Wednesday, December 18, 2013

ስደትን ለማስቀረት ዘላቂ ማቋቋሚያና የአስተሳሰብ ለውጥ

(Dec 18, 2013, (አዲስ አበባ))--ከጎረቤት ወይም ከዘመድ አዝማድ መካከል አንዷ ወደ አረብ አገር ሄዳ ገንዘብ መላክ ከጀመረች የእኩዮቿ ብቻ ሳይሆን የእናትና አባቶቻቸውም ልብ ይሸፍታል። ብዙ ልጆች ያሉት ቤተሰብ አረብ አገር ቢልካቸው ቤተሰቡ ምን ያህል ሊለወጥ እንደሚችል ያሰላል። ከዚያም አልፎ ተበድሮ ተለቅቶ ልጆቹን ወደ «ተስፋዪቱ» ምድር ይልካል። እናም በአንዷ «ስኬት» ብዙዎች «ተምረው» ልባቸው ቀድሞ አካላቸው ደግሞ ተከትሎ ይኮበልላል።

በአንጻሩ ግን በተለያየ ችግርና ውጣውረድ ውስጥ አልፈው፤ በሕገወጥ መንገድ ተጉዘው ተስፋ ወዳደረጉበት ሀገር ከደረሱ በኋላ የፈላ ውሃ ተደፍቶባቸው፣ ተደብድበውና ተገርፈው፣ ከሥራ ብዛት የተነሳ ራሳቸውን ስተው፣ ከባድ የሥነ ልቦና እና የአካል ጉዳት ደርሶባቸው ከሚመጡ ዜጐች የሚማርና እግሩን የሚሰበስብ ወጣት፤ መክሮ የሚያስቀር ወላጅ ቁጥር ጥቂት ነው። እንዲያውም ከዚህ አስከፊ የዕለት ተዕለት ገጠመኝ የሚማር የለም ብሎ በድፍረት መናገር ይቻላል። ለእዚህም በየጊዜው በሕጋዊና በሕገወጥ መንገድ የሚጎርፈው ሕዝብ ብዛት እማኝ ነው።

«ብልህ በሰው ይማራል፤ ሞኝ በራሱ ይማራል» እንዲሉ ብዙዎች በራሳቸው ካልደረሰ በስተቀር አያምኑም። በአንድ ወቅት የደሴ አካባቢ ነዋሪ የሆነችና ልጆቿን ትታ ወደ አረብ አገር የሄደች፤ በኋላም የአካል ጉዳት ደርሶባትና በሰው ሸክም ለመንቀሳቀስ የተገደደች ሴት ስለ ተሞክሮዋ የተናገረችው ይህንን ሃሳብ ያጠናክረዋል። የአካባቢዋን ወጣቶች በእርሷ የደረሰውን እያዩ በሀገራቸው ሰርተው እንዲኖሩ ብትመክራቸውም እኒያ ልባቸው የሸፈተ ወጣቶች ምላሽ አንገት የሚያስደፋ ሆኖባት ነበር። «ይህ የአንቺ ዕድል ነው» እኛ ግን መሞከር አለብን የሚል ነበር ምላሻቸው፤ በስደት ላይ ያለው የተሳሳተ ይህ ዓይነቱ ግንዛቤ ምን ያህል ስር እንደሰደደ የሚያሳይ ነው።

የእዚህ ችግር ምንጭ በዋነኝነት የአስተሳሰብ ነው ማለት ይቻላል። በሀገር ሰርቶ መኖር ብሎም መክበር እንደሚቻል ያለማወቅ ወይም ለማወቅ ያለመፈለግ ትልቁን ድርሻ ይወስዳል። በዚህም ላይ የደላሎች ሰበካ በተለይም በገጠር አካባቢ ያለውን ወጣት በሙሉ ለማለት በሚቻል ደረጃ ልቡን ማሸፈት ችሏል። ብዙዎች በአገራቸው ሠርተው እልፍ እንደማይልላቸው ነው የሚያስቡት። የመጨረሻው አማራጫቸውም በሕጋዊም ሆነ በሕገወጥ መንገድ ከሀገር ወጥቶ «ገንዘብ አፍሶ መምጣት» ነው። የደላሎቹ ሰበካ ከልካይ በሌለው ሁኔታ ወደ ወጣቶቹ በመድረሱ እንኳንስ ሥራ አጦቹ ወጣቶች የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ታዳጊዎችን ሳይቀር ከአላማቸው ፈቀቅ አድርጓቸዋል።

ዕድሜያቸው ለሥራ ያልደረሱ ታዳጊዎች ከ18 ዓመት በላይ እንደሆናቸው አስመስሎ መታወቂያ በማውጣት ለእጅ አዙር ባርነት የዳረጋቸውም ከሕገወጡ የሥራ ኃላፊ በተጨማሪ የተሳሳተው አስተሳሰብ ነው። ታዳጊዎቹ ወደ አረብ አገር ለመሄድ የወሰኑበትን ምክንያት ሲጠየቁ የተሻለ ኑሮ ፍለጋ እንደሆነ ይናገራሉ። ለመሆኑ እነሱ ገና ትምህርታቸውን ያላጠናቀቁና አንዱንም የሕይወት ገጽታ ሳያጣጥሙ እንዴት ለእዚህ ውሳኔ ሊበቁ ቻሉ ? የሚለው ጥያቄ ከአዕምሮ ጓዳ ብቅ ሊል ግድ ነው።

ውጤታማ ተማሪ ሆኖ ራስንም፣ ቤተሰብንም፣ ሀገርንም ማገልገል እንደሚቻል ድሮ የነበረውን አስተሳሰብ ምን ሸርሽሮት ገና ተማሪ ሳሉ ገንዘብ የሚያገኙበትን መንገድ ማየትና ስደትን የመጨረሻው አማራጭ አድርገው መውሰድ ቻሉ? ሲባል ይህ ሃሳብ የራሳቸው እንዳልሆነ መገመት ይቻላል። ከወላጆች ጀምሮ እየገዘፈ የመጣውና «በሀገር ሠርቶ የተሻለ ኑሩ መኖር አይቻልም» ብሎ የማሰብ አዝማሚያ እነዚህ ጨቅላዎች ላይ ሳይቀር ጥላውን ማጥላቱን መገንዘብ ይቻላል። ሌላው ዓለም ከኢትዮጵያ እጅግ የተሻለ ምቾት ያስገኛል የሚለው አመለካከትም የተጋነነ ነው።

አስተሳሰቡን በማስረጽ ብቻ ሳይሆን ለተግባራዊነቱም የተዋናዩ ብዛት ቀላል አይደለም። ደላሎች መሪ ተዋንያን ይሁኑ እንጂ ቤተሰብ፣ የአካባቢው ህብረተሰብ እንዲሁም አንዳንድ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ የሚገኙ ጥቅመኞች ሳይቀሩ እጃቸው አለበት። የታዳጊዎች ዕድሜ ከፍ አድርጎ መታወቂያ ማውጣትን ጨምሮ በብዙ ሕገወጥ እንቅስቃሴ ውስጥ እጃቸው እንደሚኖርበት ምንም ጥርጥር የለውም። የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ለጊዜው መታገዱም የብዙዎችን ፀጉር የሚያስነጭ ክስተት የሆነውም ከዚሁ እውነት አንፃር ነው። ምናልባት ግን ይህ መንገድ ሲዘጋባቸው ደግሞ ከሳዑዲ አረቢያ የሚገቡ ተመላሾቹን ታከክ አድርጎ ስለሚገኝ ገቢ ሊያሰሉ ይችላሉ። በሕገወጥ መንገድ መክበር የጀመረ በሕጋዊ መንገድ ሠርቶ የሚጠግብ አይመስለውምና።

አሁን ከሳዑዲ አረቢያ ወደ አገራቸው ለሚገቡ ከ100ሺ ለሚበልጡ ወገኖቻችን የሥነ ልቦና ጉዳት፣ የጉልበትና የጊዜ ብክነትም እነዚህ ሁሉ አካላት ተጠያቂ ናቸው። መንግሥት በውል ሊገምት እንኳን ባልቻለበት ሁኔታ ወደ ሳዑዲ የሄዱት ወገኖቻችን እንዳይሆኑ ሆነው የተሸኙት በእነዚህ አካላት ነው። አሁን ከስደት ተመላሽ የሆኑት ወገኖች ብዛት ሕዝብንም መንግሥትንም ያስደነገጠ ሆኗል። መንግሥትም ወደ አገራቸው የሚገቡ ዜጎችን በተመለከተ በሰጠው የመጀመሪያ መግለጫ ከሰባት እስከ 10ሺ አካባቢ እንደሚሆኑ፤ በኋላም ቁጥራቸው ወደ 23 ሺ ሊያድግ እንደሚችል የሚያሳይ ነበር። ይህ መግለጫና እውነታው በእጅጉ የተራራቁ መሆናቸው በመንግሥት በኩልም መረጃው በጠራ መንገድ እንዳልተያዘ የሚያመለክት ነው።

በእርግጥ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም ግምቱ ሊራራቅ የቻለው ዜጎቹ በሕገወጥ መንገድ ወደ አገሪቷ የገቡ በመሆናቸውና የተደራጀ መረጃ ባለመኖሩ እንደሆነ አሳውቋል። ያም ሆነ ይህ ግን አጋጣሚው ኢትዮጵያ አምራች ኃይሏ በአስደንጋጭ ሁኔታ መኮብለሉን አሳይቷል። እነዚህን አካላት ወደ አገራቸው ከመመለሱ አስቀድሞ ወደ ውጭ አገር የሚደረገውን የሥራ ስምሪት ለጊዜውም ቢሆን ማገዱ ተገቢ መሆኑን የሚያጎላውም ይኸው ሁኔታ ነው።

ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ በመሸጋገር ጉዞ ላይ የምትገኘው ሀገራችን ከፍተኛ የሰው ኃይል ያስፈልጋታል። ወደእዚህ ሥራ ስትገባም የሰው ኃይሏን እንደ አንድ ሀብት በመቁጠር ነበር። ነገር ግን በአስተሳሰብና የጠባቂነት ችግር ምክንያት ዜጎች የሀገራቸውን ህዳሴ በሚያረጋግጠውና ራሳቸውንም ተጠቃሚ ከሚያደርገው መስመር ወጥተው በስቃይና በእንግልት ለመኖር ወኔያቸውንም ጉልበታቸውንም ሰጥተዋል። ይህ ሁኔታ እንኳንስ ለኢንዱስትሪው ዘርፍ አሁንም ላለው በቤተሰብ ደረጃ ለሚደረገው የግብርና ሥራ ፈተና ሆኗል።

ወጣት ወንዶችና ሴቶች ወደተለያዩ አረብ አገራት፣ ወደ ደቡብ አፍሪካ እንዲሁም ወደሌሎችም አገሮች በመሄዳቸው ግብርናው በእጅጉ እየተጎዳ ይገኛል። የቤተሰብ አቅም እየደከመ ሲመጣ ምትክ ሆኖ የቤተሰቡን ህልውና የሚያስቀጥለውና የራሱንም ኑሮ የሚመሰርተው የገጠር ወጣት የቤተሰቡ መከታ መሆን ስላልቻለ በርካታ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መፋለሶችም እየገጠሙ ነው።

አሁን ደግሞ ከሳዑዲ አረቢያ ብቻ ይህንን ያህል ቁጥር ያለው ሕዝብ እየተመለሰ ነው። ይህ በራሱ በሌላ አቅጣጫ ማሰብን ይጠይቃል። ተመላሾቹን ማቋቋምና የተዛባውን አስተሳሰብ ማስተካከል። ለእዚህ መንግሥት፣ ሕዝብና ራሳቸው ተመላሾቹም ጭምር ተግተው ሊሠሩ ይገባል። በተለይ ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ጉዳዩን እንደቀላል ማየት የለባቸውም።

ተመላሾቹ ሌሎች ወገኖች እውነተኛ ተሞክሯቸውን በማካፈል ብሎም በሀገር ሠርቶ መበልጸግ እንደሚቻል በተግባር በመግለጽ አርአያ መሆን ይጠበቅባቸዋል። መንግሥት እነዚህ አካላት በተደራጀ መልኩ ወደ ሥራ የሚገቡበትን መንገድ ማመቻቸት አለበት ሲባል የተመላሾች የሥራ ዝግጁነትም ሳይዘነጋ ነው። ህብረተሰቡም እነዚህን ወገኖች በደስታ ከመቀበል ጀምሮ ለመኖር በሚያደርጉት መፍጨርጨር ከጎናቸው ሊቆም ይገባል። ይህ ሲሆን ነው የስደት ሥሩ እየደረቀ በሀገር ሰርቶ መለወጥ እየለመለመ ሊሄድ የሚችለው።

እስካሁን ተመላሾቹን ለመቀበል የተደረገው ርብርብ እጅግ የሚያስደስትና የሚያኮራ ነው ። ባለሥልጣናት በፍቅር ዜጎቻቸውን ተቀብለው በመካከላቸው ተገኝተው ማዕድ መቁረስ መቻላቸው በግሌ እጀግ ያስደሰተኝና አርቆ አስተዋይነትን ያነበብኩበትም ነው። ተመላሾች «ለካስ ለእኔ የሚያስብ ሕዝብና አገር አለኝ» ብለው እንዲገነዘቡ ከማድረግ ባሻገር ከሕዝብና መንግሥት ድጋፍ አግኝቼ መኖር እችላለሁ ብለው የተስፋ ጭላንጭል እንዲያዩ የሚያደርጋቸው ነው። የተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ባለሀብቶች፣ አርቲስቶችና ሌሎች ግለሰቦች ቀን ከሌሊት ሲለፉ ማየት እውነትም ኢትዮጵያዊነት ጥልቅ ነው ለማለት ያስገድዳል። ሙያ ያለው በሙያው፣ ጉልበት ያለው በጉልበቱ፣ ገንዘብ ያለው በገንዘቡ፣ እውቀት ያለው በእውቀቱ አግዟል፤ አቅመ ደካማውም ዜጎቹ በሰላም ወደአገራቸው እንዲገቡ በጸሎት ረድቷል።እየረዳም ነው። ታዲያ ይህ መተሳሰብና መደጋገፍ ታይቶ እንደሚጠፋ የጠዋት ጤዛ መሆን የለበትም። እነዚህን ዜጎች ለማቋቋም በሚደረገው ጥረትም መደገም አለበት። በዚህም ማንም ያልቀደማቸውን በጎ አሳቢዎች መከተል ያስፈልጋል።

ከስደት ተመላሾችን ወደ ሀገራቸው ለማስገባት በሚደረገው ጥረት እኛም የድርሻችንን እንወጣ ብለው ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያመሩትና ሕዝባዊ ወገንተኝነታቸውን በቀዳሚነት ያሳዩት ባለሀብቶች ለወሰዱት ፈጣን እርምጃ ሊመሰገኑ ቢገባቸውም ተመላሾቹን በየድርጅታቸው ለመቅጠርና ለማሠልጠን የደረሱበት ውሳኔ ደግሞ ይበልጥ እንድናከብራቸው ያደርገናል። እነዚህ ባለሀብቶች በአጭር ጊዜ ውስጥ ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ ለመስጠት ቃል መግባታቸውም «ለወገን ደራሽ ወገን» የሚለውን አባባል እንድናስታውስ ያደርገናል።

የእምነት ተቋማትም እንዲሁ ተመላሾቹን ለማቋቋም በሚደረገው ጥረት የሥነ ልቦና ድጋፍ ከማድረግ ጀምሮ የገንዘብና የቁሳቁስ እርዳታ ለማድረግ ቃል ገብተዋል። ከዚህም ባሻገር በሃይማኖታዊ አስተምህሮታቸው ዜጎች በሀገራቸው ሰርተው እንዲኖሩና ከስቃይና እንግልት ራሳቸውን እንዲጠብቁ ማስተማር አለባቸው። በሥነ ልቦና ረገድ ያለው ትልቅ ሥራ በሃይማኖት ተቋማት ላይ እንደወደቀ ይሰማኛል። ሌሎች መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም የጀመሩትን እንቅስቃሴ አጠናክረው መቀጠል ይጠበቅባቸዋል።

