Wednesday, June 19, 2013

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ይቅርታ ጠየቀ

(Jun 19, 2013, (አዲስ አበባ))--በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ዋልያዎቹ ከቦትስዋና ጋር አዲስ አበባ ላይ ባደረጉት ጨዋታ ተገቢ ያልሆነ ተጫዋች አሰልፋችኋል በሚል ፊፋ ያቀረበባቸው ክስ ትክክለኛ መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ትናንት በጊዮን ሆቴል በሰጠው መግለጫ አሳውቋል፡፡

ፌዴሬሽኑ ኃላፊዎች የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ የጠየቁበትን መግለጫ በሠጡበት ወቅት (አዲስ ዘመን ጋዜጣ)
ፌዴሬሽኑ በተፈጠረው ስህተት ህዝብን ይቅርታ የጠየቀ ሲሆን ስህተቱ ሆን ተብሎ ሳይሆን በችልተኝነት እንደተፈጠረ አሳውቋል፡፡ ፌዴሬሽኑ ለጥፋቱ ተጠያቂ ያደረጋቸው የተለያዩ ግለሰቦችም በመግለጫው ላይ ተገኝተው ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡

የፌዴሬሽኑ ምክትል ፕሬዚዳንትና የዋልያዎቹ ቡድን መሪ የሆኑት አቶ ብርሃኑ ከበደ ችግሩ በቀጥታ የሚመለከታቸው በመሆኑ ዋነኛ ተጠያቂ ተደርገዋል፡፡ አቶ ብርሃኑም ችግሩ ሆን ተብሎ የተፈጠረ አለመሆኑን አስረድተው ህዝብን ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡ ችግሩ የተፈጠረው በፌዴሬሽኑ ጽህፈት ቤትና በቡድን መሪው መካከል በተፈጠረ የመረጃ ክፍተት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ዋልያዎቹ ከደቡብ አፍሪካ ባደረጉት ጨዋታ አንድ ለአንድ ሲለያዩ ምንያህል ተሾመ ቢጫ ካርድ ተመልክቷል፡፡ ከዚያ በኋላም ዋልያዎቹ ከቦትስዋና ጋር አዲስ አበባ ላይ ባደረጉት ጨዋታ ምንያል ተጨማሪ የቢጫ ካርድ ሰለባ ሆኗል፡፡

ፊፋ ምንያህል ሁለት ቢጫ ካርድ ማየቱን ተከትሎ ለኢትዮጰያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ተጫዋቹ አንድ ጨዋታ መቀጣት እንዳለበት በላከው የጨዋታ ሪፖርት አሳውቋል፡፡ የፌዴሬሽኑ ጽህፈት ቤትም ይህን አስመልክቶ ለቡድን መሪውና ለአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ደብዳቤ ልኬያለሁ ብሏል፡፡ ቡድን መሪው ደብዳቤውን መቀበል ያለመቀበላቸውን እርግጠኛ ባይሆኑም በቦትስዋናው የመልስ ጨዋታ ወቅት ሥራ በዝቶባቸው ስለ ነበር ጽህፈት ቤቱ ያደረሳቸው ደብዳቤ የት እንደገባ እርግጠኛ መሆን ያለመቻላቸውን ገልፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ የተሠራው ስህተት ትልቅ ዋጋ የሚያስከፍል በመሆኑ የቡድን መሪው ስህተታቸውን አምነው ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡

የዋልያዎቹ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውና ሌሎች አሠልጣኝ ባልደረቦች በሁለተኛ ደረጃ ተጠያቂ ተደርገው ተይዘዋል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት በጉዳዩ ላይ ጽህፈት ቤቱም ይሁን ቡድን መሪው ያደረሳቸው መረጃ ባለመኖሩና በችልተኝነት የተፈጠረ ችግር መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ህዝቡን ይቅርታ በመጠየቅም ቀጣዩንና የመጨረሻ ጨዋታ አሸንፈው ምድቡን ለማለፍ እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡

የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ሳህሉ ገብረወልድ በመግለጫው ላይ እንደተናገሩት ጥፋቱ የተፈፀመው በፌዴሬሽኑ የአሰራር ሥርዓት ምክንያት ነው፡፡ የተፈጠረው ስህተት ትልቅ በመሆኑም አቶ ሳህሉ ይቅርታ ጠይቀው ዋልያዎቹ የመጨረሻውን ማጣሪያ አሸንፈው ወደ ቀጣዩ ዙር እንደሚያልፉ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡ እንደ አቶ ሳህሉ ገለፃ ፊፋ ስህተት እንደተፈፀመ በደብዳቤ ያሳወቀው ባለፈው ሰኔ አምስት ቀን ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ዋልያዎቹ ከደቡብ አፍሪካ ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ተፅዕኖ እንዳይፈጥርባቸውና ህዝቡም ተስፋ እንዳይቆርጥ ሲባል ፌዴሬሽኑ ጉዳዩን አዘግይቶታል፡፡

ፌዴሬሽኑ ጉዳዩን እንዲያስተባብል ሦስት ቀናት ቢቀሩትም ስህተቱ በእርግጥም ስለተፈፀመ ማስተባበያ እንደማይኖርም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡ በዚህም መሰረት ፊፋን ይቅርታ ጠይቆ ለመጪው ጨዋታ መዘጋጀት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

ፊፋ ፌዴሬሽኑ ምንም ማስተባበያ ካላቀረበ ዋልያዎቹ ቦትስዋና ላይ ሄደው ያስመዘገቡት ሁለት ለአንድ ውጤት ተሰርዞ ቦትስዋና ሦስት ለዜሮ እንዳሸነፈች አድርጎ ይወስደዋል፡፡ ይህ ማለት ግን ዋልያዎቹን ምድባቸውን ከመምራት አያግዳቸውም፡፡ ዋልያዎቹ የሚቀነሰውን ሦስት ነጥብ ሳይጨምር በአስር ነጥብ ምድባቸውን አንደኛ ሆነው መምራት ያስችላቸዋል፡፡ በቀጣይ የመጨረሻ ማጣሪያ ጨዋታቸው መስከረም 6ቀን 2006 ዓ.ም ላይ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክን ካሸነፉ ቀጣዩን ዙር መቀላቀላቸውን ያረጋግጣሉ፡፡

በስምንት ነጥብ ሁለተኛ ላይ የምትገኘው ደቡብ አፍሪካ በቀጣይ የመጨረሻውን ማጣሪያ የምታደርገው ከቦትስዋና ጋር ነው፡፡ ደቡብ አፍሪካ አቻ ከወጣች ዋልያዎቹ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ጨዋታ ላይ ቢሸነፉም፣ ቢያሸንፉም ወይንም አቻ ቢወጡም ወደ ቀጣዩ ማጣሪያ ያልፋሉ።
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ


No comments:

Post a Comment