Sunday, March 02, 2014

የአድዋ ድል ሚስጢር የጀግኖች አባቶቻን አንድነት ነው - የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ

(Mar 02, 2014, (አዲስ አበባ))--አድዋ የካቲት 23/2006 ታሪካዊው የአደዋ ድል ሚስጢር የጀግኖች አባቶቻችን አንድነትና ቆራጥ ተጋድሎ  መሆኑን የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተክለብርሃን ገለጹ፡፡ 118ኛው የአድዋ የድል በአል በሶሎዳ ተራራ ስር ዛሬ በደማቅ ስነ-ስርዓት ተከብሯል፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተክለብርሃን በበዓሉ ላይ እንደገለጹት የአድዋ ድል ሚስጥር የጀግኖች አባቶቻችን አንድነትና ቆራጥ ተጋድሎ በመሆኑ የአሁኑ ትውልድ ይህንን አኩሪ ተግባር ጠብቆ የሀገሪቱን ልማት ለመፋጠን መረባረብ አለበት፡፡

አድዋንና መሰል ያለፉ አኩሪ የድል ታሪኮች የተውልንን ቅርሶችና እሴቶች በማጎልበት የህዳሴ ግድብን ጨምሮ በትላልቅ ፕሮጀክቶች አዲስ ታሪክ መስራት አለብን ብለዋል፡፡ ድሉ የተገኘው አባቶች ባህል፣ቋንቋና ሃይማኖት ሳይገድባቸው የጋራ መግባባትን በመፍጠር ቁሳዊና መንፈሳዊ አቅማቸውን አዋህደው በመስራታቸው እንደሆነም  አፈ ጉባኤው ገልጸዋል፡፡

የአድዋ ድል በአል ታላቅነቱን በሚመጥን እንዲከበር ፣መታሰቢያ እንዲቆምለትና በአለም ቅርስነት እንዲመዘገብ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የያዘውን እቅድ ለማሳካት የፌዴሬሽኑ ምክር ቤቱ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የትግራይ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኪሮስ ቢተው በበኩላቸው የአድዋ ድል የብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የትግል ውጤት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያዊያን ጀግኖች በአድዋ ሰንሰለታማ ተራራ እስከ አፍንጫው ለታጠቀው የጣሊያን ጦር በመደምሰስ  ያስመዘገቡት አኩሪ ድል ወጣቱ ትውልድም በድህነትን ላይ መድገም እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

የአድዋ  ተወላጅ የሆኑት አባት አርበኛ አጽብሐ ገብረ ህይወት በአድዋ በወራሪ ጣሊያን ላይ ወላጆች የፈፀሙትን ገድል በስም ዝርዝርና ፎቶግራፍ የተደገፈ ታሪክ ለሕዝቡ በማሳየት ወጣቱ ትውልድ ከዚህ ተምሮ ሀገሩንና ባንዲራውን በመጠበቅ ለልማትና እድገት ጠንክሮ መስራት እንዳለበት መክረዋል፡፡

118ኛው የአድዋ ድል በአል የ20ኛው ቃሉ ክፍለ ጦር አባላት ፣የሶስት ዩኒቨርስቲዎች ማህበረሰብና የአድዋ ነዋሪዎች ጨምሮ ከ20ሺህ በላይ ህዝብ  በተገኘበት በሶሎዳ ተራራ ስር በተለያዩ ዝግጅቶች በተከበረበት ወቅት የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ በፌዴሬሽኑ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ተሰቅሎ እንዲውለበለብ ተደርጓል፡፡
ምንጭ:  ኢዜአ 

No comments:

Post a Comment