናት። ከዓለም ሰላምና መረጋጋት ጋር ተያይዞ ወሳኟ አሜሪካ ናት። አሜሪካ እጅግ የሰፋና የበለፀገ ኢኮኖሚ ያላት በመሆኑ ወደ አሜሪካ ገበያ ያልገባ የኢንዱስትሪ ልማት ፈጣን ለውጥ ለማምጣት ይቸገራል። ስለዚህ የአሜሪካ ድጋፍና ይሁንታ ለኢትዮጵያ ልማትም ሆነ ደህንነት እጅግ የላቀ አስተዋፅኦ እንዳለው ሊሰመርበት እንደሚገባ በኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይና የሀገራዊ ደህንነት ፖሊሲና ስትራቴጂ ሰነድ ላይ ተቀምጧል።

በፖሊሲው ከአሜሪካ ጋር የሚኖረው ግንኙነት የልማት፣ ብድርና እርዳታ እንዲሁም የቴክኒክ ድጋፍ ለማግኘትና በላቀ ደረጃ ጥቅም ላይ ለማዋል መሠራት እንዳለበት የሚያስቀምጥ ሲሆን፤ ይሁንና በሂደት ከአሜሪካ ጋር የሚኖረው ግንኙነት በንግድና በኢንቨስትመንት ላይ እንዲሆን ይፈለጋል ይላል። በእቅድ ላይ የተመሰረተ ርብርብ በማድረግ በአሜሪካ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶችን ለማምረትና ገበያ ለማፈላለግ ጥረት መደረግ እንዳለበትም እንዲሁ በፖሊሲው ተቀምጧል።

በተጨማሪ አሜሪካ በኢትዮጵያ አካባቢ ሰላም፣ መረጋጋትና ዴሞክራሲ እንዲሰፍን በማድረግ ትልቅ ድጋፍ ልታበረክት ትችላለች። በመሆኑም በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ያላትን ዓላማና ተግባር አሜሪካ እንድትረዳ በየወቅቱ የሚነሱ ጉዳዮች ላይ መመካከርና ዘላቂነት ያለው የፖለቲካና የዲፕሎማሲ ግንኙነት እንዲኖር ጥረት ማድረግ እንደሚያስ ፈልግም በፖሊሲው ተቀምጧል።

ምክክሩ እ.አ.አ መስከረም 25 ቀን 2014 ዓ.ም ሲከናወን አሜሪካና የኢትዮጵያ ግንኙነት ከእርዳታ ሰጪነት ባለፈ ግንኙነታቸውን ወደ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ግንኙነቶች ወደ መፍጠርና በትብብር ወደ መሥራት ማደጉን ማሳያ ሆኗል።

ግንኙነቱ ኢትዮጵያ የንግድ አጋሮችን በማዘጋጀት ሂደት አሜሪካንንም እያስገባች መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ኢኮኖሚዋን ከመምራት ቀጥላ በሰላም ማስፈን በኩል እያደረገች ያለው አስተዋፅኦና እየሄደችበት ያለው መንገድ በአሜሪካ የሚደገፍ መሆኑንም በአሜሪካው ፕሬዚዳንት የተሰነዘረ ሃሳብ ላይ ተስተውሏል። ይህ ጉዳይና በውይይቱ ወቅት የተነሱ ሃሳቦች እንዲሁም በተግባር እየታየ ያለው በኢፌዴሪ ውጭ ጉዳይና የሀገራዊ ደህንነት ፖሊሲና ስትራቴጂ የተቀመጠውን ግብ እየተሳካ መሆኑን ማሳያ ነው።

በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለው ወዳጅነት የረዥም ጊዜ ቢሆንም በደርግ ጊዜ ተቋርጦ ነበር። ከደርግ ውድቀት በኋላ የአሜሪካና የኢትዮጵያ ህዝብና መንግሥት ግንኙነት ፖሊሲውን መሰረት ባደረገ መልኩ በማደግ ላይ መሆኑ እየታየ ነው። በአካባቢው አገራት ላይ ሰላም ለማስፈን ከሚደረገው ጥረት በተጨማሪ ኢትዮጵያ በማደግና ለውጥ በማስመዝገብ ላይ በመሆኗ ወደ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ተሸጋግረዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment