Saturday, June 01, 2013

ወጣቱ ወድቆ ያገኘውን 184 ሺ ዶላር በታማኝነት ማስረከቡ አየር መንገዱን አኩርቷል

(June 01, 2013, (አዲስ አበባ))--ወጣት ብርሃኑ ጀምበሬ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ መስራት ከጀመረ ገና አምስት ወራትን ብቻ ነው ያስቆጠረው። ከእነዚህ ወራት ውስጥ ባለፈው ግንቦት 20 ያጋጠመው ክስተት ልዩ ስፍራ እንዳለው ይናገራል። ወጣቱ እንደወትሮው የአውሮፕላኑን ክፍል እያፀዳ ባለበት ወቅት አንድ በካኪ ወረቀት የተጠቀለለ ነገር ይመለከታል። ጠጋ ብሎ ሲመለከተውም ገንዘብ ይሆናል። ወጣቱ ያገኘው ይህ ገንዘብ ወደ 184 ሺ የአሜሪካን ዶላር የሚጠጋ ነው።

«ብዙ በመሆኑ በጣም ደነገጥኩ። ምን ማድረግ እንዳለብኝም ጥቂት ደቂቃዎች በማሰላሰል አሳለፍኩ። በመጨረሻም ለቅርብ አለቃዬ ማሳወቅ እንዳለብኝ ወሰንኩ» የሚለው ወጣት ብርሃኑ፤ ጊዜ ሳያጠፋ ወዲያው ውሳኔውን ተግባራዊ ያደርጋል። የቅርብ አለቃውም የፀጥታ ሠራተኛውን በመጥራት ሁሉም አንድ ላይ ሆነው ለሚመለከተው አካል ገንዘቡን ማስረከባቸውን ነው ወጣት ብርሃኑ የገለጸው።

ገንዘቡን ባስረከብኩበት ወቅት 184 ሺ ዶላር ምንዛሬ ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ እንደሆነ ማወቁን የሚገልጸው ወጣቱ፣ ይህን ገንዘብ በታማኝነት ማስረከቡና ለባለንብረቱ እንዲደርስ መደረጉ ከምንም በላይ የህሊና እርካታ እንደሰጠው ነው የተናገረው። እንደእርሱ እምነት ያለፉበትን እና ያልደከሙበትን ገንዘብ መጠቀም ሰላምን ያሳጣል።

ገንዘቡን በማስረከቤ በርካታ ሰዎች «ጨዋ፣ ጎበዝ » አንዳንዶች ግን «ፈዛዛ፣ ሕይወትህን የሚቀይር ገንዘብ እንዴት ትመልሳለህ» እንዳሉት ነው ያመለከተው። «ያልደከምኩበትን ንብረት ባለመውሰዴ ሁሌም ደስተኛ እንድሆን ያደርገኛል» ብሏል።

ወጣት ቴዎድሮስ ተፈሪ የእነብርሃኑን ሥራ የሚቆጣጠር ነው፤ ወጣት ብርሃኑ ከፍተኛ ገንዘብ ማግኘቱን ለቅርብ አለቃው ካሳወቀ በኋላ መድረሱን ይናገራል። በቦታውም እንደደረሰም በብርሃኑ ፊት ላይ መደናገጥ ማየቱን ይገልጻል። በአየር መንገዱ ገንዘብም ሆነ ዕቃ ጠፍቶ ሲገኝ ይመለሳል ያለው ወጣት ቴዎድሮስ ይህን ያህል ገንዘብ ተገኝቶ እንደማይታወቅ ይናገራል ።

አየር መንገዱ እንዲህ ዓይነቶችን ታማኞች ማበረታታትና እውቅና መስጠት እንዳለበት የሚያመለክተው ወጣት ቴዎድሮስ፤ ይህን ማድረጉ «ለሌሎች ትምህርት ይሰጣል፤ በጎ ተግባር እንዲበረታታ ያደርጋል » ሲል ይናገራል። ብርሃኑ የሰራው መልካም ሥራ እንዳስተማረው ነው የገለጸው።

የሴኪዩሪቲ ኦፊሰር አቶ ዶክተር ዶኦለ በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ገንዘቡ በርከት ያለ በመሆኑ ከሌሎች ጋር በስፍራው ተገኝተው ርክክብ እንዲፈጸም አድርገዋል።

«አየር መንገዱ እንዲህ ዓይነቶቹን ታማኞች ሊያበረታታ ይገባል» የሚሉት አቶ ዶክተር፣ ይህ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ለደንበኛው መመለሱ ለአየር መንገዱ ትልቅ ዝናና ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ነው የሚናገሩት ። ደንበኛውም ያለምንም ስጋት መንቀሳቀስ እንደሚችል እንዲረዳና በአየር መንገዱ ላይም የበለጠ እምነት እንዲጥል የሚያደርገው መሆኑንም ነው ያመለከቱት።

ስማቸው እንዳይጠቀስና ምስላቸው እንዳይወጣ የፈለጉት ጋምቢያዊው ባለንብረት በበኩላቸው 184 ሺ የአሜሪካ ዶላሩን ከአየር መንገዱ ትናንት በተቀበሉበት ሥነ ሥርዓት ላይ «ሕይወቴን ያገኘሁ ያህል ተሰምቶኛል» ነበር ያሉት። «የኢትዮጵያ አየር መንገድን ከልቤ ላመሰግነው እፈልጋለሁ። የበለጠም እንድተማመንበት አድርጎኛል» ብለዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የህዝብ ግንኙነት እንደገለጸው፤ በአየር መንገዱ በርካታ መንገደኞች ይተላለፋሉ። በእዚህ ወቅት ከትንሽ እስከ ትልቅ ገንዘብም ሆነ ዕቃ ተረስቶ ሊወጣ ይችላል። ሠራተኛው በታማኝነት ያገኘውን በመመለስ ለባለንብረቱ እንዲደርስ ይደረጋል።

«የአየር መንገዱ ሠራተኛ ገንዘቡን በማግኘቱ ብቻ የተለየ ነገር አይደረግለትም» ያለው የህዝብ ግንኙነቱ አየር መንገዱ የሚያስተናግዳቸውን ደንበኞች የመንከባከብና የእነርሱ የሆኑትንም ሁሉ የመጠበቅ ኃላፊነት አለበት። እንዲህ ዓይነት ታማኝነትን ላሳዩ ሠራተኞች «እውቅና ይሰጣል» በማለት ነው የገለጹት። 
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment