Friday, March 22, 2013

ተሽከርካሪዎች ላይ ተገጥሞ በሳተላይት አቅጣጫን የሚያመለክት መሣርያ ለገበያ ቀረበ

(Mar 23, 2013, (አዲሰ አበባ))--ሰአን በተሰኘው ኩባንያ አማካይነት ላለፉት ሦስት ዓመታት ዝግጅት ሲደረግበት የቆየውና የዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍ እንዳደረገለት የተገለጸው ሥርዓት፣ በተሽከርካሪዎች ውስጥ ከመመልከቻ መስታወት አነስተኛ መጠን ያለው፣  በሳተላይት አማካይነት በሚተላለፍ መረጃ እየታገዘ አቅጣጫ የሚያመላክት መሣርያ ለገበያ ቀረበ፡፡

ሰአን ሜትሮ ፖሊታን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ያዘጋጀውና ‹‹መሪ›› የሚል ስያሜ የተሰጠው የሳተላይት አቅጣጫ አመላካች ሥርዓት፣ በአዲስ አበባ የሚገኙ ከ30 ሺሕ በላይ የመዳረሻ ሥፍራዎችንና ልዩ ልዩ ተቋማትን የሚያካትት ነው፡፡ የኩባንያው ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶክተር ሰይፈ ሥላሴ አያሌው እንዳስታወቁት፣ ለመሣርያው የተዘጋጀው የካርታ ሥራና የተቋማት መረጃዎች የተሟላው በአዲስ አበባ ሰባት ሺሕ ኪሎ ሜትር የደርሶ መልስ ምልልስ በማካሄድ ነው፡፡

አሽከርካሪዎች ቀድመው ወደሚሄዱበት አካባቢም ሆነ ተቋም በአግባቡ የሚጠቁም የአቅጣጫ መረጃ ባለማግኘታቸው ሳቢያ የሚያባክኑት ጊዜና ገንዘብ እንዲሁም የነዳጅ ፍጆታን ያስቀራል የተባለው ይህ መሣርያ፣  ለተቋማቱ ተገልጋዮችና ደንበኞችም ከውጣ ውረድና አላስፈላጊ ወጪዎች እንዲድኑ ያስችላል ተብሏል፡፡ ለከተማው አስተዳደር ደግሞ የትራፊክ ፍሰቱን በአግባቡ እንዲያስተናግዱ በማገዝ አማራጭ መንገዶችን ለማመላከት እንደሚያስችል ተነግሮለታል፡፡

መሣርያው ከተጫነለት ከ30 ሺሕ በላይ የመዳረሻ ሥፍራዎች ጋር ተዳምሮ እስከ ሰባት ሺሕ ብር በሚጠጋ ዋጋ ለገበያ እንደሚቀርብ የገለጹት ዶክተር ሰይፈ ሥላሴ፣ ኩባንያቸው የመሣርያው ክምችት ያለው በመሆኑ የአቅርቦት እጥረት እንደማይገጥመውና በዋናነትም ለከተማዋ አሽከርካሪዎች ትኩረት እንደሰጠ ገልጸዋል፡፡

የዓለም ባንክ ለአንድ ዓመት በሰጠው የፋይናንስ ድጋፍ ታግዞ ሥራውን ያከናወነው ሰአን ሜትሮ ፖሊታን፣ ‹‹መሪ የኢትዮጵያ ሳተላይት ናቪጌሽን ሲስተም›› ብሎ በሰየመው የአቅጣጫ አመላካች መሣርያ ከ800 በላይ የመንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ከ2,300 በላይ ሬስቶራንቶች፣ ከ1,000 በላይ ካፍቴሪያዎች፣ ከ1,000 በላይ የእንግዳ ማረፊያዎችና ሆቴሎች፣ 150 የጉዞ ወኪሎች፣ ከ100 በላይ መኪና አከራዮች፣ በርካታ የትምህርት፣ የሙዚየሞችና የጋለሪዎች፣ ቤተ መጻሕፍትና ሌሎችም የመዳረሻ ሥፍራዎችን አካትቶ እንደያዘ ታውቋል፡፡

በቅርቡም በመላ አገሪቱ ይሠራጫል ተብሎ የሚጠበቀው ይህ የአቅጣጫ አመላካች መሣርያ፣ ወደ ፊት ተሻሽሎና ተጨማሪ አገልግሎቶችን አካትቶ ለተጠቃሚዎች እንደሚቀርብ ዶክተር ሰይፈ ሥላሴ አስታውቀዋል፡፡
ኢሬቴድ ዜና 

No comments:

Post a Comment