Saturday, September 17, 2011

«የዊክሊክስ መረጃ በኢትዮጵያና አሜሪካ የቆየ ግንኙነት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተፅዕኖ አይኖርም »

(ቀን 2011-09-17, አዲስ አበባ, ኢዜአ)፡- የአሜሪካ አምባሳደሮችን ዋቢ በማድረግ በቅርቡ በዊክሊክስ የተለቀቀው መረጃ በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ባለው የቆየ የወዳጅነት ግንኙነት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተፅዕኖ እንደማይኖር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አስታወቁ።

ቃል አቀባዩ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ትናንት በተለይ ለጋዜጣው ሪፖርተር እንዳስታወቁት፤ አምባሳደሮቹ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር በአንድ ወቅት ከደቡብ ሱዳን ሕዝበ ውሳኔ ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ የተነሳውን ጉዳይ በሚገባ አልተገነዘቡትም ወይም ለጉዳዩ የራሳቸውን ትርጉም ሰጥተው ይሆናል። ከዚህም የተነሳ ያስተላለፉት መሠረተ ቢስ መረጃ ዘላቂና ረጅም ዘመናት ያስቆጠረውን የሁለቱን ሀገሮች ግንኙነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አይፈጥርም ብለዋል።

የደቡብ ሱዳን ሕዝበ ውሳኔ ሊካሄድ በተቃረበበት ወቅት ሁለቱ ወገኖች በአቡጃ ባደረጉት አጠቃላይ የሰላም ስምምነት መሠረት ችግራቸውን እየፈቱ ባለበት ሁኔታ የግድ ሁነኛ ተደራዳሪ ያስፈልጋል የሚል አቋም ኢትዮጵያ እንደነበራት ቃለ አቀባዩ ጠቅሰው፤ በዚህ ወሳኝ ወቅት የዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት በሱዳኑ ፕሬዚዳንት አልበሽር ላይ ይዞት የነበረው አቋም አፍራሽ ተፅዕኖ ያሳድራል በማለት አቋሟን እንደገለጸችም አስታውሰዋል።

« ኢትዮጵያ በማንኛውም ሀገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ የመግባት ፍላጐት የላትም፤ ጥብቅ ገለልተኝነትን የምታራምድ ሀገር ናት» ያሉት ቃል አቀባዩ፣ የሁለቱም ወገኖች ጉዳይ በራሳቸው መፍትሔ ማግኘት ይችላል የሚል አቋም ስታራምድ መቆየቷን አመልክተዋል።

« ኢትዮጵያ አሁንም የምታራምደው ይህንን አቋም ነው፤ ይህን አቋም ማራመዷ ከአሜሪካ ጋር ባላት ሁለገብ ግንኙነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳርፋል ብለን አናምንም» ብለዋል።

በአሜሪካና ኢትዮጵያ መካከል ያለው ግንኙነት ዘላቂና ረዥም ዘመናትን ያስቆጠረ በጣም ጥሩ ግንኙነት መሆኑን አመልክተው፤ ግንኙነቱ ስትራቴጂክ እንደሆነም ጠቅሰዋል።

ልዩነቶች በተፈጠሩ ጊዜም በሠለጠነና በጨዋ መንገድ ሲፈቱ እንደኖሩ አብራርተው፤ ምናልባትም ከልዩነቶቻችን መካከል ይህ የአሁኑ አንዱ ሊሆን ይችላል ብለዋል።

በግንኙነታችን ላይ ደባ እንዲሸረብ አንፈልግም ያሉት ቃል አቀባዩ በማንኛውም መንገድ ይህ አሁን የተፈጠረው ጉዳይ በአሜሪካና በኢትዮጵያ ግንኙነት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተፅዕኖ እንደማይኖርም አስታውቀዋል።

የዊኪሊክ መረጃ መሠረተ ቢስና የኢትዮጵያን ገጽታ ማበላሸት የማይችል እንደሆነ አብራርተው፣ ሁሉም ነገር እያደር እየጠራ ሲሄድ ድርጊታቸው ውሸት ሆኖ እንደሚገኝ አመልክተዋል።

«የኢትዮጵያ መንግሥት በሽብርተኝነት ላይ የፀና አቋም አለው፤ የሽብርተኝነት ሰለባ ሆኖ የቆየ ነው ያሉት ቃል አቀባዩ፣ መንግሥት ሽብርተኝነትን በዲፕሎማሲው፣ በፖለቲካውና በወታደራዊው መስክ በጥብቅ ሲፋለም መቆየቱንም ገልጸዋል።
ምንጭ: የኢትዩጵያ ፕሬስ ድርጅት

No comments:

Post a Comment