Saturday, December 21, 2013

የመሬትና መሬት ነክ ንብረት ረቂቅ አዋጅ እየተመከረበት ነው

(Dec 21, 2013, (አዲስ አበባ))--የከተማ መሬት ምዝገባ ረቂቅ አዋጅ ላይ መመከር የጀመረው ከ2005 ዓ.ም ጀምሮ ነው፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 25 ቀን 2005 ዓ.ም ባካሄደው 38ኛ መደበኛ ስብሰባ ረቂቅ አዋጁ ላይ ተወያይቷል፡፡ ረቂቅ አዋጅ 38/2005 ሆኖ ለዝርዝር እይታ ለከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተመርቷል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው የረቂቅ አዋጁን ከሚያስረዱና ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር የመወያያ መድረክ በማዘጋጀት ሲመረምር ቆይቷል፡፡

ነገር ግን ቋሚ ኮሚቴው እስከአሁን አዋጁ እንዲፀድቅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አላቀረበም፡፡ ሆኖም በተወካዮች ምክር ቤት የአሠራር ደንብ 20 መሠረት ረቂቅ አዋጁ በተመራ በሃያ ቀን ውስጥ መፅደቅ ነበረበት፡፡ ይህ ረቂቅ አዋጅ ወደ ምክር ቤት ከመጣ ከስድስት ወር በላይ እያለፈው ነው፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን በ4ኛዓመት 8ኛ መደበኛ ስብሰባው ከማፅደቅ ይልቅ ረቂቅ አዋጁን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት መርቶታል፡፡

መደበኛ ስብሰባው በተካሄደበት ወቅት አዋጁ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ይመራ አይመራ በሚል ሠፊ ክርክር ተካሂዶ ነበር፡፡ ቋሚ ኮሚቴው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ረቂቅ አዋጁን ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲመራውና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተያየት እንዲሰጥበት የጠየቀው ረቂቅ አዋጁ ዜጎች በመሬት ላይ ለገነቡት ቋሚ ንብረት የባለቤትነትና የመጠቀም መብት ዕውቅናና ዋስትና በመስጠት አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት የታሰበ በመሆኑ የፌዴሬሽን ምክር ቤቱን ይመለከታል በሚል እንደሆነ በቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ተገልጿል፡፡

የፌዴራል መንግሥት በሕገመንግሥቱ አንቀፅ 51(5) እና (52) 2 (መ) መሠረት መሬትና የተፈጥሮ ሀብትን በሚመለከት ሕግ የማውጣት ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ክልሎች ደግሞ በፌዴራል ሕግ መሠረት መሬትን የማስተዳደር ሥልጣን አላቸው የሚሉት የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ፤ነገር ግን ረቂቅ አዋጁ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲመራ ያስፈለገው ከመሬትም በላይ ንብረትንም የሚያካትት ሆኖ በመገኘቱ እንደሆነ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት አስረድተዋል ፡፡

በተጨማሪ የከተማ መሬትና መሬት ነክ ጉዳዮች ምዝገባን አስመልክቶ በፌዴራልና በክልል መካከል ያለው የሥልጣን ግንኙነት ሕገመንግሥቱ በአስቀመጠው ሥርዓት መሠረት መመራት ያለበት በመሆኑ ረቂቅ አዋጁ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት መቅረብ አለበት ሲሉም የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ተናግረዋል፡፡ ረቂቅ አዋጁ ከመፅደቁ በፊት የፌዴሬሽን ምክር ቤት በዝርዝር አይቶ አስተያየት ቢሰጥበት የጎላ ጠቀሜታ ይኖረዋልም ብለዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አንዳንድ አባላት ግን ለምን ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ይመራል? ከሕገመንግሥቱ መርህና ምሰሶዎች አንፃር ቢታይ ጥሩ ነው፡፡ በሕገመንግሥቱ ሕግ የማውጣት ሥልጣን ያለው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሆነ ተደንግጎ እያለና በምክር ቤቱ እንዲያልቅ ማድረግ እየተቻለ ለምን የፌዴሬሽን ምክር ቤት ይሁንታ ይጠየቃል? ቋሚ ኮሚቴው አቅሙን አሟጥጦ ኃላፊነቱን ተወጥቷል ወይ? አዋጁን በደንብ አይቷል ወይ? ኃላፊነትን አሳልፎ መስጠት አይሆንምን? በመሬት ጉዳይ ላይ በሕገመንግሥቱ በግልጽ ሕግ የማውጣት ሥልጣን የተሰጠው ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሆኖ እንዴት የፌዴሬሽን ምክር ቤት ሃሳብ ይስጥበት ትላላችሁ? የሚሉ ጥያቄዎች ቀርበው ነበር ፡፡

ከቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ በተጨማሪ የቋሚ ኮሚቴው አባላትና ረቂቅ አዋጁ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት መመራት አለበት ያሉ የምክር ቤት አባላት ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ መሬት የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በመሆኑ አዋጁ ሁሉንም የሚነካ ነው፡፡ በተጨማሪ አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመፍጠርም የሚያግዝ በመሆኑ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት መመራት አለበት፡፡ የባለቤትነትን ይዞታን ማረጋገጥና በውስጥ የአስተዳደር ሥራዎችን የሚያሳይ በመሆኑ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ይሁንታ መገኘት አለበት፡፡ ከሊዝ አዋጁ ጋር ተያይዞ እንደነበረው ዓይነት ውዥንብር እንዳይፈጠር አዋጁ ከመፅደቁ በፊት የፌዴሬሽን ምክርቤት ቢያየው የተሻለ እንደሆነ የምክር ቤቱ አባላት አመልክተዋል፡፡ አዋጁ የመሬትና የንብረት ጉዳይን የሚያካትትና እስከታች መተግበር ያለበት በመሆኑ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ቢያየው ጥሩ ነው ሲሉም ሃሳባቸውን ሰጥተዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ እንደገለጹት ቋሚ ኮሚቴው ረቂቅ አዋጁ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲመራ ይወሰን የሚል ጥያቄ ያነሳው በረቂቅ አዋጁ ላይ የሕዝብ ውይይት ሲደረግ የሚነሱ ጥያቄዎች ስለነበሩ ነው፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ሕግ የማውጣት ሥልጣን በማይጋፋ መልኩ አስተያየት ቢሰጥበት ጥሩ ነው የተባለው ከፀደቀ በኋላ ክልሎች ጥያቄ እንዳያነሱና የግልጽነት ችግር እንዳያጋጥምም ይረዳል፡፡ ይህ ደግሞ ማንንም የሚጠቅም እንጂ የሚጎዳ አይደለም ፡፡

በአዋጁ ውስጥ የክልሎችን ሥልጣን የሚነካ የሚመስል አንቀፆች አሉ፡፡ በተጨማሪ አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ የመፍጠር ዓላማ ያለው በመሆኑና ድጋሚ ማሻሻያ ከማድረግ ሕዝቡ በደንብ ቢመክርበት የፌዴሬሽን ምክር ቤትም በዝርዝር ቢያየው የሚያስከፋ አይደለም ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በእርግጥ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመሬትና የተፈጥሮ ሀብትን የሚመለከት ሕግን የማውጣት ሥልጣንና ኃላፊነት አለው፡፡ ነገር ግን ረቂቅ አዋጁ ንብረትን የሚጨምርና አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብን ለመፍጠር የታሰበ ነው፡፡ እዚህ ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ጉዳዩን አይቶ ይሁንታ ቢሰጥ ይጠናከራል ፤ለመተግበርም ይቀላል በሚል ታስቦ ነው እንጂ ሥልጣንን አሳልፎ የመስጠት ጉዳይ አለመሆኑ ተገልፆ «አስተያየት ይሰጥበት» የሚለው ሐረግ ተቀይሮ «ይሁንታ» በሚለው ተተክቶ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲመራ በሙሉ ድምፅ ተወስኗል፡፡ 
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment