Tuesday, June 18, 2013

ዳያስፖራው ግብር የመክፈል ባህልን ለማዳበር እንዲያግዝ ተጠየቀ

(Jun 17, 2013, (አዲስ አበባ))--በውጭ አገሮች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውን በሚኖሩባቸው አገሮች ያለውን ግብር የመክፈል ባህል በአገር ውስጥ ለማስፋፋት የላቀ ሚና መጫወት እንደሚጠበቅባቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም አመለከቱ።

ዶክተር ቴዎድሮስ በዳያስፖራ ፖሊሲ አተገባበር ላይ ከትናንት በስቲያ በሚሌኒየም አዳራሽ በተካሄደው ውይይት ላይ እንደገለፁት፤ ዳያስፖራው የመጣባቸው አካባቢዎች የዕድገት ምንጭ ግብር በትክክለኛ መንገድ የመክፈል ባህል እንደመሆኑ መጠን ኢትዮጵያን ለማሣደግ የግብር አከፋፈል ባህል የሚዳብርበትን አቅጣጫ ማመላከት ይጠበቅባቸዋል።

የዳያስፖራ አባላቱ የሚያነሱት የማበረታቻ ጥያቄ ከፖሊሲ አንፃር ታይቶ ምላሽ የሚያገኝ እንደሆነ የገለፁት ዶክተር ቴዎድሮስ ፣የዲያስፖራ አባላት ግብር ለመክፈል ያላቸው ተነሣሽነት ከመጡባቸው አገሮች ጋር የተቃኘ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። በሌሎች የአፍሪካ አገሮች ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት 25 በመቶ ግብር እንደሚከፈልና በኢትዮጵያ ያለው ደግሞ 11 በመቶ ብቻ መሆኑን ጠቁመው፣ ለዕድገት መሠረት የሆነውን ግብር የመክፈል ባህል በማሣደግ ረገድ ዳያስፖራው ያለበት የቤት ስራ ሠፊ እንደሆነ አመላክተዋል።

ዳያስፖራው በአገር ውስጥ ልማትና ዴሞክራሲ ተሣታፊና ተጠቃሚ እንዲሆን ለማስቻል የሚወጣው ፖሊሲ አተገባበሩ ላይ ውጤታማነት እንዲረጋገጥ አሁን ያሉ ህጐች ደንቦችና መመሪያዎች የሚሻሻሉበትና ሌሎችም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የሚወጡበት ሁኔታ መኖሩን ጠቁመዋል።

በመንግስት መስሪያ ቤቶች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና በኤምባሲዎች ያለውን ችግር ለመፍታት ርምጃዎች እንደሚወሰዱ ያመለከቱት ሚኒስትሩ፣ ችግሮችን ለመፍታት ዳያስፖራው የራሱን አስዋፅኦ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበር ጋር በመቀናጀት ዳያስፖራው የሚገጥሙትን ችግሮች ለመፍታት የሚችልበት ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው። የዳያስፖራ ድረ-ገጽም ከትናንት በስቲያ መከፈቱም ከመረጃ ክፍተት ጋር ተያይዞ የሚገጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ያስችላል።

ዳያስፖራው በግል የሚገጥመውን ፈታኝ ሁኔታ በሚኒስቴር ስር ለተደራጀው የዳያስፖራ ተሣትፎ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት አሳውቆ የሚፈታበት ሥርዓት መዘርጋቱን የተናገሩት ዶክተር ቴዎድሮስ፣ መንግስት ችግሮችን ለመፍታት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። እንደ ዶክተር ቴዎድሮስ ገለጻ፤ ወደ መካከለኛው ምስራቅ አገሮች በመሄድ ለከፍተኛ ጉዳት እየተዳረጉ ለሚገኙ ዜጎች ጉዳይ ትኩረት ተሠጥቶ እየተሠራ ነው።

የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበር ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር አባቡ ምንዳ የዳያስፖራ አባላቱየሚገጥሟቸውን ችግሮች በመፍታት ለሌሎች ዜጐች የሚተርፈው ችግሮቹን በተደራጀ መልኩ መፍታት ሲችል እንደሆነ በመጠቆም የማኅበሩ አባላት እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል። በውይይት መድረኩ የተሣተፉ የዳያስፖራ አባላት በፖሊሲው ላይ ሰፊ ውይይት ማድረጋቸውንና ችግርም እንደሌለበት አብራርተው፣ የአፈፃፀም ችግር እንዳያጋጥም መሥራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። በተለይም በየኤምባሲው የሚያጋጥሙ ከአቅም ማነስ ጋር የተያያዙ ችግሮች መፍትሔ ያሻቸዋል ብለዋል።

በፖሊሲው ዝግጅት ድጋፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት እንዲሁም የኢትዮጵያ የዳያስፖራ ማኅበር ከዶክተር ቴዎድሮስ እጅ የምስጋና የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል። በመጨረሻም ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ቦንድ ግዢ ከፍተኛ ተሣትፎ ላደረጉ ድርጅቶችና ግለሰቦች ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የተሣትፎ ምስክር ወረቀት ሰጥተዋል። 
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment