Friday, May 24, 2013

ለኅብረቱ 50ኛ ዓመት በዓል ጠንካራ የጥበቃ ሥርዓት ተዘርግቷል

(May 24, 2013, (አዲስ አበባ))--የቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት የተመሰረተበት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓልና የኅብረቱ 21ኛ የመሪዎች ስብሰባ ያለምንም የፀጥታ እንከን ለማካሄድ የሚያስችል በቂ ዝግጅት በማድረግ ጠንካራ የጥበቃ ሥርዓት መዘርጋቱን የፌዴራል ፖሊስ አስታወቀ።

የፌዴራል ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮማንደር አበበ ዘሚካኤል በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፤ በዓሉና ጉባዔው ያለምንም እንከን እንዲካሄድ ፌዴራል ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ጋር በጋራ እየሠራ ነው። የጥበቃ ሥርዓቱ ያለፉት ዓመታትን የፀጥታ አጠባበቅ ተሞክሮ በመገምገም፣ በሰው ኃይልና በአጋዥ የቴክኖሎጂ ውጤቶችም እንዲደራጅ በማድረግ የተዘረጋ ነው።

የፀጥታ አጠባበቁን አስተማማኝ ለማድረግም ከብሔራዊ ደኅንነት፣ ከአዲስ አበባና ከኦሮሚያ ፖሊስ የተውጣጣ ኮማንድ ፖስት መቋቋሙን ኮማንደር አበበ ገልጸዋል። በየደረጃው የዕዝ ሰንሰለት መዋቀሩንም አስታውቀዋል።
\
እንደ ኮማንደሩ ገለጻ፤ በዓሉና ጉባዔው ሲካሄዱ ከመቼውም ጊዜ በላይ አስተማማኝ ፀጥታ እንዲሰፍን እንግዶች በሚገቡበት አካባቢና በሚያርፉባቸው ሆቴሎች ተገቢው የጥበቃ ሥራ ከአዲስ አበባ አስተዳደር በአጠቃላይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የተቀናጀ ተግባር ማከናወን የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው።

«ሕዝቡ እንግዳ ተቀባይ ነው፤ በእዚህም ልምዱና ተሞክሮ አለው ያሉት ኮማንደር አበበ፣ ይህ ሕዝብ የፀጥታ  ጥበቃው አካል እንዲሆን የሚያስችል ሥራ መከናወኑን አመልክተዋል። ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና ከሌሎች አካላት ጋር ተሳስረን እየሠራን እንገኛለን» ብለዋል። በአዲስ አበባ አስተዳደርና  በየወረዳው ያሉ አካላት ጭምር ተቀናጅተው የሚሠሩበት ሁኔታ መፈጠሩንም አመልክተዋል።

«ፌዴራል ፖሊስ ወይም የተወሰነ የፀጥታ አካል ብቻውን የሚሠራው ሥራ የለውም» ያሉት ኮማንደሩ፤ ከኅብረተሰቡ ጋር በመሆን እንደሚሠራ ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪም  በከተማዋ እየተካሄደ ከሚገኘው የመንገድና የባቡር መስመር ግንባታ ጋር በተያያዘ በሚፈጠረው የትራፊክ መጨናነቅ ፈጣን አገልግሎት ማግኘት እንደሚቸገር ጠቅሰው፤ ችግሩን በትዕግስት በማለፍ እንደተለመደው ተባባሪ እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል።  
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

2 comments:

Anonymous said...

I AM VERY HAPPY WITH YOUR VERY VERY NICE JOB
TO PROTECT OUR COUNTRY WITH OUT ANY INCIDENT DURING
THE FIFTY YEARS CELEBRATION OF AFRICAN UNION

THANK YOU POLICE

Anonymous said...

Police yemiakora sira sera mezegaja biet yageritwan nitsena yetebik hizbum enditebaber yehun yehizib shintibetoch yekukuamu yalem mesakiana yager maferia anhun

Post a Comment