የተመላሾቹ ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ በተለይም በዘላቂነት የማቋቋሙ ጉዳይ ፈታኝ እንደሚሆን አያጠራጥርም። ስለሆነም በርካቶች ከመንግሥት ጎን እንዲሰለፉ ሁኔታዎች ያስገድዳሉ። በተለይም መንግሥት ተደራጅተው ወደ ሥራ እንዲገቡ በማድረግ፣ የመነሻ ካፒታል በማቅረብ፣ የሙያ ሥልጠና እንዲያገኙ በመደገፍ በአካባቢያቸው ያለውን ሀብት(መሬት፣ ውሃ፣ ጉልበት፣ ውስን ካፒታል) ተጠቅመው እንዲሠሩ እና ግንዛቤያቸውን እንዲያስተካክሉ በማገዝ ሥራ ላይ መተኮር አለበት። ለእዚህ ደግሞ ፈጣን ፍትሐዊና ግልፅ አገልግሎት አሰጣጥ መዘርጋት አለበት። በየቦታው ያለው ውጣ ውረድና እንግልት ሊቆም ግድ ነው።

በዚህ ዙሪያ የመንግሥት ቁርጠኝነት ከፍተኛ በመሆኑ ውጤታማ እንደሚሆን ከወዲሁ መገመት ቢቻልም አንዳንድ ስጋት ውስጥ የሚከቱ ጉዳዮች መኖራቸውን ግን መገመት ይቻላል። በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ነገር ግን የራሳቸውን ጥቅም ከማስከበር ባለፈ የሌሎች ጉዳት የማይቆረቁራቸው ወገኖች ቁጥርም ቀላል አይሆንምና በሄዱበት ሁሉ ችግር እየደነቀሩ ለእንቅስቃሴያቸው እንቅፋት ሊሆኑባቸው ይችላሉ።

ስለዚህ መንግሥት መልካም አስተዳደርን በማስፈን እነዚህ ዜጎች በሀገራቸው የሚኮሩ፣ሰርተው የሚበለጽጉ፣ ለሀገራቸው ጉዳይ ሁሉ ያገባኛል የሚሉና ባይተዋርነት የማይሰማቸው እንዲሆኑ ማድረግ ይኖርበታል። ያውም ለሌላው ዜጋ ከሚወጣው አገልግሎት በተሻለ በመሥራት። በየቢሮው ተንሰራፍቶ የሚገኘው የመልካም አስተዳደር ችግር እነዚህን ወገኖች የሚፈትናቸው ከሆነ ግን በቀላሉ ተስፋ ወደመቁረጥ ያዘነብላሉ። ይህ ደግሞ በራሱ ከግለሰብ ባሻገር ለሀገርና ለሕዝብ ከፍተኛ ቀውስ ያስከትላል። ስለዚህ የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥታት ትኩረት ሰጥተው ሊከታተሉት ይገባል። ከወረዳ ጀምሮ በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች የሚገኙ ሠራተኞች እነዚህን አካላት በዘላቂነት ለማቋቋም በሚደረገው ርብርብ ውስጥ በቀናነት ሊሳተፉ ይገባል።

በአንጻሩ ተመላሾቹም ምንም እንኳን መንግሥትና ሕዝብ በሙሉ ደስታ ቢቀበሏቸውና በዘላቂነት ለማቋቋምም ደፋ ቀና ያሉ ቢሆንም ነገሮች ሁሉ አልጋ በአልጋ ሆነው ሊጠብቋቸው እንደማይችሉ ማሰብ ይኖርባቸዋል። የሀገራቸውን ድህነትና ታዳጊነት ማጤንም ያስፈልጋል። ስለዚህ በአጭሩ ተስፋ የሚቆርጡ መሆንም የለባቸውም። በሁሉም ውስጥ መስረጽ ያለበት አስተሳሰብ ምንም አይነት ችግር ቢኖር ታግለው በማሸነፍ ለራሳቸውም፣ ለቤተሰባቸውም፣ ለሀገራቸውም የሚጠቅሙ መሆን እንደሚችሉ በእርግጠኝነት ማመንና ለተግባራዊነቱም በዚያው ልክ ሳይታክቱ መስራት ነው።

በአሁኑ ወቅት በሳዑዲ አረቢያ ኑሯቸውን አድርገው የነበሩና አሁን ወደ ሀገራቸው የገቡ ዜጎች ጉዳይ ትልቁ የአገራችን አጀንዳ ሆኗል። በቀጣይ ግን እንዲህ ያለው አስደንጋጭ ሁኔታ እንዳይከሰት የዜጎችን ግንዛቤ ከማስፋት ጀምሮ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቱም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት። ስደትና ድህነትም ይብቃን። 
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment