Friday, April 19, 2013

አሠልጣኝን መሳደብ መፍትሔ ያመጣል? (ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ)

(Apr 19, 2013,  (አዲሰ አበባ))--አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው በሙያቸው ለአገራቸው እያበረከቱት ባለው አስተዋጽኦ ምስጋናና አክብሮት እንጂ ነቀፌታ አይገባቸውም፤ ለማንኛውም ስፖርታዊ ውድድር እድገት ደጋፊው አስተዋፅኦ እንዳለው መናገር አያስፈልግም። ደጋፊ የሌለው ስፖርት ብዙ ርቀት መጓዝ እንደማይችል እሙን ነው። ደጋፊዎች በስፖርት እድገት ላይ የሚያበረክቱት አዎንታዊ አስተዋፅኦ እንዳለ ሁሉ አሉታዊ ተፅእኖ እንደሚያሳድሩም አይካድም።

የአገራችን ህዝብ ለስፖርት በተለይም ለእግር ኳስ ያለው ፍቅር ቃላት ከሚገልፁት በላይ ለመሆኑ ዋልያዎቹ ከሰላሳ አንድ ዓመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከሱዳን አቻቸው ጋር አዲስ አበባ ስታድየም ላይ ያደረጉትን ጨዋታ ማስታወስ በቂ ይሆናል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ በሱዳን ከሜዳው ውጪ ተሸንፎ ጥቅምት4 ቀን 2005ዓ.ም ደግሞ በሜዳው የመልስ ጨዋታ የሚያደርግበት ነበር። በዚህ እለት ዋልያዎቹ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከሱዳን ብሔራዊ ቡድን ያነሰ እድል ቢኖራቸውም እግር ኳስ አፍቃሪው የአገራችን ህዝብ ጨዋታውን «እናሸንፋለን» በሚል ትልቅ ተስፋ ከመደገፍ አልተቆጠበም።

ጨዋታው ከሚካሄድበት ዕለት ቀደም ብሎ ሁሉም የእግር ኳስ አፍቃሪና የተለያዩ ክለብ ደጋፊዎች በአንድነት እንዲሁም የመገናኛ ብዙኃኑ ቡድኑን ሲደግፉ ነበር የቆዩት።በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን ከየክልል የመጡ እግር ኳስ አፍቃሪዎች ጭምር ስታድየም አካባቢ እሳት እያነደዱ አድረው ደከመን ሳይሉ ብሔራዊ ቡድኑን እስከ ጨዋታው መጨረሻ ድረስ የደገፉበት ያ እለት ወደ ፊትም ሊጠቀስ የሚችል ታሪክ ነው ማለት ይቻላል።

እዚህ ላይ አንባቢዎች እንድትገነዘቡልኝ የማሳስበው ያለፈውን የአፍሪካ ዋንጫ ለማተት ፈልጌ አለመሆኑን ነው። የአገራችን እግር ኳስ አፍቃሪዎች ምን ያህል ለስፖርቱ ተገዢ እንደሆኑ መንደርደሪያ ይሆነኛል ብዬ ለማንሳት ፈልጌ እንጂ። የአገራችን እግር ኳስ አፍቃሪዎች ከላይ በተጠቀሱት ዓይነት ባህሪያት የሚታወቁ ቢሆንም አልፎ አልፎ በስታድየም የምናያቸው አላስፈላጊ ድርጊቶች የጥሩ እግር ኳስ አፍቃሪዎቻችንን ስም ሊያጎድፍ የሚችል ሆነዋል።

በተለይም ሰሞኑን በአዲስ አበባ ደርቢ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊሰና ኢትዮጵያ ቡና ባካሄዱት ጨዋታ ላይ የተንፀባረቀው አሉታዊ ድርጊት በእግር ኳሳችን ታሪክ አሳፋሪ የሚባል ነው። በዚህ ጨዋታ እለት የዋልያዎቹ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ጨዋታ ሊከታተሉ ስታዲየም ተገኝተው ሳለ በአንዳንድ ደጋፊዎች ተሰድበዋል። አሰልጣኙ በደጋፊዎች መሰደባቸውን ተከትሎም በእለቱ የጨዋታው ድባብ ለመደፍረስ ተገድዷል።

አሰልጣኙ ላይ የስድብ ናዳ ያወረዱት የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች እንደሆኑ አሰልጣኙ ተናግረዋል። በሌላም በኩል ተሳዳቢዎቹ ሙሉ በሙሉ የቡና ደጋፊዎች ናቸው ብሎ መደምደም እንደማይቻልም አሰልጣኙ መናገራቸው ይታወሳል። በእርግጥም አሠልጣኙን የሰደቡት ደጋፊዎች የቡና ደጋፊዎች ናቸው ብሎ መደምደም ይከብዳል። ምክንያቱም ክለቡ ለአሰልጣኙም ይሁን ለአገራችን እግር ኳስ አክብሮት ያላቸው ደጋፊዎች ባለቤት ነው ።

አሰልጣኝ ሰውነት የቡናን ክለብ ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ ያላደረጉበትም ምክንያት ክለቡ በጥቂት ደጋፊዎች ምክንያት ስሙ በመጥፎ እንዲነሳ ባለመፈለጋቸው ይመስላል።

አሰልጣኝ ምንም ውጤት ያምጣ ሊከበር እንደሚገባ አምናለሁ። አሰልጣኝ ሰውነት ማንም ያልቻለውን ችለው ውጤት አስገኝተዋል። አይቻልም የተባለውን እንደሚቻል በተጨባጭ ማሳየታቸውን የሚጠራጠር ያለም አይመስለኝም። አሰልጣኙ የምንመኘውና በማይቻል በሚመስለን አፍሪካ ዋንጫ ላይ ተሳትፈን ማንነታችንን እንድናሳይ ያደረጉ የአገራችን እግር ኳስ ባለ ውለታ ናቸው። ለዚህ ሃሳብ ተቃራኒ የሚሆን ካለ ተጨባጭ መረጃ ይዞ መከራከር ይችላል።

እኚህ አሰልጣኝ ብሔራዊ ቡድኑን ከበርካታ ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ በማስቻላቸው ብቻ ሊመሰገኑ ይገባል። ይህን አምኖ መቀበል የከበደው ሰው ካለ አሰልጣኙን በመሳደብ ሳይሆን ማሳመን ያለበት ግልፅ በሆነ መንገድ ማስረጃ አቅርቦ በመነጋገር ነው።

አሰልጣኙ እንደማንኛውም ሰው ስህተት ሊሰሩ እንደሚችሉ ልብ ልንል ይገባል። ከዚህ ቀደም ብቻ ሳይሆን አሁንም ወደ ፊትም አሰልጣኙ ስህተት ሊሰሩ ይችላሉ። ይህ ደግሞ በማንኛውም አሰልጣኝ ላይ ሊስተዋል የሚችል ነው።

እዚህ ላይ ሌላውን ዓለም መመልከት ያለብን ይመስለኛል። አሰልጣኝ የፈለገውን ዓይነት ስህተት ቢሰራ ስድብ ሳይሆን የሚቀርብበት ተቃውሞ ነው።

ቼልሲ ራፋኤል ቤኒቴዝን በጊዜያዊ አሰልጣኝነት ሲቀጥር ቂም ያለባቸው የቼልሲ ደጋፊዎች አሰልጣኝ ራፋኤልን በተለያዩ ጽሁፎችና መፈክሮች ከስራቸው እንዲሰናበቱ ጠየቁ እንጂ አሰልጣኙን የሚያንቋሽሽ ስድብ አልተሳደቡም። የአገራችን ደጋፊዎች ከዚህ መማር ይችላሉ። አንድ አሰልጣኝ እንኳን እየሰራና ለውጥ እያመጣ ቀርቶ በአንዳንድ አጋጣሚዎች ሳይሳካለት ቢቀር እንኳን መሰደብ ሳይሆን በግልፅ ችግሮቹ ሊነገሩት ነው የሚገባው።

አንዳንድ ስነ ምግባር የጎደላቸው ደጋፊዎች አውቀውም ይሁን ሳያውቁት የሚሰሩት ስህተት በአሰልጣኙ ላይ ብቻ ሳይሆን በአገራችን እግር ኳስ ላይም መጥፎ ጥላን የሚያጠላ ነው የሚል እምነት አለኝ ። ኢትዮጵያ በአሰልጣኝ ሰውነት አማካኝነት የፊፋን ደረጃ በከፍተኛ ደረጃ እያሻሻለች መጥታለች። ይህም ብቻ ሳይሆን በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ምድቧን በመምራት ከዚህ ቀደም ያልነበረ ታሪክ ለመስራት የተመቻቸ መንገድ ይዛለች።

አገራችን ይህን የያዘችውን መልካም ጎዳና ሳትለቅቅ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ የአሰልጣኙ ተነሳሽነትና ሞራል ቁልፍ ሚና አለው። ለዚህም የአሰልጣኙ መሰደብ ዞሮ ዞሮ የሚጎዳው ብሔራዊ ቡድኑን መሆኑን መረዳት ያሰፈልጋል።

አንድ አሰልጣኝ ብሔራዊ ቡድኑን እያሠለጠነ ከሆነ የጊዜ ገደብ ተሰጥቶት በነፃነት ሊሰራ ይገባል። ለውጥ ካላመጣ ደግሞ በተገቢው መንገድ ግልፅ ሆነን ስህተቱን በመናገር መስተካከል ያለባቸው ጉድለቶች እንዲስተካከሉ ማድረግ እንጂ ስድብ ለምንም አይነት ችግር መፍትሄ ሊሆን እንደማይችል መረዳት ተገቢ ነው የሚሆነው።
አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment